(1) 1.አሊፍ፤ ላም፤ ራ፤. ይህ ቁርኣን አናቅጾቹ በጥንካሬ የተሰካኩ ከዚያም የተዘረዘሩ፤ ጥበበኛና ውስጠ አዋቂ ከሆነው (አምላክ) ዘንድ የተወረደ መጽሐፍ ነው::
(2) 2. መልዕክተኛው (እንዲህ በሚልበት ሰዎች ሆይ! ): «አላህን እንጂ ሌላን አትገዙ:: እኔ ለእናንተ ከእርሱ ዘንድ የተላኩ አስፈራሪና አብሳሪ ነኝ።»
(3) 3. (እንዲህም በሚልበት ሰዎች ሆይ! ): «ጌታችሁን ምህረት ለምኑት:: ከዚያ ወደ እርሱ ተመለሱ:: እስከ ተወሰነ ጊዜ ድረስ መልካምን መጥቀም ይጠቅማችኋል:: ለትሩፋት ባለቤት ሁሉ ችሮታውን (ምንዳዉን) ይሰጠዋል:: ብትሸሹም እኔ በእናንተ ላይ የታላቅን ቀን ቅጣት እፈራላችኋለሁ::
(4) 4. «መመለሻችሁ ወደ አላህ ብቻ ነው። እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነውና።»
(5) 5. ሙስሊሞች ሆይ! አስተውሉ! እነርሱ ከእርሱ ከአላህ ይደበቁ ዘንድ ደረቶቻቸውን ያጥፋሉ:: ሙስሊሞች ሆይ! አስተውሉ! ልብሶቻቸውን በሚከናነቡ ጊዜ የሚደብቁትንም ሆነ የሚገልጹትን ሁሉ ያውቃል:: እርሱ በደረቶች ውስጥ ያለውን ሁሉ አዋቂ ነውና::
(6) 6. በምድርም ላይ ምንም ተንቀሳቃሽ የለችም ምግቧ በአላህ ላይ ያለና ማረፊያዋንም ሆነ መርጊያዋን የሚያውቅ ቢሆን እንጂ:: ሁሉም ነገር ግልጽ በሆነው መጽሐፍ ውስጥ ነው::
(7) 7. አላህ ያ ሰማያትንና ምድርን በስድስት ቀናት ውስጥ የፈጠረ ነው:: ዐርሹም በውሃ ላይ ነበር:: የትኛችሁ ስራችሁ ያማረ መሆኑ ይፈትናችሁ ዘንድ ፈጠራችሁ:: «እናንተ ከሞት በኋላ በእርግጥ ተቀስቃሾች ናችሁ» ብትልም። እነዚያ የካዱት «ይህ ግልጽ ድግምት እንጂ ሌላ አይደለም።» ይላሉ::
(8) 8. ቅጣቱንም ለተቆጠሩ ጥቂት ጊዜያቶች ብናቆይላቸው «ከመውረድ የሚከለክለው ምንድን ነው?» ይላሉ:: ሙስሊሞች ሆይ! አስተውሉ:: በሚመጣባቸው ቀን ከእነርሱ ላይ ተመላሽ አይደለም:: በእርሱ ይሳለቁበት የነበሩትም ቅጣት በእነርሱ ላይ ይወርድባቸዋል::
(9) 9. ሰውንም ከችሮታችን ብናቀምሰውና ከዚያ ብንወስድበት እርሱ ተስፋ ቆራጭና ክህደተ ብርቱ ነው::
(10) 10. ካገኘችዉም ችግር በኋላ ጸጋዎቻችንን ብናቀምሰው «ችግሮች ከእኔ ላይ ተወገዱ።» ይላል:: አያመሰግንም:: እርሱ ተደሳችና ጉረኛ ነውና::
(11) 11. እነዚያ የታገሱና መልካም ሥራዎችንም የሰሩ ሁሉ እነዚያ ለእነርሱ ምህረትና ታላቅ ምንዳ አለላቸው::
(12) 12. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «በእርሱ ላይ (የሀብት) ድልብ ለምን አልተወረደም? ወይም ከእርሱ ጋር መልአክ ለምን አልመጣም?» ማለታቸውን በመፍራት ወደ አንተ ከሚወርደው ከፊሉን ልትተው በእርሱም ልብህ ጠባብ ሊሆን ይፈራልሃል:: አንተ አስፈራሪ ብቻ ነህ:: አላህ በሁሉ ነገር ላይ (ወኪል) ተጠባባቂ ነው::
(13) 13. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ይልቁንም «ቁርኣንን ቀጣጠፈው» ይላሉን? «እውነተኞች እንደሆናችሁ ብጤው የሆኑን አስር የተቀጣጠፉ ምዕራፎች እስቲ አምጡ:: ከአላህም ሌላ የቻላችሁትን ረዳት ጥሩ።» በላቸው።
(14) 14. ለእናንተ ምላሽ ካልሰጧችሁ «(ጣዖት አምላኪያን ሆይ!) የተወረደው በአላህ እውቀት ብቻ መሆኑንና ከእርሱ ሌላ አምላክ አለመኖሩንም እወቁ:: እናም አትሰልሙምን?» በላቸው።
(15) 15. ቅርቢቱን ህይወትና ጌጧን የሚሹ የሆኑትን ሁሉ ሥራዎቻቸውን ምንዳዋን በእርሷ ውስጥ ወደ እነርሱ እንሞላላቸዋለን:: እነርሱም በእርሷ ውስጥ ምንም አይጎድልባቸዉም::
(16) 16. እነዚያ እነርሱ በመጨረሻይቱ ዓለም ከእሳት በስተቀር የሌላቸው ናቸው:: የሰሩትም ሥራ በእርሷ ውስጥ ተበላሸ:: በቅርቢቱ ዓለም ይሰሩት የነበሩትም በጎ ሥራ ብልሹ ነው::
(17) 17. ከጌታው ዘንድ አስረጅ የደረሰውንና ከእርሱም የሆነ መስካሪ የሚከተለው ከቁርኣን በፊትም ለሙሳ መጽሐፍ መሪና እዝነት ሲሆን የመሰከረለት (ሰውና) የቅርቢቱን ህይወት እንደሚሻው (ሰው) ነውን? እነዚያ በእርሱ (ቁርኣን) ያምናሉ:: ከአህዛቦቹ በእርሱ የሚክድ ሰው ሁሉ መመለሻው እሳት ናት:: (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከእርሱም በመጠራጠር ውስጥ አትሁን:: እሱ ከጌታህ ዘንድ የሆነ እውነት ነው:: ግን አብዛኞቹ ሰዎች አያምኑም::
(18) 18. በአላህ ላይ ውሸትን ከሚቀጣጥፍ ይበልጥ በዳይ ማነው? እነዚያ በጌታቸው ላይ ይቀረባሉ:: መስካሪዎቹም «እነዚህ በጌታቸው ላይ የዋሹት ናቸው።» ይላሉ:: «አስተዉሉ! የአላህ እርግማን በበዳዮች ላይ ብቻ ይሁን።» ይባላል።
(19) 19. እነርሱም እነዚያ ከአላህ መንገድ ሰዎችን የሚከለክሉ የአላህን መንገድ መጥመሟንም የሚሹት ናቸው:: እነርሱም በመጨረሻይቱ ዓለም ከሓዲያን ናቸው።
(20) 20. እነዚያም በምድር ውስጥ ከአላህ የሚያመልጡ አልነበሩም:: ከአላህ ሌላ ለእነርሱ ረዳቶች አልነበሯቸዉም:: ለእነርሱ ቅጣቱ ይደራረብላቸዋል:: እውነትን መስማትን የሚችሉ አልነበሩም:: የሚያዩም አልነበሩም::
(21) 21. እነዚያ እነርሱ ነፍሶቻቸውን ያከሰሩና ይቀጣጥፉት የነበሩት ነገር የጠፋባቸው ናቸው::
(22) 22. እነርሱ በመጨረሻይቱ ዓለም በጣም ከሳሪዎቹ ለመሆናቸው ጥርጥር የለዉም።
(23) 23. እነዚያ ያመኑትና በጎ ሥራዎችን የሠሩት ወደ ጌታቸዉም የተዋረዱት እነዚያ የገነት ናቸው:: እነርሱ በውስጧ ዘላለም ዘውታሪዎች ናቸው::
(24) 24. የሁለቱ ክፍሎች ምሳሌ አይኑ የማያይ አይነ ስውር፤ ጆሮው የማይሰማ ደንቆሮ ሰውና አይኑ የሚያይ ጆሮው የሚሰማ ሰው ብጤ ነው:: ሁለቱ በምሳሌነት ይስተካከላሉን? አትገሰጹንም?
(25) 25. ኑሕን ወደ ህዝቦቹ ላክንና አላቸዉም: «እኔ ለእናንተ ግልጽ አስፈራሪ ነኝ።
(26) 26. «አላህን እንጂ ሌላን አትገዙ። እኔ ለእናንተ የአሳማሚን ቀን ቅጣት እፈራላችኋለሁና።»
(27) 27. ከህዝቦቹም መካከል እነዚያ የካዱት መሪዎች «ብጤያችን ሰው ሆነህ እንጂ አናይህም:: እነዚያም እነርሱ ሐሳበ ጥሬዎች የሆኑት ወራዶቻችን እንጂ ሌላ ተከትሎህ አናይህም:: ለእናንተም በእኛ ላይ ምንም ብልጫን አናይም:: ከቶውንም ውሸታሞች መሆናችሁን እንጠረጥራችኋለን።» አሉ።
(28) 28. እርሱም አላቸው: «ህዝቦቼ ሆይ! እስቲ ንገሩኝ ከጌታዬ በግልጽ ማስረጃ ላይ ሆኜ ከእርሱም ዘንድ የሆነን ችሮታ ነብይነት ቢሰጠኝና በእናንተ ላይ ግን ይህች እውነታ ብትደበቅባችሁ እናንተ ለእርሷ ጠይዎች ስትሆኑ እርሷን በመቀበል እናስገድዳችኋለንን?
(29) 29. «ህዝቦቼ ሆይ! በእርሱ የተላክሁበትን በማድረስ ላይ ገንዘብን አልጠይቃችሁም:: ምንዳዬ ከአላህ እንጂ ከሌላ አይደለም:: እኔም እነዚያን በአላህ ያመኑትን ከአጠገቤ አባራሪ አይደለሁም:: እነርሱ ከጌታቸው ጋር የሚገናኙ ናቸውና:: ግን እኔም የምትሳሳቱ ህዝቦች ሆናችሁ አያችኋለሁ::
(30) 30. «ህዝቦቼ ሆይ! ባባርራቸው ከአላህ ቅጣት የሚያድነኝ ማን ነው? አትገሰጹምን?
(31) 31. «ለናንተም እኔ ዘንድ የአላህ ግምጃ ቤቶች አሉ:: ሩቅንም አውቃለሁ አልላችሁም:: እኔም መልአክ ነኝ አልላችሁም:: ለእነዚያም ዓይኖቻችሁ ለሚያዋርዷቸው አላህ ደግ ነገርን እምነትን አይሰጣቸዉም አልልም:: አላህ በነፍሶቻቸው ውስጥ ያለውን ሁሉ ነገር አዋቂ ነው:: እኔ ያን ጊዜ ከበደለኞች እሆናለሁና።» አላቸው።
(32) 32. «ኑህ ሆይ! በእርግጥ ተከራከርከን:: እኛን መከራከርህንም አበዛህ:: ከእውነተኞቹም ከሆንክ የምታስፈራራብንን ቅጣት አምጣው እስቲ።» አሉ።
(33) 33. አላቸውም: «እርሱን የሚያመጣባችሁ አላህ የፈለገ ከሆነ ብቻ ነው። እናንተም የምታቅቱ አይደላችሁም።
(34) 34. «እናንተም አላህ ሊያጠማችሁ ፈልጎ ከሆነ ልመክራችሁ ብፈልግም ምክሬ አይጠቅማችሁም:: እርሱ ጌታችሁ ነው:: ወደ እርሱም ብቻ ትመለሳላችሁ።» አላቸው።
(35) 35. ይልቁንም ቀጠፈው ይላሉን? (ሙሐመድ ሆይ) «ብቀጥፈው ኃጢአቴ ቅጣቱ በእኔ ላይ ነው:: እኔም ከምታጠፉት ጥፋት ሁሉ ንጹህ ነኝ።» በላቸው።
(36) 36. ወደ ኑህም (እንዲህ በሚል) ተወረደ: «እነሆ ከህዝቦችህ በእርግጥ ካመኑት በስተቀር ወደፊት ሌሎች አያምኑም:: ይሠሩትም በነበሩት ክህደት አትዘን።
(37) 37. «በጥበቃችንና በትዕዛዛችን ሆነህ መርከቢቱን ሥራ። በእነዚያም በበደሉት ሰዎች ነገር አታናግረኝ። እነርሱ በእርግጥ የሚሰምጡ ናቸውና።» አለው።
(38) 38. ከወገኖቹም መሪዎቹ በእርሱ አጠገብ ባለፉ ቁጥር በእርሱ ላይ እየተሳለቁበት መርከቢቱን ይሠራል። አላቸውም: «በእኛ ብትሳለቁ እኛም እንደተሳለቃችሁብን በእናንተ እንሳለቅባችኋለን።
(39) 39. «የሚያዋርደው ቅጣት የሚመጣበትን በእርሱም ላይ ዘውታሪ ቅጣት የሚሰፍርበትን ማንነት ወደ ፊት ታውቃላችሁ።» አላቸው።
(40) 40. ትዕዛዛችንም በመጣና እቶኑም በገነፈለ ጊዜ «በመርከቧ ውስጥ ከየዓይነቱ ሁሉ ሁለት ሁለት (ወንድና ሴት) ቤተሰቦችህንም ቃል ያለፈበት ብቻ ሲቀር ያመነንም ሰው ሁሉ ጫን።» አልነው:: ከእርሱም ጋር ጥቂቶች እንጂ አላመኑም ነበር::
(41) 41. «‹መሄዷም መቆሟም በአላህ ስም ነው።› እያላችሁ በእርሷ ተሳፈሩ:: ጌታዬ መሓሪና አዛኝ ነውና።» አላቸው።
(42) 42. እርሷም እንደ ተራራዎች በሆነ ማዕበል ውስጥ እነርሱን ይዛቸው የምትንሻለል ስትሆን (በአላህ ስም ተቀመጡባት።) ኑህም ልጁን ከመርከቢቱ የራቀ ሆኖ ሳለ «ልጄ ሆይ! ከእኛ ጋር ተሳፈር። ከከሓዲያንም አትሁን።» ሲል ጠራው።
(43) 43. ልጁም «ከውሃው ወደሚጠብቀኝ ተራራ እጠጋለሁ።» አለ:: አባቱም «ዛሬ ከአላህ ትዕዛዝ ምንም ጠባቂ የለም:: እርሱ ብቻ ያዘነለት ካልሆነ በስተቀር።» አለው:: ማዕበሉም በመካከላቸው ጋረደ:: ልጁም ከሰማጮች ሆነ::
(44) 44. ተባለም «ምድር ሆይ! ዉሃሽን ዋጪ:: ሰማይ ሆይ! ዝናብሽን ያዢ።» ውሃዉም ሠረገ:: ቅጣቱም ተፈጸመ:: ጁዲይ በሚባለም ተራራ ላይ መርከቢቱ ተደላደለች:: «ለከሓዲያን ጥፋት ተገባቸው (ጥፉ)።» ተባለ።
(45) 45. ኑህም ጌታውን- «ጌታዬ ሆይ! ልጄ ከቤተሰቤ አንዱ ነው:: ቃል ኪዳንህም እውነት ነው:: አንተም ከፈራጆች ሁሉ ይበልጥ አዋቂ ነህ።» በማለት ጠየቀ (ተጣራ)::
(46) 46. አላህም «ኑህ ሆይ! እርሱ ከቤተሰብህ አይደለም:: እርሱ መልካም ያልሆነ ስራ ነው:: በእርሱ እውቀት የሌለህንም ነገር አትጠይቀኝ:: እኔ ከአላዋቂዎች እንዳትሆን እገስጽሃለሁ።» አለው::
(47) 47. «ጌታዬ ሆይ! በእርሱ ለእኔ እውቀት የሌለኝን ነገር የምጠይቅህ ከመሆን እኔ ባንተ እጠበቃለሁ:: ለእኔም ባትምረኝና ባታዝንልኝ ከከሳሪዎቹ እሆናለሁ።» አለ።
(48) 48. «ኑህ ሆይ! ከእኛ በሆነ ሰላም ባንተ ላይና አንተም ጋር ባሉት ህዝቦች ላይ በሆኑ በረከቶችም የተጎናጸፍክ ሆነህ ወደ ምድር ውረድ:: ከነሱው ዘሮች የሆኑ ህዝቦችም በቅርቢቱ ዓለም በእርግጥ እናስመቻቸዋለን:: ከዚያም ከእኛ የሆነ አሳማሚ ቅጣት ይደርስባቸዋል።» ተባለ።
(49) 49. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ይህ ዘገባ ከሩቁ ወሬዎች መካከል ወደ አንተ ያወረድነው ነው:: አንተም ሆንክ ህዝቦችህ ከዚህ በፊት የምታውቁት አልነበራችሁም:: ታገሥ ምስጉን የሆነችው ፍጻሜ ለሚጠነቀቁት ብቻ ናትና::
(50) 50. ወደ ዓድም ወንድማቸውን ሁድን ላክን:: አላቸው፡ «ወገኖቼ ሆይ! አላህን ብቻ ተገዙ:: ከእርሱ ሌላ ምንም አምላክ የላችሁም:: እናንተ ቀጣፊዎች እንጂ ሌላ አይደላችሁም::
(51) 51. «ህዝቦቼ ሆይ! በእርሱ (በማድረሴ) ላይም ምንዳን አልጠይቃችሁም:: ምንዳዬ በዚያ በፈጠረኝ ላይ እንጂ በሌላ ላይ አይደለም:: አታውቁምን?
(52) 52. «ህዝቦቼ ሆይ! ጌታችሁን ምህረትን ለምኑት:: ከዚያ ወደ እርሱ ተጸጸቱ:: ዝናብን በእናንተ ላይ ተከታታይ አድርጎ ይልክላችኋልና:: ወደ ኃይላችሁም ሀይልን ይጨምርላችኋል:: አመጸኞችም ሆናችሁ አትሽሹ::»
(53) 53. እነርሱም አሉ፡- «ሁድ ሆይ! በአስረጂ አልመጣህልንም:: እኛም ላንተ ንግግር ብለን አማልክቶቻችንን የምንተው አይደለንም:: እኛም ላንተ ትክክለኛ አማኞች አይደለንም።
(54) 54. «ከፊሎቹ አማልክቶቻችን በክፉ ነገር በዕብደት ለክፈውሃል እንጂ ሌላን አንልም።» አሉ:: እርሱም አላቸው: «እኔ አላህን አስመሰክራለሁ:: ከምታጋሩትም እኔ ንጹህ መሆኔን መስክሩ።
(55) 55. «ከእርሱ ሌላ አማልክትን ከምታጋሩት ንጹህ ነኝ። ሁላችሁም ሆናችሁ ተንኮልን ሥሩብኝ ከዚያ አታቆዩኝ።
(56) 56. «እኔ ጌታዬና ጌታችሁ በሆነው በአላህ ላይ ብቻ ተመካሁ:: በምድር ላይ ምንም ተንቀሳቃሽ የለችም እርሱ አናትዋን የያዛት ብትሆን እንጂ:: ጌታዬ (ቃሉም ሥራዉም) በቀጥተኛው መንገድ ላይ ነው።
(57) 57. «ብትዞሩም ወደ እናንተ የተላኩበትን ነገር በእርግጥ አድርሼላችኋለሁ:: ጌታዬም ሌላን ህዝብ ይተካል:: ምንም አትጎዱትም:: ጌታዬ በሁሉ ነገር ላይ ተጠባባቂ ነውና።» አላቸው::
(58) 58. ትዕዛዛችን በመጣ ጊዜ ሁድንና እነዚያን ከእሱጋ ያመኑትን ከእኛ በሆነው ችሮታ አዳን:: ከብርቱ ቅጣትም አዳናቸው::
(59) 59. ይህ ነገድ ዓድ ነው:: በጌታቸው ታዐምራት ካዱ:: መልዕክተኞቹንም አመጹ:: የኃያል ሞገደኛን ሁሉ ትዕዛዝም ተከተሉ::
(60) 60. በዚች በቅርቢቱ ዓለምም እርግማን እንዲከተላቸው ተደረጉ:: በትንሳኤም ቀን እንደዚሁ:: አስተውሉ! ዓዶች ጌታቸውን ካዱ። አስተውሉ! የሁድ ህዝቦች ለሆኑት ዓዶች ከእዝነት መራቅ ይገባቸው::
(61) 61. ወደ ሠሙዶችም ወንድማቸውን ሷሊህን ላክን። «ህዝቦቼ ሆይ! አላህን ተገዙ:: ከእርሱ ሌላ ለእናንተ አምላክ የላችሁም:: እርሱ በምድር ፈጠራችሁ:: በውስጧ እንድታለሟትም አደረጋችሁ:: ምህረቱንም ለምኑት:: ከዚያም ወደ እርሱ ተመለሱ:: ጌታዬ ለሁሉም ቅርብና ለለመነው ተቀባይ ነውና።» አላቸው።
(62) 62. እነርሱም «ሷሊህ ሆይ! ከዚህ በፊት በእኛ ውስጥ መሪ ልትሆን በእርግጥ የምትከጀል የነበርክ ስትሆን:: አባቶቻችን የሚገዙትን ከመገዛት ትከለክለናለህን? እኛም ወደሱ ከምትጠራን ነገር በእርግጥ አወላዋይ በሆነ መጠራጠር ውስጥ ነን።» አሉ።
(63) 63. ሷሊህም አለ: «ህዝቦቼ ሆይ! እስቲ ንገሩኝ ከጌታዬ በሆነ ማስረጃ ላይ ሆኜ ከእርሱም የሆነን ችሮታ ነብይነት ቢሰጠኝና ባልታዘዘው ከአላህ ቅጣት የሚያድነኝ ማነው? ከማጥፋትም በስተቀር ምንም አትጨምሩልኝም።
(64) 64. «ህዝቦቼ ሆይ! ይህች ለእናንተ ታዓምር ስትሆን የአላህ ግመል ናት:: ተዋትም በአላህ ምድር ውስጥ ትብላ:: በክፉም አትንኳት። ቅርብ የሆነ ቅጣት ያገኛችኋልና።» አለ።
(65) 65. ወግተው ገደሏትም ሷሊህም «በሀገራችሁም ሶስትን ቀናት ብቻ ተጠቀሙ ይህ የማይዋሽ ቀጠሮ ነው።» አላቸው::
(66) 66. እናም ትዕዛዛችን በመጣ ጊዜ ሷሊህንና እነዚያን ከእሱ ጋር ያመኑትን ከእኛ በሆነው እዝነት አዳንን:: ከዚያም ቀን ውርደት አዳንናቸው:: ጌታህ ብርቱውና ሁሉን አሸናፊው ነውና::
(67) 67. እነዚያን የበደሉትንም ከባድ ጩኸት ያዛቸው:: በየቤቶቻቸዉም ውስጥ የተንበረከኩ ሙት በድን ሆነው አደሩ(አነጉ)::
(68) 68. በእርሷ ውስጥ እንዳልኖሩ ሆኑ:: አስተውሉ! ሠሙዶች ጌታቸውን በእርግጥ ካዱ:: አስተውሉ! ለሠሙዶች ከአላህ እዝነት መራቅ ተገባቸው::
(69) 69. መልዕክተኞቻችንም ወደ ኢብራሂም በልጅ መውለድ ብስራት መጡለትና ሰላም አሉት:: እሱም ሰላም አላቸው:: ጥቂትም ሳይቆይ ወዲያውኑ የተጠበሰን የወይፈን ስጋ አመጣ::
(70) 70. እጆቻቸዉም ወደ ምግቡ የማይደርሱ መሆናቸውን ባየ ጊዜ ተግባራቸው እንግዳ ሆነበት:: ከእነርሱም ፍርሃት ተሰማው:: «አትፍራ እኛ ወደ ሉጥ ህዝቦች ተልከናልና።» አሉት።
(71) 71. ሚስቱም ቁማ ነበርና ሳቀች:: እናም በኢስሓቅ አበሰርናት:: ከኢስሐቅም በኋላ በልጁ በየዕቁብ አበሰርናት::
(72) 72. እርሷም «ዋልኝ እኔ አሮጊት ይህም ባለቤቴ ሽማግሌ ሆኖ ሳለ እወልዳለሁን? ይህ በእርግጥ አስደናቂ ነገር ነው።» አለች።
(73) 73. «በአላህ ትዕዛዝ ትደነቂያለሽን? :: የአላህ እዝነትና በረከት በእናንተ በኢብራሂም ቤተሰቦች ላይ ይሁን:: እሱ ምስጉንና ለጋሽ ነውና።» አሉ።
(74) 74. ከኢብራሂም ፍራቻው በሄደለትና ብስራት በመጣችለት ጊዜ በሉጥ ህዝቦች ነገር ይከራከረን ጀመር::
(75) 75. ኢብራሂም በእርግጥ ታጋሽ፤ አልቃሻ (እጅግ የሚማፀን) እና መላሳ ነውና::
(76) 76. (እነርሱም አሉት): «ኢብራሂም ሆይ! ይህን ክርክር ተው:: እነሆ የጌታህ ትዕዛዝ በእርግጥ መጥቷል:: እነርሱም የማይመለስ ቅጣት የሚመጣባቸው ናቸው።»
(77) 77. መልዕክተኞቻችንም ወደ ሉጥ በመጡ ጊዜ በእነርሱ ምክንያት አዘነ:: ልቡም በእነርሱ ተጨነቀ:: «ይህ ብርቱ ቀን ነዉ።» አለም።
(78) 78. ህዝቦቹም ወደ እርሱ እየተጣደፉ መጡና ከዚህም በፊት መጥፎ ሥራዎችን ይሠሩ ነበር:: «ህዝቦቼ ሆይ! እነዚህ ሴቶች ልጆቼ ናቸው:: ለእናንተ ይልቅ በጣም የጸዱ ናቸው:: አግቧቸው እናም አላህን ፍሩ:: በእንግዶቼም አታሳፍሩኝ። ከናንተ ውስጥ አንድ ቅን ሰው እንኳን የለምን?» አላቸው::
(79) 79. «ከሴቶች ልጆችህ እኛ ምንም ጉዳይ የሌለን መሆኑን በትክክል ታውቃለህ:: አንተም የምንሻውን በእርግጥ ታውቃለህ።» አሉት።
(80) 80. «በእናንተ ላይ ኃይል በኖረኝ ወይም ወደ ብርቱ ወገን ብጠጋ ኖሮ (የምሠራውን በሠራሁ ነበር)።» አላቸው።
(81) 81. «ሉጥ ሆይ! እኛ የጌታህ መልዕክተኞች ነን:: ህዝቦች ወደ አንተ በክፉ አይደርሱብህም:: ቤተሰብህንም ይዘህ ከሌሊቱ በከፊሉ ውስጥ ሂድ:: ከናንተም አንድም ወደ ኋላው አይገላመጥ:: ሚስትህ ብቻ ስትቀር:: እነሆ እርሷንማ እነርሱን የሚያገኛቸው ስቃይ ሁሉ ያገኛታልና:: ቀጠሯቸው ንጋቱ ላይ ነው:: ንጋቱ ቅርብ አይደለምን?» አሉት።
(82) 82. እናም ትዕዛዛችን በመጣ ጊዜ ከተማይቱን ላይዋን ከታችዋ አድርገን ገለበጥናት:: ተከታታይም የሆነን የሸክላ ድንጋይ በእርሷ ላይ አዘነብንባት::
(83) 83. ከጌታህ ዘንድ ምልክት የተደረገባት ስትሆን (አዘነብናት)። እርሷም (መንደሯ) ከበደለኞቹ ህዝቦች ሩቅ አይደለችም::
(84) 84. ወደ መድየንም ወንድማቸውን ሹዐይብን ላክን:: አላቸውም: «ህዝቦቼ ሆይ! አላህን ብቻ ተገዙ:: ከእሱ ሌላ ለእናንተ አምላክ የላችሁም:: ስፍርንና ሚዛንን አታጉሉ:: እኔ በጸጋ ላይ ሆናችሁ አያችኋለሁ:: እኔም በእናንተ ላይ የከባቢን ቀን ቅጣት እፈራላችኋለሁ::
(85) 85. «ህዝቦቼ ሆይ! ስፍርንና ሚዛንን በትክክል ሙሉ:: ሰዎችን መብቶቻቸውን አታጓድሉባቸው:: በምድርም ውስጥ አጥፊዎች ሆናችሁ አታበላሹ።
(86) 86. «አላህ ያስቀረላችሁ ለእናንተ የተሻለ ነው:: ትክክለኛ አማኞች እንደ ሆናችሁ አላህ በሰጣችሁ ውደዱ። እኔም መካሪ እንጂ በእናንተ ላይ ተጠባባቂ አይደለሁም።»
(87) 87. «ሹዐይብ ሆይ! ስግደትህ አባቶቻችን የሚገዙትን ጣኦታት እንድንተው ወይም በገንዘቦቻችን የምንሻውን መሥራትን እንድንተው ታዝሃለችን? አንተ በእርግጥ ታጋሹ ቅኑው አንተ ነህና።» አሉት።
(88) 88. (እርሱም) አለ: «ህዝቦቼ ሆይ! ንገሩኝ እስቲ ከጌታዬ በሆነ አስረጅ ላይ ሆኜ ከእርሱም የሆነን መልካም ሲሳይ ቢሰጠኝ በቅጥፈት ልቀላቅለው ይገባልን? የከለከልኳችሁንም ነገር በመፈጸም ልለያችሁ አልሻም:: በተቻለኝ ያህል ማበጀትን እንጂ አልሻም:: ለደግ ሥራ መታደሌ በአላህ ፈቃድ ብቻ እንጂ በሌላ አይደለም:: በእርሱ ላይ ብቻ ተመካሁ:: ወደ እርሱም እመለሳለሁ።
(89) 89. «ወገኖቼ ሆይ! እኔን መከራከራችሁ የኑህን ህዝቦች ወይም የሁድን ህዝቦች ወይም የሷሊህን ህዝቦች ያገኛቸው ቅጣት ብጤ አይነት እንዲያገኛችሁ አይገፋፋችሁ:: የሉጥም ህዝቦች ከናንተ ሩቅ አይደሉም።
(90) 90. «ጌታችሁንም ምህረት ለምኑት ከዚያ ወደ እርሱ ተመለሱ። ጌታዬ አዛኝና ወዳድ ነውና።» አለ።
(91) 91. «ሹዐይብ ሆይ! ከምትለው ነገር ብዙውን አናውቀዉም (አይገባንም):: እኛም አንተን በኛ ውስጥ ደከማ ሆነህ እናይሃለን:: ጎሶችህም ባልኖሩ ኖሮ በወገርንህ ነበር:: አንተም በእኛ ላይ የተከበርክ አይደለህም።» አሉት::
(92) 92. (እርሱም) አለ: «ህዝቦቼ ሆይ? ጎሳዎቼ በእናንተ ላይ ከአላህ ይልቅ የከበሩ ናቸውን? አላህን ከኋላችሁ ወደ ጀርባ አደረጋችሁት:: ጌታዬ በምትሠሩት ሁሉ ከባቢ ነው።
(93) 93. «ህዝቦቼ ሆይ! በችሎታችሁ ልክ ሥሩ እኔ ሠሪ ነኝ። የሚያዋርደው ቅጣት የሚመጣበትንና እርሱ ውሸታም የሆነው ማን እንደ ሆነ ወደ ፊት ታውቃላችሁ:: ጠብቁም እኔም ከናንተ ጋር ተጠባባቂ ነኝና።» አለ።
(94) 94. ትዕዛዛችን በመጣ ጊዜ ሹዐይብንና እነዚያን ከእርሱ ጋር ያመኑትን ከእኛ በሆነው ችሮታ አዳን:: እነዚያን የበደሉትንም (የጂብሪል) ጩኸት ያዘቻቸው። በየቤቶቻቸዉም ውስጥ ተንከፍርረው አደሩ::
(95) 95. በእርሷ ውስጥ እንዳልነበሩ ሆኑ:: አስተዉሉ! ሠሙድ ከአላህ እዝነት እንደራቀች መድየንም ትራቅ::
(96) 96. ሙሳንም በታዐምራቶቻችንና በግልጽ ብርሃን በእርግጥ ላክነው::
(97) ወደ ፈርዖንና ወደስዎቹ ላክነው፡፡የፈርዖንን ነገር ህዝቦቹ ተከተሉ፡፡ የፈርዖን ነገር ቀጥተኛ አል ነበረም፡፡
(98) በትንሳኤ ቀን ህዝቦቹን ይቀድማል፡፡ ከዚያም ወደ አሳት ያወርዳቸዋል፡፡ የሚገቡትም አገባብ ምንኛ ከፋ፡፡
(99) 99. በዚችም በቅርቢቱ ዓለም እርግማንን አስከተልናቸው:: በትንሳኤም ቀን እንደዚሁ። የተሰጡት ስጦታ ምንኛ ከፋ!
(100) 100. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ይህ ከላይ የተነገረው ከከተሞቹ ወሬዎች የተወሰነው ነው:: ባንተ ላይ እንተርከዋለን:: ከእርሷ ቋሚና እጭድም የሆነ አለ::
(101) 101. እኛም አልበደልናቸዉም:: ግን ነፍሶቻቸውን በደሉ:: የጌታህ ጉዳይ በመጣ ጊዜ እነዚያ ከአላህ ሌላ የሚገዟቸው አማልክቶቻቸው ሁሉ በምንም አላዳኗቸዉም:: ከማክሰርም በስተቀር ምንም አልጨመሩላቸዉም::
(102) 102. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) የጌታህ ቅጣት የከተሞችን ሰዎች በዳዮች ሲሆኑ በቀጣቸው ጊዜ ልክ እንደዚህ ነው:: ቅጣቱ በእርግጥ አሳማሚና ብርቱ ነው::
(103) 103. በዚህ ውስጥ የመጨረሻውን ቀን ቅጣት ለሚፈሩ ሁሉ መገሰጫ አለ:: ይህ የትንሳኤ ቀን ሰዎች በእርሱ የሚሰበሰቡበት ቀን ነው:: ይህ የሚጣዱት ቀን ነው::
(104) 104. ይህንን ቀን ለተቆጠረም (ለተወሰነ) ጊዜ እንጂ አናቆየዉም::
(105) 105. በሚመጣ ቀን ማንኛዉም ነፍስ በእርሱ ፈቃድ ቢሆን እንጂ አትናገርም:: ከእነርሱም መናጢም (እድለቢስ) እድለኛም አለ::
(106) 106. እነዚያ ያመጹትማ በእሳት ውስጥ ናቸው:: ለእነርሱ በእርሷ ውስጥ ማናፋትና መንሰቅሰቅ አላቸው::
(107) 107. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህ ከፈለገው በስተቀር ሰማያትና ምድር እስከዘወተሩ ድረስ በውስጧ ዘውታሪዎች ሲሆኑ በእሳት ውስጥ ይኖራሉ:: ጌታህ የሚፈልገውን ሠሪ ነውና::
(108) 108. እነዚያ እድለኞቹማ ጌታ ከሻው በስተቀር ሰማያትና ምድር እስከ ዘወተሩ ድረስ በውስጧ ዘውታሪዎች ሆነው በገነት ውስጥ ይኖራሉ:: የማያቋርጥ ስጦታን ተሰጡ::
(109) 109. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እነዚያ ከሓዲያን ከሚገዙት ጣኦት በመጠራጠር ውስጥ አትሁን:: አባቶቻቸው ከዚህ በፊት እንደሚገዙት እንጂ አይገዙም:: እኛም እነዚህን ፈንታቸውን የማይጓደል ሲሆን የምንሞላላቸው ነን::
(110) 110. ለሙሳም መጽሐፍን በእርግጥ ሰጠነው:: በእርሱም ተለያዩበት። ከጌታህ ያለፈች ቃል ባልነበረች ኖሮ በመካከላቸው አሁን ይፈረድ ነበር:: እነርሱም ከእርሱ ከቁርኣን አወላዋይ በሆነ መጠራጠር ውስጥ ናቸው::
(111) 111. ሁሉንም ጌታህ ሥራዎቻቸውን ምንዳቸውን በእርግጥ ይሞላላቸዋል:: እርሱ በሚሠሩት ሁሉ ውስጠ አዋቂ ነውና::
(112) 112. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ልክ እንደታዘዝከው ቀጥ በል። ካንተ ጋር ያመኑትም ቀጥ ይበሉ። ወሰንንም አትለፉ። እርሱ የምትሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነውና::
(113) 113. ወደ እነዚያም ወደ በደሉት ህዝቦች አትዘንበሉ:: እሳት ትነካችኋለችና:: ከአላህ ሌላ ጠባቂዎች የሏችሁም ከዚያ አትረዱም::
(114) 114. ሶላትንም በቀን ጫፍና ጫፎች ከሌሊትም ክፍሎች ፈጽም:: መልካም ሥራዎች ኃጢአቶችን ያስወግዳሉና:: ይህ ለተገሳጮች ሁሉ ግሳጼ ነው::
(115) 115. ታገስ አላህ የበጎ ሠሪዎችን ምንዳ አያጠፋምና::
(116) 116. ከናንተ በፊት ከነበሩት ከክፍለ ዘመናት (ሰዎች) ውስጥ በምድር ላይ ከማበላሸት የሚከለክሉ የመልካም ሥራዎች ቅሪት ባለቤቶች ለምን አልነበሩም? ግን ከእነርሱ ያዳንናቸው ጥቂቶቹ ከለከሉና ዳኑ:: እነዚያም የበደሉት ሰዎች አልከለከሉም። በእርሱ የተቀማጠሉበትን ተድላ ተከተሉ አመጠኞችም ነበሩ::
(117) 117. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህ ከተሞችን ባለቤቶቻቸው መልካም ሠሪዎች ሆነው ሳሉ በመበደል የሚያጠፋቸው አልነበረም::
(118) 118. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህ በሻ ኖሮ ሰዎችን ሁሉ አንድ ህዝብ ባደረጋቸው ነበር። የተለያዩም ከመሆን አይወገዱም::
(119) 119. ጌታህ ያዘነለት ብቻ ሲቀር ከመለያየት አይወገዱም:: ለዚሁም ነው የፈጠራቸው:: የጌታህ ቃልም «ገሀነምን ከአጋንንትና ከሰዎች ከሁሉም በእርግጥ እሞላታለሁ።» በማለት ተፈጸመች::
(120) 120. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከመልዕክተኞቹም ዜናዎች ተፈላጊውን ሁሉንም ልብህን በእርሱ የምናጸናበትን እንተርክልሀለን። በዚህችም ሱራ እውነቱ ነገር፣ ለምእምናን ግሳጼና ማስታወሻ መጥቶልሀል::
(121) 121. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ለእነዚያም ለማያምኑት (እንዲህ) በላቸው: «ባላችሁበት ሁኔታ ላይ ሥሩ:: እኛ ሠሪዎች ነን።
(122) 122. «የራሳችሁን ውጤት ተጠባበቁ እኛ ተጠባባቂዎች ነንና።» በላቸው::
(123) 123. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በሰማያትና በምድር ያለው ሚስጥር ሁሉ የአላህ ብቻ ነው:: ሁሉም ነገር ወደ እርሱ ብቻ ይመለሳል:: ስለዚህ እሱን ብቻ ተገዛው:: በእርሱም ላይ ብቻ ተመካ:: ጌታህም ከሚሰሩት ሁሉ ዘንጊ አይደለም::