24 - An-Noor ()

|

(1) 1.(ሙስሊሞች ሆይ!) (ይህ) ያወረድነውና በእናንተ ላይ (እንድትሰሩበት) የደነገግነው ምዕራፍ ነው:: እርሱ በርሷም ውስጥ ትገሰጹ ዘንድ ግልጽ አናቅጽን አውርደናል::

(2) 2. ዝሙተኛይቱ ሴትና ዝሙተኛው ወንድ ከሁለቱ እያንዳንዳቸው (ያላገቡ እንደሆኑ) መቶ ግርፋትን ግረፏቸው:: በአላህና በመጨረሻው ቀን የምታምኑ እንደሆናችሁ በእነርሱ ላይ በደነገገው በአላህ ፍርድ ርህራሄ አትያዛችሁ። ሙስሊሞች ሆይ! ቅጣታቸውንም በምትፈጽሙበት ጊዜ ከአማኞች የተወሰኑ ቡድኖች ይገኙበት::

(3) 3. ዝሙተኛ ወንድ ዝሙተኛን ሴት ወይም በአላህ አጋሪን ሴት እንጂ ሌላን አያገባም (አይፈልግም) :: ዝሙተኛይቱም ሴት ዝሙተኛ ወይም በአላህ አጋሪ ወንድ እንጂ ሌላ አያገባትም (አይፈልጋትም):: ይህም በአማኞች ላይ ተከልክሏል::

(4) 4. እነዚያ ጥብቆችን ሴቶች በዝሙት የሚሰድቡ ከዚያ በሰደቡበት አራት ምስክሮች ያላመጡ ሰማንያ ግርፋት ግረፏቸው:: ከእነርሱም ምስክርነትን ለሁልጊዜ አትቀበሉ:: እነዚያም እነርሱ አመጸኞች ናቸው::

(5) 5. እነዚያ ከዚህ በኋላ የተጸጸቱና ሥራቸውን ያሳመሩ ሲቀሩ:: አላህ በጣም መሓሪና አዛኝ ነውና::

(6) 6. እነዚያ ሚስቶቻቻውን (በዝሙት) የሚሰድቡ ለነሱም ከነፍሶቻቸው በስተቀር ምስክሮች የሌሏቸው የሆኑ የአንዳቸው ምስክርነት ከእውነተኞች ለመሆናቸው በአላህ ስም አራት ጊዜ ምሎ መመስከር ነው::

(7) 7. አምስተኛይቱም ከውሸታሞች ቢሆን በእርሱ ላይ የአላህ እርግማን እንዲሰፍንበት (ምሎ መመስከር ነው)

(8) 8. «እርሱም ከውሸታሞች ነው።» ብላ አራት ጊዜ በአላህ ስም መመስከሯ ከእርሷ ላይ ቅጣትን ይከላከልላታል::

(9) 9. አምስተኛይቱም እርሱ ከእውነተኞች ቢሆን በርሷ ላይ የአላህ ቁጣ ይኑርባት ብላ መመስከሯ ነው::

(10) 10. (እናንተ ያመናችሁ ሆይ!) በእናንተም ላይ የአላህ ችሮታና እዝነቱ ባልነበረና አላህ ጸጸትን ተቀባይና ጥበበኛ ባልሆነ ኖሮ (ውሸታሙን ሁሉ በዚሁ አለም ላይ ይገልጸው ነበር)::

(11) 11. እነዚያ መጥፎን ውሸት ያመጡ ከናንተው የሆኑ ቡድኖች ናቸው:: ለእናንተ ክፉ ነገር እንደሆነ አታስቡት፤ በእውነቱ እርሱ ለእናንተ መልካም ነገር ነው:: ከጭፍሮቹ ለእያንዳንዱ ሰው ከኃጢአት የሠራው ሥራ ዋጋ አለው:: ያም ከእነርሱ ትልቁን ኃጢአት የተሸከመው ለእርሱ ከባድ ቅጣት አለው::

(12) 12. (ውሸቱን) በሰማችሁት ጊዜ አማኞችና ምዕመናት በነፍሶቻቸው ለምን ደግን ነገር አልጠረጠሩም? ለምንስ «ይህ ግልጽ ቅጥፈት ነው።» አላሉም?

(13) 13. በእርሱ ላይ ለምን አራትን ምስክሮች አላመጡም? ምስክሮቹንም ካላመጡ እነዚያ አላህ ዘንድ ውሸታሞቹ እነርሱ ብቻ ናቸው::

(14) 14. በቅርቢቱም ሆነ በመጨረሻይቱ ዓለም በእናንተ ላይ የአላህ ችሮታና እዝነቱ ባልነበረ ኖሮ በውስጡ በገባችሁበት ወሬ ምክንያት ታላቅ ቅጣት በእርግጥ በደረሰባችሁ ነበር::

(15) 15. በምላሶቻችሁም በምትቀባበሉት ጊዜ ለእናንተም በእርሱ እውቀት በሌላችሁ ነገር በአፎቻችሁ በተናገራችሁና አላህ ዘንድ ከባድ ኃጢአት ሆኖ ሳለ ቀላል አድርጋችሁ ባሰባችሁት ጊዜ ከባድ ቅጣት በነካችሁ ነበር::

(16) 16. በሰማችሁትም ጊዜ: «በዚህ ጉዳይ ልንናገር ለእኛ አይገባንም:: አላህ ጥራት ይገባህ:: ይህ ከባድ ቅጥፈት ነው።» አትሉም ነበርን?

(17) 17. አማኞች እንደሆናችሁ ወደ ዚህ መሰል ተግባር ብጤው በፍጹም እንዳትመለሱ አላህ ይገስጻችኋል::

(18) 18. ለእናንተም አላህ አናቅጽን ይገልጽላችኋል:: አላህ ሁሉን አዋቂና ጥበበኛ ነው::

(19) 19. እነዚያ በነዚያ በትክክል በአላህ ባመኑት ሰዎች መካከል መጥፎ ወሬ እንድትስፋፋ የሚወዱ ለእነርሱ በቅርቢቱም ሆነ በመጨረሻይቱ ዓለም አሳማሚ ቅጣት አላቸው:: አላህ ሁሉን ነገር ያውቃል እናንተ ግን አታውቁም::

(20) 20. በእናንተም ላይ የአላህ ችሮታውና እዝነቱ ባልነበረ አላህም ሩህሩህና አዛኝ ባልሆነ ኖሮ (ቶሎ ባጠፋችሁ ነበር)::

(21) 21. እናንተ ያመናችሁሆይ! የሰይጣንን እርምጃዎች አትከተሉ:: የሰይጣንን እርምጃዎች የሚከተል ሰው ሁሉ ኃጢአትን ተሸከመ:: እርሱ በመጥፎና በሚጠላ ነገር ያዛልና፤ በእናንተም ላይ የአላህ ችሮታና እዝነቱ ባልነበረ ኖሮ ከናንተ አንድም ፈጽሞ (ከወንጀል) ባልጠራ ነበር:: ግን አላህ የሚሻውን ሰው ያጠራል:: አላህ ሁሉንም ሰሚ ሁሉንም አዋቂ ነው።

(22) 22. ከናንተም መካከል የችሮታና የክብረት ባለቤቶች የሆኑት ክፍሎች ለቅርብ ዘመዶችና ለድሆችና በአላህም መንገድ ለተሰደዱ ሰዎች ምንንም ነገር ላይሰጡ አይማሉ:: ይቅርታም ያድርጉ:: ጥፋተኞቹንም ይለፉ። አላህ ለእናንተ ሊምር አትወዱምን ? አላህ መሓሪና አዛኝ ነው::

(23) 23. እነዚያ ጥብቆቹንና ከዝሙት ዘንጊዎቹን ምዕምናት የሚሰድቡ ሰዎች ሁሉ በቅርቢቱም ሆነ በመጨረሻይቱ ዓለም ተረገሙ:: ለእነርሱም ታላቅ ቅጣት አለባቸው::

(24) 24. በእነርሱ ላይ ምላሶቻቸው እጆቻቸውና እግሮቻቸው ይሰሩት በነበሩት ነገር ሁሉ በሚመሰክሩባቸው ቀን ከባድ ቅጣት አለላቸው::

(25) 25. በዚያም ቀን አላህ ተገቢ ዋጋቸውን ይሞላላቸዋል:: አላህም ፍፁም ግልፅ እውነት መሆኑን ያውቃሉ።

(26) 26. መጥፎዎቹ ሴቶች ለመጥፎዎቹ ወንዶች፤መጥፎዎቹ ወንዶችም ለመጥፎዎቹ ሴቶች ብቻ የተገቡ ናቸው:: ጥሩዎቹ ሴቶችም ለጥሩዎቹ ወንዶች፤ ጥሩዎቹ ወንዶችም ለጥሩዎቹ ሴቶች ብቻ የሚገቡ ናቸው:: እነዚህ ጥሩዎቹም መጥፎዎቹ ከሚሉት ነገር ንጹህ የተደረጉ ናቸው:: ለእነርሱ በገነት ምህረትና መልካም ሲሳይ አለላቸው::

(27) 27. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እስከምታስፈቅዱና በባለቤቶቹ ላይ ሰላምታን እስከምታቀርቡ ድረስ በሌላ ሰዎች ቤቶች አትግቡ:: ይህ ጉዳይ ለእናንተም መልካም ነው:: እናንተ ትገነዘቡ ዘንድ በዚህ ታዘዛችሁ::

(28) 28. በውስጧም አንድንም ሰው ባታገኙ ለእናንተ እስከሚፈቀድላችሁ ድረስ አትግቧት። «ተመለሱ» ከተባላችሁም ተመለሱ:: እርሱ ለእናንተ የተሻለ ነው:: አላህ የምትሠሩትን ሁሉ አዋቂ ነው::

(29) 29. መኖሪያ ያልሆኑን ቤቶች ግን በውስጣቸው ለእናንተ ጥቅም ካላችሁ ሳታስፈቅዱ ብትገቡ በእናንተ ላይ ምንም ኃጢአት የለባችሁም:: አላህም የምትገልጹትንም ሆነ የምትደብቁትን ሁሉ ያውቃል::

(30) 30. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ለአማኞች ንገራቸው አይኖቻቸውን (ያልተፈቀደላቸዉን) ከማየት ይከልክሉ:: ብልቶቻቸውንም ይጠብቁ:: ይህ ለእነርሱ የተሻለ ነው:: አላህ በሚሠሩት ሁሉ ውስጠ አዋቂ ነውና::

(31) 31. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ለምዕመናት (ሴቶችም) ንገራቸው አይኖቻቸውን ይከልክሉ። ብልቶቻቸውንም ይጠብቁ:: ጌጣቸውንም ግልጽ ከሆነው በስተቀር ሆን ብለው አይግለጡ:: ጉፍታዎቻቸውንም በአንገትጌዎቻቸው ያጣፉ:: (የውስጥ) ጌጣቸውንም ለባሎቻቸው ወይም ለአባቶቻቸው ወይም ለባሎቻቸው አባቶች ወይም ለወንዶች ልጆቻቸው ወይም ለባሎቻቸው ወንዶች ልጆች ወይም ለወንድሞቻቸው ወይም ለወንድሞቻቸው ወንዶች ልጆች ወይም ለእህቶቻቸው ወንዶች ልጆች ወይም ለሴቶቻቸው (ሙስሊም ሴቶች) ወይም በእጆቻቸው ለያዙት (ባሪያ) ወይም ከወንዶች ለሴት ጉዳይ የሌላቸው ለሆኑ ተከታዮች ወይም ለእነዚያ በሴቶች ሀፍረተ ገላ ላይ ላላወቁ ህጻኖች ካልሆነ በስተቀር አይግለጹ:: ከጌጣቸዉም የሚሸፍኑት ይታወቅ ዘንድ በእግሮቻቸው አይምቱ:: ምዕመናኖች ሆይ! ከጀሀነም ቅጣት ትድኑ ዘንድ ሁላችሁም ወደ አላህ ተጸጸቱ::

(32) 32. (ሙስሊሞች ሆይ!) ከናንተ መካከል ትዳር የሌላቸውን ሰዎች አጋቡ:: ከወንዶች ባሮቻችሁና ከሴቶች ባሮቻችሁም ለጋብቻ ብቁ የሆኑትን ክፍሎች አጋቡ:: ድሆች ከሆኑም አላህ ከችሮታው ያከብራቸዋል:: አላህ ስጦታው ሰፊና ሁሉን አዋቂ ነውና::

(33) 33. እነዚያም የማግቢያን ጣጣ የማያገኙ ሰዎች አላህ ከችሮታው እስከሚያከብራቸው ድረስ ይጠብቁ። እነዚያንም እጆቻችሁ ከጨበጧቸው አገልጋዮች መካከል ገንዘብ ሰጥተው ነጻ ለመውጣት መጻጻፍን የሚፈልጉትን ከእነርሱ መልካም ነገርን ብታውቁ (ብታዩ) ተጻጻፏቸው:: አላህ ከሰጣችሁ ገንዘብም ስጧቸው:: ሴቶች ባሮቻችሁንም መጠበቅን ከፈለጉ የቅርቢቱን ህይወት ጥቅም ለመፈለግ ብላችሁ በዝሙት ተግባር ላይ አታስገድዷቸው:: የሚያስገድዳቸዉም ሰው አላህ ከመገደዳቸው በኋላ ለተገደዱት መሓሪና አዛኝ ነውና::

(34) 34. (ሰዎች ሆይ!) ወደ እናንተ አብራሪ የሆኑን አናቅጽ ከእነዚያ ከበፊታችሁ ካለፉትም ምሳሌዎች ዓይነት ምሳሌን ለጥንቁቆችም መገሰጫን በእርግጥ አወረድን::

(35) 35. አላህ የሰማያትና የምድር ብርሃን (አብሪ) ነው፤ የብርሃኑ ምሳሌ በውስጡ መብራት እንዳለባት ዝግ መስኮት፤ መብራቱ በብርጭቆ ውስጥ የሆነ፤ ብርጭቆው ደግሞ ፍጹም ሉላዊ ክብ የምትመስል ምስራቃዊም ምዕራባዊም ካልሆነች፤ ከተባረከች የወይራ ዛፍ ዘይቷ እሳት ባይነካዉም እንኳ ሊያበራ የሚቀርብ ከሆነች ዘይት የሚቃጠል እንደሆነ መብራት ነው:: ይህ በብርሃን ላይ የሆነ ብርሃን ነው:: አላህ ወደ ብርሃኑ የሚሻውን ሰው ይመራል:: አላህም ለሰዎች ምሳሌዎችን ያቀርባል። አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ አዋቂ ነውና።

(36) 36. አላህ እንዲከበሩና ስሙ በውስጣቸው እንዲወሳ ባዘዘው ቤቶች ውስጥ አወድሱት:: በውስጧ በጧትና በማታ ለርሱ ያጠሩታል።

(37) 37. አላህን ከማውሳትና ሶላትን ከመስገድ ዘካንም ከመስጠት ንግድም ሽያጭም የማያታልላቸው ልቦችና ዓይኖች በእርሱ የሚገላበጡበትን ቀን የሚፈሩ የሆኑ ሰዎች ያጠሩታል::

(38) 38. አላህም የሰሩትን ስራ መልካሙን ሊመነዳቸው ከችሮታዉም ሊጨምርላቸው ያጠሩታል:: አላህም ለሚሻው ሁሉ ያለ ግምት ይሰጣል::

(39) 39. እነዚያም በአላህ የካዱት ሰዎች መልካም ስራዎቻቸው በበረሃ ሜዳ እንዳለ ሲሪብዱ ነው:: ሲሪብዱ ውሃ የጠማው ሰው እንደውሃ አስቦት በቀረቡት ጊዜ ምንም ነገር ሆኖ እንደማያገኘው ነው፤ አላህንም እስፍራው ዘንድ ያገኘዋል:: ምርመራውንም ይሞላለታል፤ አላህም ምርመራው ፈጣን ነው።

(40) 40. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ወይም መጥፎ ስራዎቻቸው ከበላዩ ማዕበል ከበላዩ ደመና ያለበት ማዕበል በሚሸፍነው ጥልቅ ባህር ውስጥ እንዳሉ ጨለማዎች ነው:: እነዚያ ከፊላቸው ከከፊሉ በላይ ድርብርብ የሆኑ ጨለማዎች ናቸው:: በዚህች የተሞከረ ሰው እጁን ባወጣ ጊዜ ሊያያት አይደርስም:: አላህ ለእርሱ ብርሃንን ያላደረገለት ሰው ሁሉ ለእርሱ ምንጊዜም ምንም ብርሃን የለዉም::

(41) 41. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አላህ በሰማያትና በምድር ላይ ያለ ሁሉ በራሪዎችም ክንፎቻቸውን በአየር ላይ ያንሳፈፉ ሆነው ለእርሱ የሚያጠሩ መሆናቸውን አላወቅህምን? ሁሉም ስግደቱንና ማጥራቱን በእርግጥ አወቀ:: አላህ የሚሰሩትን ሁሉ አዋቂ ነውና::

(42) 42. የሰማያትም ሆነ የምድር ግዛት የአላህ ነው:: መመለሻም ወደ አላህ ነው::

(43) 43. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አላህ ደመናን የሚነዳ መሆኑን አላየህምን? ከዚያም ከፊሉን ከከፊሉ ያገናኛል፤ ከዚያም የተደራረበ ያደርገዋል፤ ዝናቡንም ከመካከሉ የሚወጣ ሆኖ ታየዋለህ፤ ከሰማይም ከደመናም በውስጡ ካሉት ጋራዎችም በረዶን ያወርዳል:: በእርሱም የሚሻውን ሰው በጉዳት ይነካል:: ከሻዉም ሰው ላይ ይመልሰዋል:: የብልጭታው ብርሃን ዓይኖችን ሊወስድ ይቀርባል::

(44) 44. አላህ ሌሊትንና ቀንን ያገላብጣል፤ በዚህም ለአስተዋዮች በእርግጥ ማስረጃ አለበት።

(45) 45. አላህም ተንቀሳቃሽን ሁሉ ከውሃ ፈጠረ:: ከእነርሱም መካከል በሆዱ ላይ የሚሄድ አለ፤ ከእነርሱም መካከል በሁለት እግሮቹ ላይ የሚሄድ አለ፤ ከእነርሱም መካከል በአራት እግሩ የሚሄድ አለ:: አላህ የሚሻውን ሁሉ ይፈጥራል:: አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነውና::

(46) 46. አብራሪን አናቅጽ በእርግጥ አወረድን፤ አላህ የሚሻውን ወደ ቀጥተኛ መንገድ ይመራዋል::

(47) 47. (አስመሳዮች) «በአላህና በመልዕክተኛው አምነናል ታዘናልም» ይላሉ። ከዚያም ከዚህ በኋላ ከእነርሱ ከፊሉ ይሸሻል:: እነዚያም ትክክለኛ አማኞች አይደሉም::

(48) 48. ወደ አላህና ወደ መልዕክተኛዉም በመካከላቸው ለሚከሰቱ ጉዳዮች ሊፈርድ በተጠሩ ጊዜ ከእነርሱ መካከል ከፊሉ ወዲያውኑ ይሸሻሉ::

(49) 49. እውነቱም (ሐቁ) ለእነርሱ ቢሆን ወደ እርሱ ታዛዣች ሆነው ይመጣሉ።

(50) 50. በልቦቻቸው ውስጥ በሽታ አለን? ወይስ በነብይነቱ ተጠራጠሩን? ወይስ አላህና መልዕክተኛው በእነርሱ ላይ የሚበድሉ መሆንን ይፈራሉን? ይልቁንም እነዚያ እነርሱ በዳዮቹ ናቸው::

(51) 51. የምዕምናን ቃል ግን የነበረው ወደ አላህና ወደ መልዕክተኛው በመካከላቸው ሊፈርድ በተጠሩ ጊዜ «ሰማን ታዘዝንም» ማለት ብቻ ነው:: እነዚህ ማለት እነዚያ የፈለጉትን የሚያገኙቱ ናቸው::

(52) 52. አላህንና መልዕክተኛውን የሚታዘዝ፤ አላህንም የሚፈራና ቁጣውን የሚጠነቀቀው፤ ፍላጎታቸውን የሚያገኙ እነዚያ እነርሱ ናቸው።

(53) 53. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ለዘመቻ ብታዛቸው በእርግጥ እንደሚወጡ የጠነከሩ መሓላዎቻቸውን በአላህ ስም ይምላሉ፤ «አትማሉ:: የታወቀ የንፍቅና መታዘዝ ነውና:: አላህ በምትሰሩት ነገር ሁሉ ውስጠ አዋቂ ነው።» በላቸው።

(54) 54. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ! ሙስሊሞች ሆይ!) «አላህንና መልዕክተኛውንም ታዘዙ:: ብትሸሹም አትጎዱትም:: በእርሱ ላይ ያለበት የተገደደውን ማድረስ ብቻ ነው:: በእናንተም ላይ ያለባችሁ የተገደዳችሁትን መታዘዝ ብቻ ነው:: ብትታዘዙትም ወደ ቀናው መንገድ ትመራላችሁ በመልዕክተኛው ላይ ግልጽ ማድረስ እንጂ ሌላ የለበትምና።» በላቸው።

(55) 55. አላህ እነዚያን ከናንተ መካከል በትክክል ያመኑትንና መልካም ስራዎችን የሰሩትን እነዚያን ከእነርሱ በፊት የነበሩትን እንደተካቸው ሁሉ በምድር ላይ በእርግጥ ሊተካቸው፤ ለእነርሱም ያንን የወደደላቸውን ሃይማኖታቸውን ሊያደላድልላቸው፤ ከፍርሃታቸዉም በኋላ ደህናነትን ሊለውጥላቸው የተስፋን ቃል ሰጥቷቸዋል:: በእኔ ምንንም የማያጋሩ ሆነው ሊገዙኝ ነው፤ ከዚያም በኋላ በሱ የካዱ ሰዎች እነዚያ አመጸኞች ማለት እነርሱ ብቻ ናቸው::

(56) 56. (ሙስሊሞች ሆይ!) ይታዘንላችሁ ዘንድ ሶላትን አስተካክላችሁ ስገዱ፣ ምጽዋትንም ስጡ፣ መልዕክተኛውንም ታዘዙ።

(57) 57. እነዚያን በአላህ የካዱትን በምድር ውስጥ የሚያቅቱ አድርገህ አታስብ፤ መኖሪያቸውም እሳት ናት:: ገሀነም በእርግጥም ምንኛ ትከፋ።

(58) 58. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እነዚያ እጆቻችሁ የጨበጧቸው ባሮች እነዚያም ከናንተ መካከል ለአካለ መጠን ያልደረሱት (ህፃናት) በሶስት ጊዜ: ከጎህ ስግደት በፊት፤ በቀትር ልብሶቻችሁን በምታወልቁበት ጊዜና ከምሽት ስግደትም በኋላ ወደ እናንተ ለመግባት ሲፈልጉ ያስፈቅዷችሁ:: እነዚህ የእናንተ ሶስት የሐፍረተ ገላ መግለጫ ጊዜያቶች ናቸውና:: ከእነዚህ በኋላ ግን በእናንተም ሆነ በነሱ ላይ (ያለፈቃድ በመግባት) ኃጢአት የለም:: እናንተን ለማገልገል በዙሪያችሁ ዟሪዎች ናቸውና:: ከፊላችሁ በከፊሉ ላይ ዟሪ ነውና፤ ልክ እንደዚሁ አላህ ለእናንተ ህግጋቱን ይገልጽላችኋል:: አላህ ሁሉን አዋቂና ጥበበኛ ነውና::

(59) 59. ከናንተም መካከል ለአቅመ አዳም በደረሱ ጊዜ እነዚያ ከእነርሱ በፊት የነበሩት ታላላቆች እንዳስፈቀዷችሁ ያስፈቅዱ:: ልክ እንደዚሁ አላህ ለእናንተ አንቀፆቹን ያብራራል:: አላህ ሁሉን አዋቂና ጥበበኛ ነው::

(60) 60. (ሙስሊሞች ሆይ!) እነዚያ ጋብቻን የማይፈልጉት ባልቴቶች በጌጥ የተገለጹ ሳይሆኑ የላይ ልብሶቻቸውን ቢጥሉ በእርሱ ኃጢአት የለባቸዉም:: ግን መጠበቃቸው ለእነርሱ የተሻለ ነው:: አላህም ለሚባለው ሁሉ ሰሚ ለሁሉም አዋቂ ነው::

(61) 61. (ከሰዎች ጋር በመብላት) በዕውር (አይነስውር) ላይ ኃጢአት የለበትም:: በአንካሳም ላይ ኃጢአት የለበትም:: በበሽተኛም ላይ ኃጢአት የለበትም:: በነፍሶቻችሁም ላይ ከቤቶቻችሁ ወይም ከአባቶቻችሁ ቤቶች ወይም ከእናቶቻችሁ ቤቶች ወይም ከውድሞቻችሁ ቤቶች ወይም ከእህቶቻችሁ ቤቶች፤ ወይም ከአባት ወንድሞች አጎቶቻችሁ ቤቶች፤ ወይም ከአባት እህቶች አክስቶቻችሁ ቤቶች ወይም ከእናት ወንድሞች የሹሞቻችሁ ቤቶች፤ ወይም ከእናት እህቶች የሜዎቻችሁ ቤቶች ወይም መክፈቻዎችን ከያዛችሁት ቤት ወይም ከወዳጃችሁ ቤት ብትበሉ ኃጢአት የለባችሁም:: ተሰብስባችሁ ወይም ተለያይታችሁ ብትበሉ በእናንተ ላይ ምንም ኃጢአት የለባችሁም:: ቤቶችንም በገባችሁ ጊዜ ከአላህ ዘንድ የሆነችን የተባረከች መልካም ሰላምታ በነፍሶቻችሁ ላይ ሰላም በሉ:: ልክ እንደዚህ አላህ አናቅጽን ለእናንተ ያብራራል፤ ልታውቁ ይከጅላልና::

(62) 62. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ትክክለኛ አማኞች ማለት እነዚያ በአላህና በመልዕክተኛው ያመኑት:: ከመልዕክተኛው ጋር በሚሰበሰብ ጉዳይ ላይ በሆኑ ጊዜ እስከሚያስፈቅዱት ድረስ የማይሄዱት ብቻ ናቸው:: እነዚያ የሚያስፈቅዱህ እርሱ እነዚያ በትክክል በአላህና በመልዕክተኛው የሚያምኑት ናቸው:: ለግል ጉዳያቸዉም ፈቃድ በጠየቁህ ጊዜ ከእነርሱ ላሻኸው ሰው ፍቀድለት:: ለእነርሱም ከአላህ ምህረትን ለምንላቸው:: አላህ መሓሪና አዛኝ ነውና::

(63) 63. አማኞች ሆይ በመካከላችሁ የመልዕክተኛውን ጥሪ ከፊላችሁ ከፊሉን እንደመጥራት አታድርጉት:: ከናንተ ውስጥ እነዚያን እየተከለሉ በመሽሎክሎክ የሚወጡትን አላህ በእርግጥ ያውቃቸዋል:: እነዚያም ትእዛዙን የሚጥሱ ሁሉ መከራ እንዳትደርስባቸው ወይም አሳማሚ ቅጣት እንዳያገኛቸው ይጠንቀቁ::

(64) 64. (ሙስሊሞች ሆይ! አስተዉሉ) በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የአላህ ብቻ ነው:: እናንተ በእርሱ ላይ ያላችሁበትን ሁኔታ በእርግጥ ያውቃል:: ወደ እርሱ የሚመለሱበትን ቀንም ያውቃል:: ከዚያ የሰሩትንም ሁሉ ይነግራቸዋል:: አላህም ነገሩን ሁሉ አዋቂ ነውና::