73 - Al-Muzzammil ()

|

(1) 1. አንተ ተከናናቢው ሆይ::

(2) 2. ሌሊቱን (ሁሉ) ጥቂት ሲቀር ቁም (ስገድ)::

(3) 3. ግማሹን (ቁም) ወይም ከእርሱ ጥቂትን ቀንስ::

(4) 4. ወይም በእርሱ ላይ ጨምር:: ቁርኣንንም በዝግታ አንብብ::

(5) 5. እኛ ባንተ ላይ ከባድ ቃልን እናወርዳለንና::

(6) 6. ሌሊት መነሳት (ህዋሳትንና ልብን) ለማስማማት በጣም ብርቱ ነው:: ለማንበብም ትክክለኛ ሰዓት ነው::

(7) 7. ላንተ በቀን ውስጥ ረዥም የመዘዋወርያ ሰዓት አለህ::

(8) 8. የጌታህን ስም አውሳ:: ወደ እርሱም (አምልኮ) መቋረጥን ተቋረጥ::

(9) 9. (እርሱም) የምስራቅና የምዕራብ ጌታ ነው:: ከእርሱ ሌላ ትክክለኛ አምላክ የለም:: መጠጊያ አድርገህም ያዘው::

(10) 10. (ከሓዲያንም) በሚሉት ላይ ታገስ:: መልካምንም መተው ተዋቸው::

(11) 11. የድሎት ባለቤቶችም ከሆኑት አስተባባዮች ጋር ተወኝ:: ጥቂትንም ጊዜ አቆያቸው::

(12) 12. ከእኛ ዘንድ ከባድ ማሰሪያዎችና እሳት አሉንና::

(13) 13. (ጉሮሮን) የሚያንቅ ምግብና አሳማሚ ቅጣትም አለ።

(14) 14. በዚያ ምድርና ጋራዎች በሚርገፈገፉበት፤ ጋራዎችም ፈሳሽ የአሸዋ ክምር በሚሆኑበት ቀን::

(15) 15. እኛ ወደ ፊርዖን መልዕክተኛን እንደላክን ሁሉ በእናንተ ላይ መስካሪ መልዕክተኛንም ወደ እናንተ ላክን።

(16) 16. ፊርዓውንም መልዕክተኛውን አመጸ:: ብርቱ መያዝንም ያዝነው::

(17) 17. (በአላህ) ከካዳችሁ ያን ልጆችን ሸበቶዎች የሚያደርገውን ቀን ቅጣት እንዴት ትጠነቀቃላችሁ?

(18) 18. ሰማዩ በቀኑ ተሰንጣቂ ነው:: ቀጠሮዉም ተፈፃሚ ነው::

(19) 19. ይህች መገሰጫ ናት። መዳንንም የሻ (የፈለገ) ሰው ወደ ጌታው (የሚያደርሰዉን) መንገድ ይይዛል::

(20) 20. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አንተ ከሌሊቱ ሁለት እጅ ያነሰን፤ ግማሹንም ሲሶውንም የምትቆም መሆንህን ጌታህ ያውቃል:: (ሙስሊሞች) ከእነዚያም አብረውህ ካሉ ከፊሎች የሚቆሙ መሆናቸውንም ያውቃል:: አላህ ሌሊትና ቀንን ይለካል:: ሌሊቱን በሙሉ የማትቆሙት መሆናችሁን አወቀ:: እናም በእናንተ ላይ ህጉን ወደ ማቃለል ተመለሰላችሁ:: ስለዚህ ከቁርኣን (በስግደት) የተቻላችሁን ያህል አንብቡ:: ከናንተ ውስጥ ሌሎችም በሽተኞች ከአላህ ችሮታ ለመፈለግ በምድር ላይ የሚጓዙ ሌሎችም፤ በአላህ መንገድ ሃይማኖት ላይ የሚጋደሉ እንደሚኖሩ አወቀ:: አቃለለላቸዉም ከቁርኣን የቻላችሁትን አንብቡ:: ሶላትንም ስገዱ:: ዘካንም ስጡ:: ለአላህ መልካም ብድርንም አበድሩ:: ከመልካም ስራም ለነፍሶቻችሁ የምታስቀድሙትን ሁሉ የተሻለና በምንዳም ታላቅ ሆኖ በአላህ ዘንድ ታገኙታላችሁ:: አላህን ምህረት ለምኑት:: አላህ መሀሪና አዛኝ ነውና::