64 - At-Taghaabun ()

|

(1) 1. በሰማያት ውስጥም ሆነ በምድር ውስጥ ያለው ሁሉ አላህን ያሞግሳል:: ንግስናው የእርሱ ብቻ ነው:: ምስጋናም ለእርሱ ብቻ ነው:: እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው::

(2) 2. እርሱ ያ የፈጠራችሁ ነው:: ከእናንተም መካከል ከሓዲ አለ:: ከእናተም መካከል አማኝ አለ:: አላህ የምትሰሩትን ሁሉ ተመልካች ነው::

(3) 3. (እርሱ) ሰማያትንና ምድርን በእውነት ፈጠረ:: ቀረጻችሁም ቅርጻችሁንም አሳመረ፡፡ መመለሻችሁም ወደ እርሱ ብቻ ነው::

(4) 4. በሰማያትና በምድር ውስጥ ያለውን ሁሉ ያውቃል:: የምትደብቋትንም ሆነ የምትገልጡትን ያውቃል:: አላህም በልቦች ውስጥ ያለውን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡

(5) 5. የእነዚያ ከአሁን በፊት የካዱትና የክህደታቸውን ቅጣት የቀመሱ ህዝቦች ወሬ አልመጣላችሁምን? ለእነርሱ አሳማሚ ቅጣት አለባቸው::

(6) 6. ይህ (ቅጣት) እነርሱ መልዕክተኞቻቸው አስረጂዎችን ይዘው ሲመጡላቸው «ሰዎች ይመሩናልን?» ስላሉና ስለ ካዱ፤ ከእምነትም ስለ ዞሩ ነው:: አላህ ከእነርሱ እምነት ተብቃቃ:: አላህ ተብቃቂና ምስጉን ነውና::

(7) 7. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እነዚያ በአላህ የካዱት ሰዎች በፍጹም የማይቀሰቀሱ መሆናቸውን አሰቡ። «(እንዴት አትቀሰቀሱም?) በጌታየ ይሁንብኝ ትቀሰቀሳላችሁ:: ከዚያ ትፈጽሙት የነበረውን ተግባራችሁን ትናገራላችሁ:: ይህ ተግባር ለአላህ ቀላል ነው» በላቸው።

(8) 8. በአላህ በመልዕክተኛውና በዚያም ባወረድነው ብርሃን እመኑም:: አላህ የምትሰሩትን ሁሉ ውስጠ አዋቂ ነውና።

(9) 9. (ይኸዉም) ለመሰብሰቢያው ቀን የሚሰበስባችሁ እለት አስታውሱ:: ይህ ቀን የቁጭት ቀን ነው:: በአላህም የሚያምን ሰው መልካምንም የሚሠራ ከርሱ ኃጢአቶቹን ይሰርይለታል፤ (ይፍቅለታል)፤ ከስሮቿ ወንዞች የሚፈሱባት ገነቶች ለዘላለም ያስገባዋል:: ይህ ታላቅ እደለኝነት ነው::

(10) 10. እነዚያም የካዱትና በአንቀፆቻችንም ያስተባበሉት የዝንታለም እሳት ባለቤቶች ማለት እነርሱ ናቸው:: (ጀሀነም) መመለሻነቷ ምን ይከፋ!

(11) 11. ከመከራም በአላህ ፈቃድ ቢሆን እንጂ ማንንም አይነካም:: በአላህ የሚያምን ሰው አላህ ልቡን ለትግስት ይመራዋል:: አላህም በሁሉም ነገር አዋቂ ነው::

(12) 12. አላህን ታዘዙ መልዕክተኛውንም ታዘዙ:: ብትዞሩም (መልዕክተኛውን አትጎዱም::) በመልዕክተኛችንም ላይ ያለበት በግልጽ ማድረስ ብቻ ነው::

(13) 13. አላህ ከእርሱ በስተቀር ትክክለኛ አምላክ የለም:: ትክክለኛ አማኞች በአላህ ብቻ ይመኩ::

(14) 14. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ከሚስቶቻችሁና ከልጆቻችሁ (ከአላህ መንገድ በማስተጓጎል) ለእናንተ ጠላቶች የሆኑ አሉ:: ስለዚህ ተጠንቀቋቸው:: ይቅርታ ብታደርጉ፤ ብታልፏቸዉም፤ ብትምሩዋቸዉም፤ አላህ በጣም መሀሪ፤ አዛኝ ነው::

(15) 15. ገንዘቦቻችሁና ልጆቻችሁ ለእናንተ መፈተኛ ብቻ ናቸው:: አላህም ከእርሱ ዘንድ ታላቅ ምንዳ አለ::

(16) 16. አላህንም የቻላችሁትን ያህል ፍሩት:: ትዕዛዙን ስሙም፤ ታዘዙም፤ ለግሱም፤ ለነፍሶቻችሁ መልካምን ይሰጣችኋልና:: የነፍሶቻቸዉን ንፍገት የሚጠበቁ ሰዎች ሁሉ እነዚያ እነርሱ ፍላጎታቸውን የሚያገኙ ናቸው::

(17) 17. ለአላህ መልካም ብድርን ብታበድሩት (ምንዳውን) ለእናንተ ይደራርበዋል:: ለእናንተም ይምራል:: አላህ አመስጋኝና ታጋሽ ነውና::

(18) 18. (እርሱ) ስውሩንም ይፋዉንም ሁሉን አዋቂ ኃያልና ጥበበኛ ነዉና።