16 - An-Nahl ()

|

(1) 1. (ከሓዲያን ሆይ!)፤ የአላህ ትዕዛዝ መጣ ስለዚህ አታጣድፉት:: አላህ ከማይገባው ሁሉ ጠራ:: ከሚያጋሩትም ሁሉ ላቀ::

(2) 2. ከባሮቹ መካከል በሚሻው ሰው ላይ መላዕክትን ከራዕይ ጋር በፈቃዱ ያወርዳል:: «ከሓዲያንን በቅጣት አስጠንቅቁ:: እነሆ ከእኔ በስተቀር ሌላ ትክክለኛ አምላክ የለም:: ፍሩኝም።» ማለትን አስታውቁ በማለት ያወርዳል።

(3) 3. ሰማያትንና ምድርን በእውነት ፈጠረ:: ከሚያጋሩት ሁሉ ጠራ :: ከፍም አለ::

(4) 4.ሰውን ከፍትወት ጠብታ ፈጠረው:: ከዚያም እርሱ ወዲያውኑ ትንሣኤን በመካድ ግልጽ ተከራካሪ ይሆናል::

(5) 5. (ሰዎች ሆይ!) ግመልን፤ ከብትን፤ ፍየልንም፤ በእርሷ ብርድ መከላከያ ሙቀትና ሌሎች ጥቅሞችም ያሉባት ስትሆን ለእናንተ ፈጠረላችሁ:: ከእርሷም ትበላላችሁ (ትመገባላችሁ)::

(6) 6. በእርሷም ወደ ማረፊያዋ በምትመልሷት ጊዜና ጧት ወደ ግጦሽ ቦታዋ በምታሰማሯት ወቅት ለእናንተ ውበት አለላችሁ።

(7) 7. ጓዞቻችሁንም ነፍሶቻችሁን በማስቸገር እንጂ ወደ ማትደርሱበት አገር ትሸከማለች:: ጌታችሁ በእርግጥ ሩህሩህ እና አዛኝ ነውና::

(8) 8. ፈረሶችን፤ በቅሎዎችንና አህዮችን ልትጋልቧቸውና ልታጌጡባቸው ፈጠረላችሁ:: የማታውቁትን ድንቅ ነገርም ወደ ፊት ይፈጥራል::

(9) 9. በአላህም ላይ በችሮታው ቀጥተኛውን መንገድ መግለጽ አለበት:: ከእርሷም ጠማማ አለ:: በሻም ኖሮ ሁላችሁንም ባቀናችሁ ነበር::

(10) 10. እርሱ ያ ከሰማይ ውሃን ያወረደ ነው:: ከእርሱም ለእናንተ መጠጥ አለላችሁ:: ከእርሱም እንስሳዎችን በእርሱ ውስጥ የምታሰማሩበት ዛፍ ይበቅልበታል::

(11) 11. በእርሱ አዝመራን፣ የዘይት ወይራን፣ ዘምባባዎችን፣ ወይኖችንና ከፍሬዎችም ሁሉ ያበቅልላችኋል:: በዚህ ክስተት ውስጥ ለሚያስተነትኑ ሕዝቦች ሁሉ በእርግጥ ትልቅ ተዓምር አለ።

(12) 12. ለእናንተ ሌሊትንና ቀንን ጸሐይንና ጨረቃንም ገራላችሁ:: ከዋክብትም በሙሉ በፈቃዱ ብቻ የተገሩ ናቸው:: በዚህ ክስተት ውስጥ ለሚያውቁ ሕዝቦች ሁሉ በእርግጥ አያሌ ተዓምራት አሉ::

(13) 13. በምድርም ላይ መልኮቹ የተለያዩ ሆኖ የፈጠረላችሁን ሁሉ ገራላችሁ:: በዚህ ውስጥ ለሚገሠጹ ሕዝቦች ሁሉ ግልጽ ተዐምር አለ::

(14) 14. እርሱ ያ ባሕርን ከእርሱ እርጥብ ስጋን ልትበሉና ከእርሱም የምትለብሱትን ጌጣጌጥ ታወጡ ዘንድ የገራ ነው:: መርከቦችንም በውስጡ ውሃውን ቀዳጆች ሆነው ሲንሻለሉ ታያለህ:: ከችሮታው ልትፈልጉና ልታመሰግኑም ገራላችሁ::

(15) 15. በምድር ውስጥ በናንተ እንዳታረገርግ ተራራዎችን ጣለባት። ትመሩም ዘንድ ጅረቶችንና መንገዶችን አደረገ።

(16) 16. ምልክቶችንም አደረገ:: በከዋክብትም እነርሱ ይመራሉ::

(17) 17. (ሰዎች ሆይ!) የሚፈጥር ልክ እንደማይፈጥር ነውን? አትገሠጹምን?

(18) 18. የአላህን ጸጋ ብትቆጥሩ አትዘልቋትም:: አላህ መሓሪና አዛኝ ነውና::

(19) 19. አላህ የምትደብቁትንና የምትገልጹትንም ሁሉ ያውቃል::

(20) 20. እነዚያም ከአላህ ሌላ የምትገዟቸው አማልክት ሁሉ ምንንም አይፈጥሩም:: እንዲያዉም እነርሱ ራሳቸው ይፈጠራሉ::

(21) 21. እነርሱ ሕያው ያልሆኑ ሙታን ናቸው:: እራሳቸው እንኳን መቼ እንደሚቀሰቀሱ አያውቁም::

(22) 22. አምላካችሁ አንድ አምላክ ብቻ ነው:: እነዚያም በመጨረሻይቱ ዓለም የማያምኑት ልቦቻቸው ከሓዲያን ናቸው:: እነርሱም የኮሩ ናቸው::

(23) 23. አላህ የሚደብቁትንና የሚገልጹትን ሁሉ የሚያውቅ ለመሆኑ ቅንጣት ያህል ጥርጣሬ የለበትም:: እርሱ ኩሩዎችን አይወድም::

(24) 24. ጌታችሁ በሙሐመድ ላይ ምን አወረደ በተባሉ ጊዜም: «የመጀመሪያዎቹ ሕዝቦች ተረቶችን ነው።» ይላሉ።

(25) 25. ይህንን የሚሉት በትንሣኤ ቀን ኃጢአቶቻቸውን በሙሉና ከነዚያም ያለ ዕውቀት ሆነው ከሚያጣምሟቸው ሰዎች ኃጢአቶች ከፊሉን ሊሸከሙ ነው:: ንቁ የሚሸከሙት ኃጢአት ምንኛ ከፋ!

(26) 26. እነዚያ ከእነርሱ (ከቁረይሾች) በፊት የነበሩት ከሓዲያን አሴሩ:: ከዚያም አላህ ሕንጻዎቻቸውን ከመሠረቶቻቸው አፈረሰ:: እናም ጣሪያው በላያቸው ላይ ወደቀባቸው:: ቅጣቱም ከማያውቁት ስፍራ መጣባቸው::

(27) 27. ከዚያም በትንሣኤ ቀን ያዋርዳቸዋል:: «እነዚያም በእነርሱ ጉዳይ ትከራከሩኝ የነበራችሁት ተጋሪዎቼ የት ናቸው?» ይላቸዋል። እነዚያ እውቀትን የተሰጡት ክፍሎች «ዛሬ ሐፍረቱና ቅጣቱ በከሓዲያን ላይ ነው።» ይላሉ።

(28) 28. እነዚያ ነፍሶቻችውን በዳይ ሆነው መላዕክት የሚገድሏቸው «ከክፉ ሥራ ምንም ነገር የምንሠራም አልነበርንም» ሲሉ ታዛዥነታቸውን ይገልፃሉ:: «በእውነት አላህ ትሠሩት የነበራችሁትን ነገር አዋቂ ነው።» ይባላሉ።

(29) 29. «የገሀነምንም ደጃፎች በውስጧ ዘውታሪዎች ስትሆኑ ግቡ።» ይባላሉ:: የኩሩ ሰዎች ሁሉ መኖሪያ የሆነችው ገሀነምም በእርግጥ ከፋች!

(30) 30. ለእነዚያም ለተጠነቀቁት ሰዎች «ጌታችሁ ምንን ነገር አወረደ?» ተባሉ:: «መልካምን ነገር አወረደ» አሉ:: ለእነዚያ ደግ ለሠሩት ህዝቦች ሁሉ በዚህች በቅርቢቱ ዓለም መልካም ኑሮ አለላቸው:: የመጨረሻይቱም አገር በእርግጥ በላጭ ናት:: የጥንቁቆቹም አገር ገነት ምን ታምር!

(31) 31. እርሷም የሚገቧትና በሥርዋ ወንዞች የሚፈሱባት ስትሆን የመኖሪያ አትክልቶች (ጀነት) ናት:: ለእነርሱም በውስጧ የሚሹት ነገር ሁሉ አለላቸው:: ልክ እንደዚሁም አላህ ጥንቁቆችን ይመነዳል::

(32) 32. እነዚያ ጥሩ ሆነው መላዕክት «ሰላም ለእናንተ ይሁን" እያሉ የሚገድሏቸው "ትሠሩት በነበራችሁት ሥራ ምክንያትም ወደ ገነት ግቡ።» ይባላሉ።

(33) 33. ከሓዲያን የመላዕክትን ወደ እነርሱ መምጣት ወይም የጌታህ ትዕዛዝ መምጣቱን እንጂ ሌላን ይጠባበቃሉን? ከእነርሱ በፊት የነበሩትም ልክ እንደዚህ ሠርተዋል:: አላህም አልበደላቸዉም:: ግን እነርሱ ነፍሶቻቸውን የሚበድሉ ነበሩ::

(34) 34. እናም የሠሯቸዉም ኃጢአቶች ቅጣት አገኛቸው:: ይሳለቁበት የነበሩት ነገር ሁሉ በእነርሱ ላይ ወረደባቸው::

(35) 35. እነዚያም ጣዖታትን በአላህ ያጋሩ ህዝቦች «አላህ በሻ ኖሮ ከእርሱ ሌላ እኛም ሆንን አባቶቻችን ምንንም ባልተገዛን ነበር:: ያለ እርሱም ትዕዛዝ ምንንም እርም ባላደረግን ነበር።» አሉ:: እነዚያም ከእነርሱ በፊት የነበሩት ህዝቦች ልክ እንደዚሁ ሠሩ:: በመልዕክተኞቹም ላይ ግልጽ ማድረስ ብቻ እንጂ ሌላ የለባቸዉም::

(36) 36. በየሕዝቡም ሁሉ ውስጥ አላህን ተገዙ ጣዖትን ራቁ በማለት የሚያስተምር መልዕክተኛን ልከናል:: ከእነርሱም ውስጥ አላህ ያቀናው አለ:: ከእነርሱም ውስጥ በእርሱ ላይ ጥመት የተረጋገጠበት አለ:: እናም በምድር ላይ ሂዱ:: የአስተባባዮችም መጨረሻ እንዴት እንደ ነበር ተመልከቱ::

(37) 37. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በመቅናታቸው ላይ ብትጓጓ (ምንም ልታደርግ አትችልም):: ምክንያቱም አላህ የሚያጠመውን አያቀናዉምና:: ለእነርሱም ከረዳቶች ምንም የላቸዉም::

(38) 38. ጥብቅ መሐሎቻቸውንም «አላህ የሚሞትን ሰው አያስነሳም።» ሲሉ በአላህ ስም ማሉ:: አባባላቸው ሐሰት ነው። ያስነሳቸዋል:: በእርሱ ላይ ቃል ኪዳን ገብቷል:: አረጋግጧልም:: ግን አብዛኞቹ ሰዎች አያውቁም::

(39) 39. የሚቀሰቅሳቸዉም ለእነርሱ ያንን የሚለያዩበትን ሊገልጽላቸውና እነዚያ የካዱትም እነርሱ ውሸታሞች የነበሩ መሆናቸውን እንዲያውቁ ነው::

(40) 40. ለማንኛዉም ነገር መሆኑን በፈለግን ጊዜ ቃላችን ለእርሱ "ሁን" ማለት ብቻ ነው:: ወዲያዉም ይሆናል::

(41) 41. እነዚያም ከተበደሉ በኋላ በአላህ መንገድ ላይ የተሰደዱ በቅርቢቱ ዓለም መልካሚቱን አገር (መዲናን) እናሰፍራቸዋለን:: የመጨረሻይቱም ዓለም ምንዳ ታላቅ ነው:: (ከሓዲያን) ቢያውቁ ኖሮ (በተከተሏቸው ነበር)::

(42) 42. እነርሱ እነዚያ የታገሡና በጌታቸዉም ላይ የሚጠጉ ናቸው::

(43) 43. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ካንተም በፊት ወደ እነርሱ ወሕይን የምናወርድላቸውን ሰዎችን እንጂ ሌላን አልላክንም:: (ሰዎች ሆይ! ) የማታውቁም ከሆናችሁ የዕውቀትን ባለቤቶችን ጠይቁ::

(44) 44. በግልጽ ማስረጃዎችና በመጽሐፍ ላክናቸው። ለሰዎችም ወደ እነርሱ የተወረደላቸውን ፍች ትገልጽላቸውና ያስተነትኑም ዘንድ ወደ አንተ ቁርኣንን አወረድን::

(45) 45. እነዚያን መጥፎዎችን የዶለቱ ሰዎች አላህ በእነርሱ ምድርን የሚያስዉጣቸው ወይም ከማያውቁት ሥፍራ ቅጣት የሚመጣባቸው መሆኑን ተማመኑን? አይፈሩምን?

(46) 46. ወይም ከአገር ወደ አገር በሚዛወሩበት ጊዜ በእንቅስቃሴ ላይ እያሉ የሚይዛቸው መሆኑን አይፈሩምን? እነርሱም አሸናፊዎች አይደሉም::

(47) 47. ወይም ቀስ በቀስ በማጉደል ላይ የሚይዛቸው መሆኑን ተማመኑን? አይፈሩምን? ጌታችሁም ሩሕሩህና አዛኝ ነው::

(48) 48. ወደዚያ ከማንኛዉም ነገር አላህ ወደ ፈጠረው ጥላዎቹ እነርሱም የተዋረዱ ሲሆኑ ለአላህ ሰጋጆች ሆነው ከቀኝ እና ከግራዎች ወደ ሚዛወሩት አላዩምን?

(49) 49. በሰማያትና በምድር ያለው ተንቀሳቃሽ ሁሉ መላዕክትም ለአላህ ብቻ ይሰግዳሉ:: እነርሱም አይኮሩም::

(50) 50. ጌታቸውን ከበላያቸው ሲሆን ይፈሩታል:: የታዘዙትንም ሁሉ ይሰራሉ (ይፈጽማሉ):: {1}
{1} አዚህ የንባብ ሱጁድ (ሱጁድ አትላዋ) ይደረጋል።

(51) 51. አላህም አለ: «ሁለት አማልክት አትያዙ እርሱ አንድ አምላክ ብቻ ነው:: እኔን ብቻ ፍሩኝ።»

(52) 52. በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የእርሱ ብቻ ነው:: አምልኮም ዘወትር ለርሱ ብቻ ነው:: ከአላህ ሌላ ያለን ትፈራላችሁን?

(53) 53. ማንኛዉም በናንተ ላይ ያለው ጸጋ ከአላህ ብቻ ነው። ከዚያም ችግር በደረሰባችሁ ጊዜ ወደ እርሱ ብቻ ትጮሀላችሁ።

(54) 54. ከዚያም ከናንተ ላይ ችግርን ባነሳላችሁ ጊዜ ከናንተ የሆኑ ቡድኖች ወዲያውኑ በጌታችሁ ጣዖትን ያጋራሉ::

(55) 55. የሚያጋሩትም በሰጠናቸው ሊክዱ ነው:: ተጠቀሙም ወደፊትም የሚደርስባቸውን ታውቃላችሁ::

(56) 56. ለማያውቁት ጣዖታትም ከሰጠናቸው ሲሳይ ድርሻን ያደርጋሉ:: በአላህ እምላለሁ ትቀጣጥፉት ከነበራችሁት ሁሉ በእርግጥ ትጠየቃላችሁ::

(57) 57. ለአላህ ሴቶች ልጆችን ያደርጋሉ። ጥራት ይገባው። ለእነርሱ ግን የሚፈልጉትን ያደርጋሉ።

(58) 58. ከመሀከላቸው አንዱ በሴት ልጅ (መወለድ) በተበሰረ ጊዜ እርሱ የተቆጨ ሆኖ ፊቱ ጠቁሮ ቅስሙ ይሰበራል።

(59) 59. ከተበሰረበት ነገር መጥፎነት በውርደት ላይ ሆኖም ቢሆን ይያዘውን? ወይስ በአፈር ውስጥ ይደብቀውን? በማለት እያምታታ ከሰዎች ይደበቃል:: የሚፈርዱት ፍርድ ምንኛ ከፋ!

(60) 60. ለእነዚያ በመጨረሻይቱ ዓለም ለማያምኑት ሰዎች ሁሉ መጥፎ መገለጫ አላቸው:: ለአላህ ግን ታላቅ መገለጫ አለው:: እርሱም ሁሉን አሸናፊና ጥበበኛ ነው::

(61) 61. አላህም ሰዎችን በበደላቸው ሁሉ በቀጣቸው ኖሮ በምድር ላይ ከተንቀሳቃሽ ምንንም ባላስቀረ ነበር:: ግን እስከተወሰነ ጊዜ ድረስ ያቆያቸዋል:: ጊዜያቸዉም በመጣ ወቅት አንዲትን ሰዓት አይዘገዩም፤ አይቀድሙም።

(62) 62. ለአላህም የሚጠሉትን ነገር ያደርጋሉ:: ለእነርሱም መልካሚቱ (ሀገር) እንዳለቻቸው በምላሶቻቸው ውሸትን ይናገራሉ:: ለእነርሱም እሳት ያለቻቸው መሆናቸውና እነርሱም ወደ እርሷ በቅድሚያ የሚነዱ መሆናቸው ጥርጥር የለበትም::

(63) 63. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በአላህ እንምላለን ካንተ በፊት ወደ ነበሩት ሕዝቦች በእርግጥ ብዙ መልዕክተኞችን ልከናል:: ሰይጣንም ለእነርሱ ስራዎቻቸውን ሸለመላቸው:: ረዳታቸው ዛሬም እርሱ ነው:: ለእነርሱም ኋላ አሳማሚ ቅጣት አላቸው::

(64) 64. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ያንን በእርሱ የተለያዩበትን ለእነርሱ ልታብራራላቸውና ለሚያምኑትም ህዝቦች መሪና እዝነት ሊሆን እንጂ ባንተ ላይ መፅሀፉን አላወረድንም።

(65) 65. አላህ ከሰማይ ውሃን አወረደ:: በእርሱም ምድርን ከሞተች በኋላ ህያው አደረገ:: በዚህ ውስጥ ለሚሰሙ ህዝቦች በእርግጥ ተዓምር አለ::

(66) 66. (ሰዎች ሆይ!) ለእናንተ በግመል በከብት በፍየል አፈጣጠር አያሌ ምክር ሰጪ ትምህርት አለላችሁ:: በሆዶች ውስጥ ካለው ከፈርስና ከደም መካከል ጥሩ ወተትን ለጠጪዎች ጣፋጭ ሲሆን እናጠጣችኋለን::

(67) 67. ከዘንባባዎች ከወይኖችም ፍሬዎች እንመግባችኋለን፤ ከእርሱ ጠጅንና መልካም ምግብንም ትሰራላችሁ (ታዘጋጃላችሁ):: በዚህም ውስጥ ለሚያስቡ ህዝቦች በእርግጥ ተዓምር አለ::

(68) 68. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህም ወደ ንብ እንዲህ ሲል (አስታወቀ) አስተማረ፡ «ከተራራዎች ከዛፍና ሰዎች ከሚሠሩት ቀፎ ቤቶችን ያዢ::

(69) 69. «ከዚያም ከፍሬዎች ሁሉ ብይ የጌታሽንም መንገዶች ለአንቺ የተገሩ ሲሆኑ ግቢ።» ከሆዶቿ መልኮቹ የተለያዩ መጠጥ ይወጣል:: በእርሱ ውስጥ ለሰዎች ፍቱን መድሀኒት አለበት። በዚህ ውስጥ ለሚያስተነትኑ ህዝቦች ተዓምር አለበት::

(70) 70. አላህም ፈጠራችሁ ከዚያ ይገድላችኋል:: ከናንተም መካከል ከእውቀት በኋላ ምንንም ነገር የማያውቅ ወደሚሆንበት የጃጀ እድሜ የሚመለስም ሰው አለ:: አላህ ሁሉን አዋቂ፤ በሁሉም ነገር ላይ ቻይም ነው።

(71) 71. አላህ ከፊላችሁን በከፊሉ ላይ በሲሳይ አበለጠ:: እነዚያም በላጭ የተደረጉት ሲሳያቸውን እጆቻቸው በያዟቸው ባሮች ላይ እነርሱ በእርሱ ይስተካከሉ ዘንድ መላሾች አይደሉም:: ታዲያ በአላህ ጸጋ ለእርሱ ተጋሪ በማድረግ ይክዳሉን?

(72) 72. አላህ ከነፍሶቻችሁ (ከጎሳዎቻችሁ) ለእናንተ ሚስቶችን አደረገ (የትዳር አጋሮችን ፈጠረ)፤ ለእናንተም ከሚስቶቻችሁ ወንዶች ልጆችን የልጅ ልጆችንም አደረገላችሁ:: ከመልካሞችም ጸጋዎች ሰጣችሁ:: ታዲያ በውሸት በጣኦት አምነው በአላህ ጸጋ ይክዳሉን?

(73) 73. ከአላህም ሌላ ከሰማያትና ከምድር ምንንም ሲሳይ የማይሰጧቸውንና ምንንም የማይችሉትን እነርሱ ያመልካሉን::

(74) 74. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ለአላህ አምሳያዎችን አታድርጉ:: አላህ ያውቃል፤ እናንተ ግን አታውቁም::

(75) 75. በምንም ላይ የማይችል ሆኖ በይዞታ (አለቃ ያለበት) የሆነውን ባሪያና መልካም ሲሳይን ሰጥተነው እርሱም ከእርሱ ከሰጠነው በሚስጥርና በግልጽ የሚለግሰውን ነፃ ሰው አላህ ለጣኦትና ለእርሱ ምሳሌ አደረገ:: ሁለቱ ይስተካከላሉን? ምስጋና ሁሉ ለአላህ ይሁን:: በእውነቱ አብዛኞቻቸው አያውቁም::

(76) 76. አላህ ሁለትን ወንዶች (ለከሓዲያንና ለአማኞች) ምሳሌ አደረገ:: አንደኛቸው በምንም ነገር ላይ የማይችል ዲዳ ነው:: እርሱም በጌታው ላይ ሸክም ነው:: ወደ የትም ቢያዞረው ደግ ነገር አያመጣም:: እርሱና ያ በቀጥተኛው መንገድ ላይ ሆኖ በማስተካከል (ፍትህ) የሚያዘው ሰው ይስተካከላሉን?

(77) 77. በሰማያትና በምድር ያለው ሩቅ ምስጢር የአላህ ብቻ ነው:: የሰዓቲቱም ነገር መምጣቷ እንደ ዓይን ቅጽበት እንጂ አይደለም:: ወይም ይበልጥ የቀረበ ነው:: አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነውና::

(78) 78. አላህ ከእናቶቻችሁ ሆዶች ምንም የማታውቁ ሆናችሁ አወጣችሁ:: ታመሰግኑ ዘንድም ለእናንተ መስሚያንና ማያዎችን ልቦችንም አደረገላችሁ (ፈጠረላችሁ)::

(79) 79. ወደ በራሪዎችም በሰማይ አየር ውስጥ ለመብረር የተገሩ ሲሆኑ ከመውደቅ አላህ እንጂ ሌላ የማይዛቸው መሆናቸውን አይመለከቱምን? በዚህ ውስጥ ለሚያምኑ ህዝቦች ሁሉ አያሌ ተዓምራት አሉ::

(80) 80. አላህም ከቤቶቻችሁ ለእናንተ መርጊያን (ማረፊያን) አደረገላችሁ (ፈጠረላችሁ):: ከእንስሳዎችም ቆዳዎችን በጉዟችሁ ቀንም ሆነ በመቀመጫችሁ ቀን የምታቀሏቸውን ቤቶች (ዳሶች) ለእናንተ ፈጠረላችሁ:: ከበጓ ሱፎች፣ ከግመሏም ጠጉሮች፣ ከፍየሏም ጠጉሮች የቤት እቃዎችን እስከ ጊዜም ድረስ መጠቃቀሚያን አደረገላችሁ።

(81) 81. አላህ ከፈጠረው ነገር ለእናንተ ጥላዎችን ፈጠረላችሁ:: ከጋራዎችም መከለያዎችን ፈጠረላችሁ:: ሐሩርንም ብርድንም የሚጠብቋችሁን ልብሶች፤ የጦራችሁንም አደጋ የሚጠብቋችሁን ጥሩሮች ፈጠረላችሁ:: ልክ እንደዚሁ ትሰልሙ ዘንድ ጸጋውን በእናንተ ላይ ይሞላል::

(82) 82. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከኢስላም ቢሸሹም ባንተ ላይ ያለብህ ግልጽ ማድረስ ብቻ ነው::

(83) 83. የአላህን ጸጋ ያውቃሉ:: ሆኖም ከዚያ ይክዷታል:: አብዛኞቻቸዉም ከሓዲያን ናቸው::

(84) 84. ከየህዝቡም ሁሉ መስካሪን የምንቀሰቅስበትን ቀን አስታውስ:: ከዚያ ለእነዚያ ለካዱት ንግግር አይፈቀድላቸዉም:: እነርሱም በወቀሳ አይታለፉም::

(85) 85. እነዚያ የበደሉ ሰዎች ቅጣትን ባዩ ጊዜ ለእነርሱ አይቃለልላቸዉም:: ጊዜም አይሰጣቸዉም::

(86) 86. እነዚያ በአላህ ያጋሩት ሰዎች ተጋሪዎቻቸውን ባዩ ጊዜ «ጌታችን ሆይ! እነዚህ ካንተ ሌላ እናመልካቸው የነበሩ ተጋሪዎቻችን ናቸው።» ይላሉ። አማልክቶችም «ውሸታሞች ናችሁ።» በማለት ቃሉን ወደ እነርሱው መልሰው ይወረውራሉ።

(87) 87. አጋሪዎቹ በዚያ ቀንም ታዛዥነታቸውን ወደ አላህ ያቀርባሉ:: ይቀጣጥፉት የነበሩትም ሁሉ ከእነርሱ ይጠፋባቸዋል::

(88) 88. እነዚያ በአላህ የካዱና ከአላህ መንገድ የከለከሉ ያጠፉ በነበሩት ምክንያት ቅጣትን በቅጣት ላይ ጨመርንባቸው::

(89) 89. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በየህዝቡ ሁሉ ውስጥ ከጎሳቸው በራሳቸው ላይ መስካሪን የምንቀሰቅስበትንና አንተንም በእነዚህ ሕዝቦች ላይ መስካሪ አድርገን የምናመጣብህን ቀን አስታውስ:: መጽሐፉንም ለሁሉም ነገር አብራሪ፤ መመሪያ፣ እዝነትና ለሙስሊሞች አብሳሪ ሆኖ ባንተ ላይ አወረድነው::

(90) 90. አላህ በማስተካከል (በፍትህ) ፤ በማሳመር (በመልካም ሥራ) እና ለዝምድና ባለቤት በመስጠትም ያዛል። ከአስከፊ (ጸያፍ ነገር) ከማመንዘር፤ ከሚጠላ ነገር ሁሉ ከመበደልም ይከለክላል:: ትገነዘቡ ዘንድ ይገሥጻችኋል::

(91) 91. (ሙስሊሞች ሆይ!) ቃል ኪዳን በገባችሁ ጊዜ በአላህ ቃል ኪዳን ሙሉ:: መሓሎቻችሁንም ከአጠነከራችኋት በኋላና አላህን በእናንተ ላይ መስካሪ ያደረጋችሁ ስትሆኑ አታፍርሱ:: አላህ የምትሠሩትን ሁሉ ያውቃልና::

(92) 92. ቃል ኪዳናችሁን በማፍረስ አንዲቱ ሕዝብ ከሌላይቱ ሕዝብ የበዛች ለመሆንዋ በመካከላችሁ መሓሎቻችሁን ለክዳት መግቢያ አድርጋችሁ የምትይዙ ስትሆኑ እንደዚያች ፈትሏን ከጠነከረ በኋላ ትርትሮች አድርጋ እንዳፈረሰችው ሴት አትሁኑ:: አላህ በእርሱ ይሞክራችኋል፤ በትንሣኤ ቀንም ትለያዩበት የነበራችሁትን ነገር በእርግጥ ያብራራላችኋል::

(93) 93. አላህ በፈለገ ኖሮ አንዲት ሕዝብ ባደረጋችሁ ነበር:: ግን አላህ የሚሻውን ሰው ያጠማል:: የሚሻውን ሰው ያቀናል:: ትሠሩት ከነበራችሁት ሁሉ በእርግጥ ትጠየቃላችሁ::

(94) 94. ጫማዎች ከተደላደሉ በኋላ እንዳያንዳልጡ ከአላህ መንገድ በመከልከላችሁ ምክንያት ቅጣትንም እንዳትቀምሱ መሓሎቻችሁን በመካከላችሁ ለክዳት መግቢያ አታድርጉት:: ለእናንተም ያን ጊዜ ታላቅ ቅጣት አላችሁ::

(95) 95. በአላህ ቃል ኪዳን ጥቂትን ዋጋ አትግዙ። የምታውቁ ብትሆኑ አላህ ዘንድ ያለው ምንዳ እርሱ ለእናንተ በላጭ ነውና::

(96) 96. እናንተ ዘንድ ያለው ሁሉ ያልቃል:: አላህ ዘንድ ያለው ግን ለዘለዓለም ቀሪ ነው (አያልቅም):: እነዚያንም የታገሡትን ይሠሩት በነበሩት በመልካሙ ምንዳቸውን እንመነዳቸዋለን::

(97) 97. ከወንድም ይሁን ከሴት እርሱ አማኝ ሆኖ በጎን የሠራ ሁሉ መልካም ኑሮን እናኖረዋለን:: ይሠሩት ከነበሩት ነገር በመልካሙም ምንዳቸውን እንመነዳቸዋለን::

(98) 98. ቁርኣንንም ለማንበብ ባሰብክ ጊዜ እርጉም ከሆነው ሰይጣን በአላህ ተጠበቅ::

(99) 99. እርሱ በእነዚያ በትክክል ባመኑትና በጌታቸው ላይ በሚጠጉት ላይ ለእርሱ ሥልጣን የለዉምና::

(100) 100. ሥልጣኑ በእነዚያ በሚታዘዙት ላይና በእነዚያም እነርሱ በእርሱ ምክንያት አጋሪዎች በሆኑት ላይ ብቻ ነው::

(101) 101. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በአንቀጽም ስፍራ ሌላ አንቀጽን በለወጥን ጊዜ አላህም የሚያወርደውን ነገር አዋቂ ነው:: «አንተ ቀጣፊ እንጂ ሌላ አይደለህም።» ይላሉ:: በእውነቱ አብዛኞቻቸው አያውቁም::

(102) 102. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «እነዚያን ያመኑትን ሰዎች ለማረጋጋት ሙስሊሞቹንም ለመምራትና ለማብሰር ቁርኣንን ጂብሪል እውነተኛ ሲሆን ከጌታህ አወረደው።» በላቸው::

(103) 103. እነርሱም «እርሱን ቁርኣንን የሚያስተምረው ሰው ብቻ ነው።» ማለታቸውን በእርግጥ እናውቃለን:: የዚያ ወደ እርሱ የሚያስጠጉበት ሰው ቋንቋ ዐረበኛ ያልሆነ ዐጀምኛ ነው:: ይህ ቁርኣን ግን በግልጽ በዐረብኛ ቋንቋ የተነገረ ነው::

(104) 104. እነዚያን በአላህ አናቅጽ የማያምኑትን አላህ አይመራቸዉም:: ለእነርሱም አሳማሚ ቅጣት አለባቸው::

(105) 105. ውሸትን የሚቀጣጥፉት እነዚያ በአላህ አናቅጽ የማያምኑት ብቻ ናቸው:: እነዚያም ውሸታሞቹ እነርሱ ብቻ ናቸው::

(106) 106. ከእምነቱ በኋላ በአላህ የካደ ሰው ብርቱ ቅጣት አለው። ልቡ በእምነት የረካ ሆኖ በክሕደት ቃል ለመናገር የተገደደ ሰው ብቻ ሲቀር:: ግን ልባቸውን በክሕደት የከፈቱ ሰዎች ከአላህ ቁጣ አለባቸው:: ለእነርሱም ታላቅ ቅጣት አላቸው::

(107) 107. ይህ ቅጣት እነርሱ ቅርቢቱን ሕይወት ከመጨረሻይቱ በመምረጣቸው ምክንያትና አላህም ከሓዲያንን ሕዝቦች የማያቀና በመሆኑ ነው::

(108) 108. እነዚያ እነርሱ በልቦቻቸው፤ በዓይኖቻቸውና በጆሮቻቸዉም ላይ አላህ ያተመባቸው ናቸው:: እነዚያም ዝንጉዎቹ እነርሱ ብቻ ናቸው::

(109) 109. እነርሱ በመጨረሻይቱ ዓለም ከሳሪዎቹ እነርሱ ለመሆናቸው ጥርጥር የለም::

(110) 110. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከዚያም ጌታህ ለእነዚያ ከተፈተኑ በኋላ ለተሰደዱት ከዚያም ለታገሉትና ለታገሡት ሁሉ ጌታህም ከፈተናዋ በኋላ በእርግጥ መሐሪና አዛኝ ነው።

(111) 111. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ነፍስ ሁሉ ከራሷ ላይ የምትከራከር ሆና የምትመጣበትን ነፍስም ሁሉ የሠራችውን ዋጋ የምትቀበልበትን ቀን (አስታውስ):: እነርሱም ፈጹሞ አይበደሉም::

(112) 112. አላህ ጸጥተኛ የረካች ሲሳይዋ ሰፊ ሆኖ ከየስፍራው ይመጣላት የነበረችውንና ከዚያም በአላህ ጸጋዎች የካደችውን አላህም ይሠሩት በነበሩት ኃጢአት የረሀብንና የፍርሀትን ቅጣቶች ያቀመሳትን ከተማ ምሳሌ አደረገ::

(113) 113. ከእነርሱም ውስጥ የሆነ መልዕክተኛም በእርግጥ መጣላቸው:: አስተባበሉትም እነርሱም በዳዬች ሆነው ቅጣቱ ያዛቸው::

(114) 114. አላህም ከሰጣችሁ ሲሳይ የተፈቀደና ንጹሕ ሲሆን ብሉ:: የአላህንም ጸጋ እርሱን የምትገዙት ከሆናችሁ አመስግኑት::

(115) 115. በእናንተ ላይ እርም ያደረገው በክትን፣ ደምን፣ የአሳማን ሥጋ፣ ያንንም በሚታረድ ጊዜ በእርሱ ላይ ከአላህ ስም ሌላ የተወሳበትን ብቻ ነው:: አመጸኛና ወሰን አላፊም ሳይሆን ከእነዚህ አንዱን ለመብላት የተገደደ ሰው ይፈቀድለታል:: አላህ መሓሪና አዛኝ ነውና::

(116) 116. (ሰዎች ሆይ) በአላህ ላይ ውሸትን ልትቀጣጥፉ ምላሶቻችሁ በሚመጥኑት ውሸት «ይህ የተፈቀደ ነው፤ ይህ ደግሞ እርም ነው» አትበሉ:: እነዚያ በአላህ ላይ ውሸትን የሚቀጣጥፉ ክፍሎች በፍጹም አይድኑም::

(117) 117. ጥቂት መጣቀም ብቻ አለላቸው:: ለእነርሱም አሳማሚ ቅጣት አለባቸው::

(118) 118. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በእነዚያ አይሁድ በሆኑት ሰዎች ላይ ከአሁን በፊት ባንተ ላይ የተረክነውን ነገር እርም አድርገንባቸዋል:: እኛም አልበደልናቸዉም:: ግን ራሳቸው ነፍሶቻቸውን ይበድሉ ነበሩ::

(119) 119. ከዚያም ጌታህ ለእነዚያ በስህተት መጥፎን ለሠሩትና ከዚያም ከዚህ በኋላ ለተጸጸቱ ሥራቸውንም ላበጁ ጌታህ ከእርሷ በኋላ በእርግጥ መሓሪና አዛኝ ነው::

(120) 120. ኢብራሂም ለአላህ ታዛዥ፤ ወደ ቀጥተኛ ሃይማኖት ተዘንባይ ህዝብ ነበር:: ከአጋሪዎችም አልነበረም::

(121) 121. ለጸጋዎቹ አመስጋኝ ነበር:: መረጠው:: ወደ ቀጥተኛዉም መንገድ መራው::

(122) 122. በቅርቢቱም ዓለም በጎ ነገርን ሰጠነው:: እርሱም በመጨረሻይቱ ዓለም በእርግጥ ከመልካሞቹ ነው::

(123) 123. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከዚያም የኢብራሂምን ሃይማኖት ቀጥተኛ ሲሆን ተከተል:: ከአጋሪዎቹም አልነበረም ማለትን ወደ አንተ አወረድን::

(124) 124. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በቅዳሜ ቀን መስራት ክልክል የተደረገው በእነዚያ በእርሱ በተለያዩበት ሰዎች ላይ ብቻ ነው:: (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህም በትንሳኤ ቀን ይለያዩበት በነበሩት ነገር በመካከላቸው በእርግጥ ይፈርዳል::

(125) 125. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ወደ ጌታህ መንገድ በብልሃትና በመልካም ግሳጼ በለዘብተኛ ቃልም ሰዎችን ጥራ:: በዚያችም እርሷ መልካም በሆነችው ዘዴ ተከራከራቸው:: ጌታህ ከመንገዱ የተሳሳተውን ሰው አዋቂ ነው:: እንደዚሁም እርሱ ቅን የሆኑትን ሰዎች አዋቂ ነው::

(126) 126. (ሙስሊሞች ሆይ!) ብትበቀሉም በእርሱ በተቀጣችሁበት ብጤ ተበቀሉ:: ብትታገሱ ግን እርሱ ለታጋሾች በእርግጥ በላጭ ነው::

(127) 127. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ታገስ:: መታገስህ በአላህ ማስቻል ብቻ እንጂ አይደለም:: በእነርሱም ላይ ባያምኑ አትተክዝ:: ባንተ ላይ በሚመክሩት ተንኮልም በጭንቀት ውስጥ አትሁን::

(128) 128. አላህ ከእነዚያ እነርሱ ከሚፈሩትና ከእነዚያም እነርሱ ከመልካም ሠሪ ከሆኑት ሰዎች ጋር ነው::