(1) 1. አሊፍ፤ ላም፤ ሚም፤
(2) 2. አላህ ከእርሱ ሌላ ትክክለኛ አምላክ የለም:: አላህ ህያው፤ በራሱ የተብቃቃና የሁሉ ነገር አስተናባሪ (የፍጡራን ተንከባካቢ) ነው::
(3) 3. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አላህ ቁርኣንን ከእርሱ በፊት ያሉትን መጽሐፍት የሚያረጋግጥ ሲሆን ባንተ ላይ ከፋፍሎ በእውነት አወረደው። ከቁርኣን በፊትም ለሰዎች መሪ አድርጎ ተውራትንና ኢንጅልን አውርዷል።
(4) 4. ከቁርኣን በፊትም ለሰዎች መሪ አድርጎ ተውራትንና ኢንጅልን አውርዷል። (በእውነትና በውሸት መካከል መለያ የሆነውን) ፉርቃንንም አወረደ። እነዚያ በአላህ አናቅጽ የካዱ ሁሉ ብርቱ ቅጣት አለባቸው። አላህ ሁሉን አሸናፊ፤ አስተባባዮችን ተበቃይም ነውና።
(5) 5. አላህ በምድርም ሆነ በሰማይ ምንም ነገር አይሸሸግበትም።
(6) 6. በማህጸኖች ውስጥ እንደፈለገው አድርጎ የሚቀርፃችሁ እርሱው ነው። ከእርሱ ከአሸናፊዉና ከጥበበኛው ጌታ በስተቀር ሌላ ትክክለኛ አምላክ በፍጹም የለም።
(7) 7. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አላህ ያ ባንተ ላይ መጽሐፍን-(ቁርኣንን) ያወረደ ነው:: ከመጽሐፉም ውስጥ ግልጽ የሆኑ አናቅጽ አሉ:: እነርሱም የመጽሐፉ መሰረቶች ናቸው። ሌሎች ደግሞ አሻሚ ትርጉም ያላቸው አሉ:: እነዚያ በልቦቻቸው ውስጥ ጥመት ያለባቸው ሌሎችን ለማሳሳት በማሰብና ትርጉሙን በሻቸው ለመለወጥ ሲሉ አሻሚ ትርጉም (ተመሳሳይነት) ያሏቸውን አናቅጽ ብቻ ይከታተላሉ። ትክክለኛ ትርጉማቸውን አላህ ብቻ እንጂ ሌላ ማንም አያውቀዉም:: እነዚያ በእውቀት የጠለቁት ግን «በእርሱ አምነናል። ሁሉም ከጌታችን ዘንድ ነው።» ይላሉ። የአእምሮ ባለቤቶች እንጂ አይገሰጽም።
(8) 8. (እነርሱም የሚሉ ናቸው:) «ጌታችን ሆይ! ቅኑን መንገድ ከመራኸን በኋላ ልቦቻችንን ወደ መጥፎ አታዘንብልብን:: ካንተ ዘንድ የሆነን ችሮታ ስጠን:: አንተ በጣም ለጋስ ነህና።
(9) 9. «ጌታችን ሆይ! አንተ በዚያ ለመምጣቱ ጥርጥር በሌለበት ቀን ሰውን ሁሉ ሰብሳቢ ነህ:: ምን ጊዜም አላህ ቀጠሮን አያፈርስምና»::
(10) 10. እነዚያ የካዱትን ገንዘቦቻቸውና ልጆቻቸው ከአላህ (ቅጣት) አያስጥሏቸዉም። እነዚያም እነርሱ የእሳት ማገዶዎች ናቸው።
(11) 11. ምሳሊያቸው ልክ እንደ ፈርዖን ቤተሰቦችና እንደነዚያ ከበፊታቸዉም እንደነበሩት ሕዝቦች ልማድ ነው:: በአናቅጻችን አስተባበሉ:: እናም አላህ በኃጢአቶቻቸው ቀጣቸው:: አላህ ቅጣተ ብርቱ ነውና::
(12) 12. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ለእነዚያ በአላህ ለካዱ ሰዎች «በቅርብ ጊዜ ትሸነፋላችሁ:: ከዚያም በገሀነም ትሰበሰባላችሁ:: ምንጣፊቱም (ገሀነም) ምን ትከፋ!» በላቸው::
(13) 13. በእነዚያ (የበድር) ቀን በተጋጠሙት ሁለት ቡድኖች ለእናንተ ብዙ ተዓምራት አሉ:: አንደኛዋ ቡድን በአላህ መንገድ ትጋደላለች:: ሌላይቱ ቡድን ደግሞ ከሓዲ ናት። በዓይን አስተያየት እጥፋቸው ሆነው ያዩዋቸዋል (በቁጥር የነርሱ እጥፍ ሁነው በአይናቸው ተመለከቷቸው)። አላህ በእርዳታው የሚሻውን ሁሉ ያበረታልና። በዚህ ውስጥ ለማስተዋል ባለቤቶች ሁሉ በእርግጥ መገሰጫ አለበት::
(14) 14. ከሴቶች፣ ከወንዶች ልጆች፣ ከወርቅ፣ ከብር፣ ከተከማቹ ገንዘቦች፣ ከተሰማሩ ፈረሶች፣ ከግመል ከከብትና ከፍየል፣ ከአዝመራም የሆኑ ፍላጎቶችን መውደድ ለሰዎች ተሸለመላቸው (ሰዎች ዘንድ የተወደዱ ተደረገላቸው)። ይህ ሁሉ የቅርቢቱ ሕይወት መጠቃቀሚያ ብቻ ነው:: አላህ ግን እርሱ ዘንድ መልካም የሆነ መመለሻ (ገነት) አለው::
(15) 15. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «ከዚህ ከተዋበላችሁ ጉዳይ የሚበልጥን ልንገራችሁን? እርሱም ለእነዚያ አላህን ለሚፈሩ ሁሉ በጌታቸው ዘንድ በስራቸው ወንዞች የሚፈሱባቸው ገነቶች በውስጧ ሁልጊዜ ነዋሪዎች ሲሆኑ ንጹህ ሚስቶችና ከአላህ የሆነ ውዴታም አለላቸው:: አላህም ባርያዎቹን ተመልካች ነው።» በላቸው።
(16) 16. (እነርሱም) እነዚያ «ጌታችን ሆይ! እኛ ባንተ አመንን። ኃጢአቶቻችንን ማርልን። የእሳትን ቅጣት ጠብቀን።» የሚሉ ናቸው።
(17) 17. እነርሱም ታጋሾች፤ እውነተኞች፤ ታዛዦች፤ ለጋሾችና በሌሊት መጨረሻዎች ሰዓታት ላይ አላህን ምህረት የሚለምኑ ናቸው::
(18) 18. አላህ (በማስተካከል) ቀጥ ያለ ሲሆን ከእርሱ በስተቀር ሌላ ትክክለኛ አምላክ የሌለ መሆኑን መሰከረ። መላዕክትና የእውቀት ባለቤቶችም መሰከሩ። ከእርሱ በስተቀር ሌላ አምላክ የለም:: እርሱ ሁሉን አሸናፊውና ጥበበኛው ነው።
(19) 19. አላህ ዘንድ የተወደደው ሀይማኖት ኢስላም ብቻ ነው:: እነዚያ መጽሐፉን የተሰጡ ሰዎች በመካከላቸው ባለው ምቀኝነት እውቀቱ ከመጣላቸው በኋላ እንጂ አልተለያዩም:: በአላህ አናቅጽ ለሚክድ ሁሉ አላህ ምርመራው ፈጣን ነው።
(20) 20. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ቢከራከሩህም «ፊቴን ለአላህ ብቻ ሰጠሁ። የተከተሉኝም እንደዚሁ ለአላህ ብቻ ሰጡ።» በላቸው:: ለእነዚያም መጽሐፉን ለተሰጡ ሰዎችና ለመሃይማኑ (ዐረቦች)፡- «ሰለማችሁን?» በላቸው:: ቢሰልሙም በእርግጥ ወደቀናው መንገድ ተመሩ:: እምቢ ቢሉ ግን ባንተ ላይ ያለብህ መልዕክትን ማድረስ ብቻ ነው:: አላህ ባሮቹን ተመልካች ነውና።
(21) 21. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እነዚያ በአላህ አናቅጽ የሚክዱ፤ ነብያትንም ያለ አግባብ የሚገድሉ፤ ከሰዎችም ውስጥ እነዚያን በትክክለኛነት የሚያዙትን የሚገድሉ በአሳማሚ ቅጣት አብስራቸው::
(22) 22. እነዚያ በቅርቢቱም ሆን በመጨረሻይቱ ዓለም ስራዎቻቸው የተበላሹ ናቸው:: ለእነርሱም ምንም ረዳቶች የሏቸዉም::
(23) 23. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ወደ እነዚያ ከመጽሐፍ (ትምህርት) ድረሻን ወደ ተሰጡት ሰዎች አላየህምን? ወደ አላህ መጽሐፍ በመካከላቸው ይፈርድ ዘንድ ይጠራሉ:: ከዚያ ከእነርሱ ገሚሶቹ (ከፊሎቹ) እውነቱን ወደ ጎን የተው ሆነው ይሸሻሉ::
(24) 24. ይህም እነርሱ «የገሀነም እሳት የተቆጠሩ ቀናትን ብቻ እንጂ አትነካንም።» በማለታቸው ነው:: በሀይማኖታቸዉም ይቀጣጥፉት የነበሩት ነገር አታለላቸው::
(25) 25. በእርሱ መምጣት ጥርጥር የሌለበት በሆነው ቀን በሰበሰብናቸውና ነፍስ ሁሉ የሰራችውን ስራ በተሞላች ጊዜ እንዴት ይሆናሉ? እነርሱም ቅንጣትንም አይበደሉም::
(26) 26. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ! እንዲህ) በል: «የንግስና ባለቤት የሆንከው አላህ ሆይ! ለምትሻው ሰው ንግስናን ትሰጣለህ:: ከምትሻዉም ሰው ንግስናን ትገፋለህ:: የምትሻውንም ሰው ታልቃለህ:: የምትሻውንም ሰው ደግሞ ታዋርዳለህ:: መልካም ነገር ሁሉ በእጅህ ብቻ ነው:: አንተ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነህና።
(27) 27. «ሌሊቱን በቀን ውስጥ ታስገባለህ:: ቀኑንም በሌሊት ውስጥ ታስገባለህ:: ሕያውንም ከሙት ታወጣለህ:: ሙታንንም ከሕያው ታወጣለህ፤ ለምትሻውም ሁሉ መጠን የለሽ ሲሳይ ትሰጣለህ።» በል።
(28) 28. አማኞች ከሓዲያንን ከአማኞች ሌላ ረዳቶች አድርገው አይያዙ። ይህንን የሚሰራ ከአላህ ሀይማኖት በምንም ውስጥ አይደለም:: ከእነርሱ መጠበቅን ብትጠበቁ እንጂ:: አላህ ከእርሱው ያስጠነቅቃችኋል:: መመለሻም ወደ አላህ ብቻ ነውና።
(29) 29. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «በልቦቻችሁ ውስጥ ያለውን ሁሉ ብትደብቁት ወይም ብትገልጹት አላህ ያውቀዋል:: በሰማያት ውስጥ ያለውንና በምድር ውስጥ ያለውን ሁሉ ያውቃል:: አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው።» በል።
(30) 30. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ያን ነፍስ ሁሉ ከመልካም ነገር የሰራችውን የቀረበ ሆኖ የምታገኝበትን ቀን (አስታውስ):: ከመጥፎም የሰራችው በእርሷና በኃጢአቱ መካከል በጣም የሰፋ ርቀት ቢኖር ትመኛለች:: አላህ እራሱን ያስጠነቅቃችኋል:: አላህ ለባሮቹ ሩህሩህ ነውና::
(31) 31. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!)፡- «አላህን የምትወዱ እንደሆናችሁ እኔን ተከተሉኝ:: አላህም ይወዳችኋል፤ ኃጢአቶቻችሁንም ለእናንተ ይምራልና:: አላህ መሀሪና አዛኝ ነውና።» በላቸው።
(32) 32. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!)፡- «አላህንና መልዕክተኛውን ታዘዙ። ብሸሹም አላህ ከሓዲያንን አይወድም» በላቸው።
(33) 33. አላህ (ነብዩ) አደምን፣(ነብዩ) ኑህን፣(የነብዩ) ኢብራሂምን ቤተሰብ እና የዒምራንን ቤተሰብ ከአለማት አበለጣቸው (መረጣቸው)።
(34) 34. እኒህን ቤተሰቦች ከፊሉ ከከፊሉ የሆነ ዝርያ አድርጎ መረጣቸው። አላህ ሁሉን ሰሚና ሁሉንም አዋቂ ነው።
(35) 35. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) የዒምራን ባለቤት (ሀና) «ጌታዬ ሆይ! በሆዴ ውስጥ ያለውን ጽንስ ከሥራ ነፃ የተደረገ ሲሆን ላንተ አገልግሎት ይውል ዘንድ ተሳልኩ:: እናም ተቀበለኝ:: አንተ ሰሚና አዋቂ ነህና።» ባለች ጊዜ የሆነውን አስታውሱ በላቸው።
(36) 36. በወለደቻትም ጊዜ፡- «ጌታዬ ሆይ! ሴት ሆና ወለድኳት።» አለች። አላህ የወለደችውን ምንነት አዋቂ ነው:: የተመኘችው ወንድ እንደ ወለደቻት ሴት የሚሆን አልነበረም:: «መርየምም ብዬ ስም አወጣሁላት:: እኔም እርሷንና ዝርያዋን ከተረገመው ሰይጣን ተንኮል ባንተ እጠብቃቸዋለሁ።» አለች።
(37) 37. ጌታዋም በመልካም አቀባበል ተቀበላት:: በመልካም አስተዳደግም አፋፋት:: ከዚያም ዘከርያ አሳደጋት:: ዘከርያም ወደ ምኩራቧ በሷ ላይ በገባ ቁጥርም እርሷ ዘንድ ሲሳይን አገኘ:: «መርየም ሆይ! ይህ ለአንቺ ከየት ነው የሚመጣልሽ?» አላት። «እርሱ የሚመጣልኝ ከአላህ ዘንድ ነው:: አላህ እኮ ለሚሻው ሁሉ ሲሳዩን ያለ ሂሳብ ይሰጣል።» አለችው።
(38) 38. እዚያ ዘንድም ዘከርያ ጌታውን እንደዚህ በማለት ለመነ: «ጌታዬ ሆይ! ካንተ ዘንድ መልካም ዘርን ለእኔ ስጠኝ:: አንተ ጸሎትን ሰሚ ነህና» አለ።
(39) 39. እርሱም በዱዓ ማድረጊያ ክፍል ቆሞ ዱዓ ሲያደርግ መላዕክት:- «አላህ በየህያ: ከአላህ በሆነ ቃል የሚያረጋግጥ፣ በላጭ፣ ከሴት ጋር የማይገናኝ ድንግልና ከደጋጎቹም አንዱ ሲሆን ያበስርሃል።» በማለት መላዕክት ጠሩት።
(40) 40. ዘከርያም «ጌታዬ ሆይ! እኔ እርጅና የደረሰብኝ ሚስቴም መካን ስትሆን እንዴት ልጅ ይኖረኛል?» አለ። መልአኩም: «ልክ እንደዚሁ ነው። አላህ የሚሻውን ነገር ሁሉ ይሰራልና።» አለው።
(41) 41. ዘከርያም «ጌታዬ ሆይ! ለእዚህ ነገር ምልክትን አድርግልኝ።» አለ:: «ምልክትህ ሶስት ቀን በጥቅሻ እንጂ ሰዎችን አለማናገርህ ነው:: በዚያ ጊዜ ጌታህን በብዙ አውሳ:: በማታና በጠዋትም አወድሰው።» አለው።
(42) 42. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) መላእክትም ባሉ ጊዜ: «መርየም ሆይ! አላህ በእርግጥ መረጠሸ:: ከነውሮች ሁሉ አጸዳሸ:: ከዓለማት ሴቶችም መካከል መረጠሸ።
(43) 43. «መርየም ሆይ! ለጌታሽ ታዘዢ:: ስገጂም:: ከአጎንባሾች ጋርም ሁነሽ አጎንብሺ።» (ያለበትን ታሪክ ለህዝቦችህ አውሳ።)
(44) 44.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ይህ ታሪክ ወደ አንተ ከምናወርደው ከሩቅ ወሬ ነው:: መርየምን ማን እንደሚያሳድግ ብዕሮቻቸውን ለዕጣ በጣሉ ጊዜ አንተ እነርሱ ዘንድ አልነበርክም:: በሚከራከሩም ጊዜ እነርሱ ዘንድ አልነበርክም::
(45) 45. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) መላዕክትም «መርየም ሆይ! አላህ ከእርሱ በሆነው ቃል የሚፈጠር ስሙ አል መሲህ ዒሳ የመርየም ልጅ በሚባል፤ በዚህ ዓለምም ሆነ በመጨረሻው ዓለም የተከበረና ከባለሟሎቹ አንዱ በሆነ ልጅ ያበስርሻል። (ባላት ጊዜ እዚያ ቦታ አልነበርክም) ::
(46) 46. «እርሱም ገና በህፃንነቱ ካደገም በኋላ ሰዎችን ያነጋግራል:: ከመልካሞቹም አንዱ ነው።» (አላት)።
(47) 47. እርሷም «ጌታዬ ሆይ! ማንም ሰው በትዳርም ሆነ በዝሙት ሳይነካኝ እንዴት ልጅ ይኖረኛል?» አለች:: መልአኩ ጅብሪልም አላት: «እነደዚሁ ነው። አላህ የሚሻውን ሁሉ ይፈጥራል። የአንድን ነገር መሆን በፈለገ ጊዜ የሚለው ‹ሁን› ብቻ ነው። ወዲያውኑም ያ ነገር ይሆናል።
(48) 48. «ጽሕፈትንና ጥበብን፤ ተውራትንና ኢንጂልንም ያስተምረዋል።
(49) 49.«ወደ ኢስራኢል ልጆችም መልዕክተኛ ያደርገዋል። ይላልም: ›, ‹እኔ ከጌታዬ ዘንድ በተዐምር መጣሁላችሁ:: እኔ ለእናንተ ከጭቃ የወፍ ቅርጽ አይነት እፈጥራለሁ:: በእርሱም እተነፍስበታለሁ:: ከዚያም በአላህ ፈቃድ ወፍ ይሆናል:: እውር ሆኖ የተወለደንም ለምጸኛንም በአላህ ፈቃድ አድናለሁ:: ሙታንንም በአላህ ፍቃድ አስነሳለሁ:: የምትበሉትንና በየቤቶቻችሁ የምታደልቡትን ሁሉ እነግራችኋለሁ:: (መረጃዎችን አገናዝባችሁ) የምታምኑ እንደሆናችሁ ለእናንተ በዚህ ውስጥ ግልጽ ተዐምር አለበት።
(50) 50.«‹ከእኔ በፊት የነበረውን ተውራትን ያረጋገጥኩ ስሆን ያንም በእናንተ ላይ እርም የተደረገውን ነገር ከፊሉን ለእናንተ እፈቅድ ዘንድ መጣሁላችሁ:: ከጌታችሁም በሆነ ተዐምር መጣሁላችሁ:: አላህን ፍሩ:: እኔንም ታዘዙኝ።
(51) 51.«‹አላህ ጌታዬ የእናንተም ጌታችሁ ነው:: ስለዚህ በብቸኝነት ተገዙት:: ይህ ቀጥተኛው መንገድ ነው።› ይላቸዋል»
(52) 52. ዒሳ ከእነርሱ ክህደት በተሰማው ጊዜ፡- «ወደ አላህ የእኔ ረዳቶች የሚሆኑ እነማን ናቸው?» አለ:: ሀዋርያትም አሉ፡- «ዒሳ ሆይ! እኛ የአላህ ረዳቶች ነን:: በአላህ አምነናል:: ትክክለኛና ታዛዦች መሆናችንን መስክር።
(53) 53. («ጌታችን ሆይ! ባወረድከው አምነን መልዕክተኛውን ተከትለናል::( እኛንም ባንተ ብቸኛ አምላክነት በነብያት መልዕክተኛነት) ከመስካሪዎች ጋራ መዝግበን።» አሉ።
(54) 54.አይሁድም በዒሳ ላይ አደሙ:: አላህ ግን አድማቸውን አከሸፈባቸው። አላህ የአድመኞችን ሴራ በማክሸፍ ከሁሉ የበለጠ ነውና።
(55) 55. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አላህ ባለ ጊዜ (አስታውስ)፡- «ዒሳ ሆይ! እኔ ወሳጅህና ከምድር ወደ እኔ አንሽህ ነኝ:: ከነዚያም በእኔ ከካዱ ሰዎች (ተንኮል) አጥሪህ ነኝ። እነዚያ የተከተሉህንም እስከ ትንሳኤ ቀን ድረስ ከነዚያ ከካዱት በላይ አድራጊ ነኝ:: ከዚያ የሁላችሁም መመለሻችሁ ወደ እኔ ነው:: ያን ትለያዩበት በነበራችሁበት ነገርም በመካከላችሁ እፈርዳለሁ።
(56) 56.«እነዚያማ የካዱትን በቅርቢቱ ዓለምም ሆነ በመጨረሻይቱ ዓለም ብርቱ ቅጣትን እቀጣቸዋለሁ:: ለእነርሱም ምንም ረዳቶች የሏቸዉም»
(57) 57. እነዚያማ አምነው መልካም ስራዎችን የሰሩትን አላህ ምንዳቸውን ይሞላላቸዋል:: አላህም በዳዮችን አይወድምና።
(58) 58.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ይህ ተዓምራትና ጥበብን ከያዘው ተግሳጽ በአንተ ላይ የምናነበው ነው።
(59) 59. አላህ ዘንድ የዒሳ (ያለ አባት መፈጠሩ) ምሳሌው ልክ እንደ (ያለ አባትና ያለ እናት እንደተፈጠሩት አባታችን) አደም ቢጤ ነው:: አላህ ከአፈር ፈጠረውና ከዚያም «ሁን» አለው። ከዚያ ሰው ሆነ።
(60) 60.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እውነታው ከጌታህ ዘንድ የመጣልህ እውነት ነው። እናም ከተጠራጣሪዎች አትሁን።
(61) 61.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እውቀት ከመጣልህ በኋላ በእርሱ (በዒሳ) የተከራከሩህን «ኑ ልጆቻችንንና ልጆቻችሁን፣ ሴቶቻችንንና (ሚስቶቻችንና) ሴቶቻችሁን (ሚስቶቻችሁን)፣ ነፍሶቻችንንና ነፍሶቻችሁን እንጥራና ከዚያ አላህን እንለምን:: የአላህንም ቁጣ በውሸታሞች ላይ እናድርግ።» በላቸው።
(62) 62.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ይህ እውነተኛው ታሪክ ነው:: ትክክለኛ አምላክም ከአላህ በስተቀር የለም። አላህም አሸናፊውና ጥበበኛው አምላክ ነው።
(63) 63. (ከማመን) እምቢ ቢሉም (አጥፊዎቹ እነርሱ ናቸው።) አላህ አጥፊዎቹን (ከደህናዎቹ) ለይቶ አዋቂ ነው።
(64) 64.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «የመጽሐፉ ባለቤቶች ሆይ! በእኛና በእናንተ መካከል ትክክል ወደ ሆነችው ቃል ኑ። (እርሷም) ‹አላህን ብቻ እንጂ ሌላን ላንገዛ፤ በእርሱም ምንንም ላናጋራ፤ ከፊላችንም ከፊሉን ከአላህ ሌላ አማልክት አድርጎ ላይዝ› ነው።» በላቸው። (ሙስሊሞች ሆይ!) እምቢ ካሉም «እኛ ሙስሊሞች መሆናችንን መስክሩ።» በሏቸው።
(65) 65. እናንተ የመጽሐፉ ባለቤቶች ሆይ! በኢብራሂም (ዙሪያ) ለምን ትከራከራላችሁ? ተውራትና ኢንጂል ከእርሱ በኋላ እንጂ አልተወረዱ። ልብ አትሉምን?
(66) 66 እናንተ እነዚያ እውቀት ባላችሁ ነገር የተከራከራችሁ ናችሁ፡፡ ታዲያ እውቀት በሌላቸሁ ነገር ላይ ለምን ትከራከራላችሁ? አላህ ሁሉን ነገር ያውቃል። እናንተ ግን አታውቁም።
(67) 67. ኢብራሂም አይሁድም ሆነ ክርስቲያን አልነበረም:: ግን በቀጥተኛው ሃይማኖት ቀጥ ያለ ሙስሊም ነበር:: ከአጋሪዎችም አልነበረም፡፡
(68) 68.በኢብራሂም ይበልጥ ተገቢዎቹ እነዚያ የተከተሉት፤ ይህ ነብይ (ነብዩ ሙሐመድ) እና እነዚያ ያመኑት ብቻ ናቸው፡፡ አላህ የአማኞች ወዳጅ ነው፡፡
(69) 69. (ሙስሊሞች ሆይ!) ከመጽሐፉ ባለቤቶች የተወሰኑት ነፍሶቻቸውን እንጂ የማያሳስቱ ሲሆኑ እናንተን ሊያሳስቷችሁ ተመኙ:: እራሳቸውን እንጂ ማንንም አያሳሳስቱም፡፡ እነርሱ ግን ይህንን እውነታ አያውቁም።
(70) 70. እናንተ የመጽሐፍ ባለቤቶች ሆይ! እናንተ የምታውቁ ስትሆኑ በአላህ አናቅጽ ለምን ትክዳላችሁ?
(71) 71. እናንተ የመጽሐፉ ባለቤቶች ሆይ! እውነትን ከውሸት ጋር ለምን ትቀላቅላላችሁ? እውነቱንም የምታውቁ ስትሆኑ ለምን ትደብቃላችሁ?
(72) 72. ከመጽሐፉ ባለቤቶች የሆኑ ቡድኖችም በዚያ ባመኑት ላይ በተወረደው ቁርኣን «በቀኑ መጀመሪያ ላይ እመኑበትና በቀኑ መጨረሻ ላይ ካዱ። እነርሱ ሊመለሱ ይከጀላልና።» አሉ።
(73) 73. (አሉም) «ሃይማኖታችሁን ለተከተለ እንጂ አትመኑም።» (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «ትክክለኛው መመሪያ የአላህ መመሪያ ብቻ ነው። እናንተ ያገኛችሁትን እድል እንዳያገኙ ወይም በእርሱ ከጌታችሁ ፊት እንዳይሞግቷችሁ በመፍራት ነውን?» በላቸው። (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «ችሮታ በአላህ እጅ ብቻ ነው። ለሚፈልገውም ይሰጠዋል። አላህም ችሮታው ሰፊና ሁሉን አዋቂ ነው።» በላቸው።
(74) 74. በችሮታው የሚሻውን ይመርጣል:: አላህ የታላቅ ችሮታ ባለቤት ነውና::
(75) 75. ከመጽሐፉ ባለቤቶች መካከል በብዙ ገንዘብ ላይ ብታምነው ቅንጣት ሳያጎድል የሚመልስልህ አለ:: ከእነርሱም መካከል በአንድ ዲናር እንኳን ብታምነው ሁል ጊዜም እሱ ላይ የምትጠባበቅ ካልሆንክ በስተቀር የማይመልስልህም አለ:: ይህ «በመሀይማን ህዝቦች ላይ በምናደርገው በደል በእኛ ላይ የምንጠየቅበት መንገድ የለብንም።» ስለሚሉና እነርሱም እያወቁ በአላህ ላይ ውሸትን ስለሚናገሩ ነው።
(76) 76 ጉዳዩ እነርሱ እንዳሉት አይደለም (ተጠያቂነት አለባቸው)። ያ በቃል ኪዳኑ የሞላና የተጠነቀቀን ሁሉ አላህ ጥንቁቆችን ይወዳል።
(77) 77. እነዚያ በአላህ ቃል ኪዳንና በመሀላዎቻቸው ጥቂትን ዋጋን የሚለውጡ ሁሉ በመጨረሻይቱ ዓለም ምንም እድል የላቸዉም:: በትንሳኤም ቀን አላህ አያነጋግራቸዉም:: ወደ እነርሱም አይመለከትም:: አያጸዳቸዉምም:: ከቶውንም ለእነርሱ አሳማሚ ቅጣት አለባቸው::
(78) 78. ከእነርሱም መካከል ከመጽሐፉ ያልሆነን ነገር ከመጽሐፉ አካል መሆኑን እንድታስቡ በመጽሐፉ ምላሶቻቸውን የሚያጣምሙም አሉ:: እርሱ ከአላህ ዘንድ ያልመጣ (ያልወረደ) ሲሆን «ከአላህ ዘንድ የመጣ (የወረደ) ነው።» ይላሉ። የሚያውቁ ሲሆኑ በአላህ ላይ ውሸትን ይናገራሉ።
(79) 79. ለማንም ሰው አላህ መጽሐፍን፣ ጥበብንና ነብይነትን ሰጥቶት ከዚያ ለሰዎች «ከአላህ ሌላ ለእኔ ባሮች ሁኑ።» ሊል አይገባዉም:: ይልቁንም «መጽሐፉን የምታስተምሩና የምታጠኑ በነበራችሁበት በእውቀታችሁ ለራሳችሁ ተግባሪዎች ሁኑ።» ይላቸዋል።
(80) 80. መላዕክትንና ነብያትንም አማልክት አድርጋችሁ እንድትይዙ ሊያዛችሁ አይገባም:: (እናንተ) ሙስሊሞች ከሆናችሁ በኋላ በክህደት ያዛችኋልን?
(81) 81. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «መጽሐፍንና ጥበብን ሰጥቻችሁ ከዚያ ከናንተ ጋር ላለው መጽሀፍ የሚያረጋግጥ መልዕክተኛ ቢመጣላችሁ በእርሱ እንድታምኑበት እንድትረዱትም።» ሲል አላህ የነቢያትን ቃል ኪዳን በያዘ ጊዜ (የነበረውን ክስተት ለህዝቦችህ አስታውስ)። «አረጋገጣችሁን? በዚህስ ላይ ቃል ኪዳኔን ያዛችሁን?» አላቸው። እነርሱም «አዎ አረጋገጥን» አሉ። «እንግዲያውስ መስክሩ:: እኔም ከናንተ ጋር ከመስካሪዎቹ ነኝ።» አላቸው።
(82) 82. እናም ከዚህ በኋላ የሸሹ አመጸኞቹ እነርሱ ብቻ ናቸው።
(83) 83. በሰማያትና በምድር ያሉ ሁሉ በውድም ሆነ በግድ ለእርሱ የታዘዙና ወደ እርሱ የሚመለሱ ሲሆኑ (ከሓዲያን) ከአላህ ሃይማኖት ሌላን ይፈልጋሉን?
(84) 84. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «በአላህ አምነናል በእኛም ላይ በተወረደው በቁርኣን (በነብዩ) ኢብራሂም፣ (በነብዩ) ኢስማኢል፣ (በነብዩ) ኢስሀቅ፣ (በነብዩ) የዕቆብና በነገዶች ላይ በተወረደው፣ ለነብዩ ሙሳ ለነብዩ ዒሳና ለነብያትም ሁሉ ከጌታቸው በተሰጠው ሁሉ አምነናል:: በእነርሱ መካከል አንድንም አንለይም:: እኛ ለእርሱ ብቻ ታዛዦች ነን።» በል።
(85) 85. ከኢስላም ሌላ ሃይማኖትን የሚፈልግ ሁሉ ፈጽሞ ከእርሱ ተቀባይነት የለዉም:: እርሱም በመጨረሻይቱ ዓለም ከከሳሪዎቹ አንዱ ነው::
(86) 86. ከእምነታቸውና መልዕክተኛዉም እውነት መሆኑን ከመሰከሩ፤ የተብራሩ አናቅጽም ከመጡላቸው በኋላ የካዱ ሕዝቦችን አላህ እንዴት ያቀናል? አላህ በዳዮችን ሕዝቦች አያቀናምና።
(87) 87. እነዚያን መሰሎች ቅጣታቸው የአላህ፣ የመላዕክትና የሰዎች ሁሉ እርግማን በእነርሱ ላይ መውረዱ ነው።
(88) 88. በውስጧ ዘወታሪዎች ሲሆኑ ቅጣቱም ከእነርሱ ላይ አይቃለልላቸዉም:: ጊዜም አይሰጡም::
(89) 89. እነዚያ ከዚያ በኋላ ንስሀ የገቡና ስራቸውን ያሳመሩ ሁሉ ሲቀሩ፤ (አላህ እነዚህንማ ይምራቸዋል።) አላህ መሀሪና አዛኝ ነውና::
(90) 90. እነዚያ ከእምነታቸው በኋላ የካዱና ከዚያ ክህደትን በክህደት ላይ የጨመሩ ንሰሃቸው ፈጽሞ ተቀባይነት የለዉም:: የተሳሳቱ ማለት እነርሱው ናቸው::
(91) 91. እነዚያ የካዱና በክህደታቸው ላይ እንዳሉ የሞቱ፤ ከእነርሱ አንዳቸው ምድርን የሞላ ወርቅ ቤዛ ቢያቀርብም እንኳ ፈጽሞ ተቀባይነት አያገኝም:: እነዚያ ለእነርሱ የሚያሰቃይ ቅጣት አለባቸው:: ለእነርሱም (ከዚህ ቅጣት) የሚያድኗቸው ምንም ረዳቶች የሏቸዉም::
(92) 92. (ሙስሊሞች ሆይ!) ከምትወዱት ነገር እስከምትለግሱ ድረስ የበጎ ስራን ዋጋ (ገነትን) አታገኙም:: ከምንም ነገር ብትለግሱም አላህ ያውቀዋል::
(93) 93. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ተውራት ከመውረዱ በፊት ኢስራኢል በራሱ ላይ እርም ካደረገው ነገር በስተቀር ምግብ ሁሉ ለኢስራኢል ልጆች የተፈቀደ ነበር። «እውነተኞች ከሆናችሁ እስኪ ተውራትን አምጡና አንብቡት።» በላቸው።
(94) 94. ከዚህ በኋላ በአላህ ላይ ውሸትን የቀጣጠፉ ሰዎች እነዚያ እነርሱ ብቻ በዳዮች (በደለኞች) ናቸው::
(95) 95. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «አላህ እውነትን ተናገረ። (ትክክለኛ የኢብራሂም ወዳጆች ከሆናችሁ) የኢብራሂምንም መንገድ ቀጥተኛ ሲሆን ተከተሉ። ከአጋሪዎችም አልነበረም።» በላቸው።
(96) 96. ለሰዎች (ማምለኪያ ይሆን ዘንድ በመሬት ላይ) በመጀመሪያ የተሰራው ቤት ብሩክና ለዓለማት ሁሉ መመሪያ ሲሆን ያ በበካህ (በመካ) ያለው ቤት (ካዕባ) ነው።
(97) 97. በውስጡ ግልጽ የሆኑ ተዐምራት አሉበት:: የኢብራሂምም መቆሚያ (የነበረው በዉስጡ አለ::) ወደ እርሱ የገባም ሁሉ ሰላም ይሆናል። በሰዎች ላይ ወደ እርሱ የመሄድን ጣጣ በቻለ ሁሉ ግዴታቸው ሲሆን ቤቱን ሊጎብኙት ለአላህ መብት አለው። በአላህ የካደ (ግን እራሱን እንጂ ማንንም አይጎዳም።) አላህ ከዓለማት ሁሉ የተብቃቃ ነውና።
(98) 98.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «የመጽሐፉ ሰዎች ሆይ! አላህ በምትሰሩት ሁሉ ላይ አዋቂ ሲሆን በአላህ ተዐምራቱ ለምን ትክዳላችሁ?» በላቸው።
(99) 99. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «እናንተ የመጽሐፉ ሰዎች ሆይ! እናንተ መስካሪዎች ሆናችሁ ከአላህ መንገድ መጥመሟን የምትፈልጉ ስትሆኑ ያመነን ሰው ለምን ትከለክላላችሁ? አላህም ከምትሰሩት ነገር ላይ ሁሉ ዘንጊ አይደለም።» በላቸው።
(100) 100. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ከእነዚያ መጽሐፍትን ከተሰጡ መካከል ከፊሎቹን ብትታዘዙ ከእምነታችሁ በኋላ ወደ ክህደት ይመልሷችኋል።
(101) 101. የአላህ አናቅጽ በእናንተ ላይ እየተነበቡና መልዕክተኛዉም በመካከላችሁ እያለ እንዴት ትክዳላችሁ? በአላህ የሚጠበቅ ሰው ሁሉ ወደ ቀጥተኛው መንገድ በእርግጥ ተመራ::
(102) 102. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ትክክለኛውን ፍራቻ ፍሩት። እናንተም ሙስሊሞች ሆናችሁ እንጂ አትሙቱ።
(103) 103. (እናንተ ያመናችሁ ሆይ!) የአላህን ጠንካራ የእምነት ገመድም ሁላችሁም ያዙ:: አትለያዩም። ጠበኞች በነበራችሁ ጊዜ በእናንተ ላይ የዋለውን የአላህን ጸጋም አስታውሱ:: ይሀውም በልቦቻችሁ መካከል አስማማ በጸጋዉም ወንድማማቾች ሆናችሁ:: በእሳት ጉድጓድ አፋፍ ላይ የነበራችሁ ስትሆኑ ከእርሷም አዳናችሁ:: ወደ ቀጥተኛው መንገድ ትመሩ ዘንድ አላህ ለእናንተ አናቅጽን እንደዚሁ ያብራራል::
(104) 104. (እናንተ ያመናችሁ ሆይ!) ከናንተ መካከል ወደ በጎ ነገር የሚጠሩና በመልካም ስራ የሚያዙ፤ ከክፉ ነገርም የሚከለክሉ ቡድኖች ይኑሩ:: እነዚያ ከእሳት የሚድኑ እነርሱው ናቸው።
(105) 105. (እናንተ ያመናችሁ ሆይ!) እንደነዚያ ግልጽ ተዐምራት ከመጣላቸው በኋላ እንደተለያዩትና እንደተጨቃጨቁት የመጽሐፉ ባለቤት ሰዎች አትሁኑ:: እነዚያም ለነርሱ ታላቅ ቅጣት አለባቸው::
(106) 106.ያን ፊቶች የሚያበሩበትና ፊቶች የሚጠቁሩበትን የትንሳኤን ቀን አስታውሱ። እነዚያ ፊቶቻቸው የጠቆሩት ወገኖች «ከእምነታችሁ በኋላ ካዳችሁን? እግዲያዉስ ትክዱ የነበራችሁትን ነገር ቅጣቱን ቅመሱ።» ይባላሉ።
(107) 107. እነዚያ ፊቶቻቸው ያበሩት ወገኖች ደግሞ በአላህ ችሮታ ገነት ውስጥ ናቸው:: እነርሱ በውስጧ ዘወታሪዎች ናቸው::
(108) 108. እነኚህ ባንተ ላይ በእውነት የምናነባቸው የአላህ አናቅጽ ናቸው:: አላህም ለዓለማት በደልን የሚሻ አይደለም::
(109) 109. በሰማያትና በምድር ውስጥ ያለ ሁሉ የአላህ ነው:: ነገሮች ሁሉ ወደ አላህ ይመለሳሉ።
(110) 110. (ሙስሊሞች ሆይ!) ለሰው ልጆች ከተገለፁት ሕዝቦች ሁሉ በላጭ ሆናችሁ:: ይኸዉም በመልካም ነገር ታዛላችሁ:: ከመጥፎም ነገር ትከለክላላችሁ:: በአላህም አንድነት ታምናላችሁና ነው:: የመጽሐፉ ሰዎችም ልክ እንደናንተው ባመኑ ኑሮ ለእነርሱ የተሻለ በሆነ ነበር። ከእነርሱ መካከል ትክክለኛ አማኞችም አሉ:: አብዛሀኞቻቸው ግን አመጸኞች ናቸው::
(111) 111 (ሙስሊሞች ሆይ!) ማስከፋትን እንጂ ፈጽሞ አይጎዷችሁም:: ቢዋጓችሁም ጀርባዎችን ያዞሩላችኋል (ይሸሻሉ)። ከዚያም በምንም ረዳት አያገኙም::
(112) 112. በየተገኙበት ስፍራ ከአላህ በሆነ ቃልኪዳን ወይም ከሰዎች በሆነ ቃል ኪዳን የተጠበቁ ካልሆኑ በስተቀር በእነርሱ ላይ ውርደት ተጽፎባቸዋል። ከአላህ በሆነ ቁጣ ተመለሱ። ድህነትም በእነርሱ ላይ ተፅፎባቸዋል። ይህ የሆነውም በአላህ ተዐምራት (አናቅጽ) ይክዱ፤ ነቢያትንም ያላ አግባብ ይገድሉ ስለነበሩ ነው:: ይህም የሆነው በማመፃቸውና ወሰንን ይተላለፉ ስለነበሩ ነው::
(113) 113. የመጽሐፉ ባለቤቶች ሁሉ እኩል አይደሉም:: ከመጽሐፉ ባለቤቶች መካከል ቀጥ ያሉና በሌሊት ሰዓቶች እየሰገዱ የአላህን አናቅጽ የሚያነቡ ሕዝቦችም አሉ።
(114) 114. በአላህና በመጨረሻዉም ቀን ያምናሉ:: በጽድቅም ነገር ያዛሉ:: ከመጥፎ ነገርም ይከለክላሉ:: ለበጎ ስራዎችም ይጣደፋሉ:: እነርሱ ከደጋግ ሰዎች ናቸው::
(115) 115. ከበጎ የሚሰሩትን አይካዱም። (ውድቅ አይደረግባቸዉም::) አላህ ጥንቁቆቹን ሁሉ አዋቂ ነውና።
(116) 116. እነዚያ በአላህ የካዱት ገንዘቦቻቸውና ልጆቻቸው ከአላህ ቅጣት ምንንም አያድኗቸዉም:: እነዚያም የእሳት ጓዶች ናቸው:: እነርሱም በእርሷ ውስጥ ዘውታሪዎች ናቸው::
(117) 117. በዚህች በቅርቢቱ ሕይወት የሚለግሱት ነገር ምሳሌው በውስጧ ውርጭ ያለባት ነፋስ ነፍሶቻቸውን የበደሉን ሕዝቦች አዝመራ እንደነካችና እንዳጠፋች ብጤ ነው። አላህም አልበደላቸዉም። ግን እነርሱ ነፍሶቻቸውን በእራሳቸው የሚበድሉ ናቸው እንጂ::
(118) 118. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ሚስጥረኛን (የልብ ወዳጅ) ከእናንተ ሌላ ከሆኑት አታድርጉ። የእናንተን ጉዳይ ከማበላሸት አይቦዝኑላችሁምና። ጉዳታችሁን ይወዳሉና (ይመኛሉ)። ለእናንተ ያላቸው ጥላቻ ከአፎቻቸው ላይ እንኳ ተገለጸ:: በልቦቻቸው የሚደብቁት ደግሞ ከዚህ ይበልጥ የከፋ ነው:: ልብ የምታደርጉ እንደሆናችሁ ለእናንተ ማብራሪያዎችን በእርግጥ ገለጽን::
(119) 119. እናንተ ትወዷቸዋላችሁ:: እነርሱ ግን በፍጹም አይወዷችሁም:: እናንተ በሁሉም መጽሐፍት ታምናላችሁ:: እነርሱ ግን ባገኟችሁ ጊዜ «አምነናል» ይላሉ:: ከናንተ ባገለሉ ጊዜ ግን ከቁጭታቸው የተነሳ በእናንተ ላይ ዐጥቆቻቸውን (ጣቶቻቸውን) ይነክሳሉ:: (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «በቁጭታችሁ ሙቱ። አላህ ልቦች የቋጠሩትን ሁሉ አዋቂ ነውና።» በላቸው።
(120) 120. ደግ ነገር ብታገኙ ይከፋቸዋል:: መጥፎ ነገር ቢደርስባችሁ ግን በሷ ይደሰታሉ:: ከታገሳችሁና አላህን ከፈራችሁ ተንኮላቸው ምንም አይጎዳችሁም:: አላህ ለሚሰሩት ሁሉ በዕውቀቱ ከባቢ ነውና::
(121) 121. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አማኞችን ለውጊያ ስፍራዎች የምታዘጋጅ ሆነህ ከቤተሰብህ በጧት በወጣህ ጊዜ የሆነውን አስታውስ:: አላህ ሁሉን ሰሚ ሁሉንም አዋቂ ነውና።
(122) 122. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አላህ ረዳታቸው ሲሆን ከእናንተ መካከል ሁለት ቡድኖች (ወገኖች) ለመፍራት ባሰቡ ጊዜ የሆነውን አስታውስ:: በአላህ ላይ ብቻ አማኞች ይመኩ::
(123) 123. (እናንተ ያመናችሁ ሆይ!) በበድር ዘመቻ ዕለት እናንተ ጥቂቶች ሆናችሁ ሳለ አላህ በእርግጥ ረዳችሁ:: አላህን ታመሰግኑ ዘንድ ፍሩት::
(124) 124. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ለአማኞች (እንዲህ) በምትል ጊዜ የሆነውን አስታውስ: «ጌታችሁ በሶስት ሺ መላዕክት የተወረዱ ሲሆኑ ቢረዳችሁ አይበቃችሁምን?
(125) 125. «አዎን! ብትታገሱና ብትጠነቀቁ አሁኑኑ በፍጥነት ጠላቶቻችሁ ቢመጡባችሁም ጌታችሁ ምልክት ባላቸው አምስት ሺህ መላዕክት ይረዳችኋል።»
(126) 126. አላህ ለእናንተ ብስራትና ልቦቻችሁ በእርሱ እንዲረኩ እንጂ እርዳታውን ለምንም አላደረገዉም:: ድልም አሸናፊና ጥበበኛ ከሆነው ከአላህ ዘንድ ብቻ እንጂ ከሌላ ከማንም የሚገኝ አይደለም::
(127) 127. (ድልን ያጎናፀፋችሁ) ከእነዚያ ከካዱት ከፊልን ሊቆርጥ (ሊያጠፋ) ወይም ሊያዋርዳቸውና ያፈሩ ሁነው እንዲመለሱ ነው።
(128) 128. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እነርሱ ራሳቸውን በዳዮች ናቸውና አላህ በእነርሱ ላይ ከፈለገም ይቅርታ ቢያደርግ ወይም በጥፋታቸው ቢቀጣቸውም ላንተ በነገሩ ላይ ምንም የለህም።
(129) 129. በሰማያትና በምድር ውስጥ ያለውም ሁሉ የአላህ ብቻ ነው:: ለፈለገው ሰው ይምራል:: የሚፈለገውን ሰው ይቀጣል:: አላህ መሀሪና አዛኝ ነውና::
(130) 130. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አራጣን የተነባበሩ እጥፎች ሲሆኑ አትብሉ:: ከገሀነም እሳት ትድኑም ዘንድ (አራጣን በመተው) አላህን ፍሩ::
(131) 131. ያችን ለከሓዲያን የተደገሰችውን የገሀነም እሳት ተጠንቀቁ::
(132) 132.(እናንተ ያመናችሁ ሆይ!) ይታዘንላችሁም ዘንድ አላህንና መልዕክተኛውን ታዘዙ::
(133) 133. ወደ ጌታችሁ ምህረትና ስፋቷ ሰባቱ ሰማያትንና ምድርን ያክል ወደ ሆነችው ገነት አላህን ለሚፈሩ የተዘጋጀች ስትሆን ተቻኮሉ::
(134) 134. ለእነዚያ በድሎትም ሆነ በችግር ጊዜ ለሚለግሱት፤ ቁጭትንም ገቺዎች፤ ለሰዎችም ይቅርታ አድራጊዎች ለሆኑት፤ አላህ በጎ ሰሪዎችን ሁሉ ይወዳልና::
(135) 135. ለእነዚያም መጥፎ ስራን በሰሩ ወይም ነፍሶቻቸውን በበደሉ ጊዜ አላህን የሚያስታውሱና ለኃጢአቶቻቸው ምህረትን የሚለምኑ ለሆኑት ተደግሳለች:: ከአላህ ሌላ ኃጢአቶችን የሚምር ማን ነው? (አንድም የለም::) በስህተት በሰሩት ላይ እነርሱ የሚያውቁ ሲሆኑ የማይዘወትሩ ለሆኑት ሁሉ ተደግሳለች::
(136) 136. እነዚያ ምንዳቸው ከጌታቸው ምህረትና በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲሆኑ በስሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸው ገነቶችም ናቸው:: የመልካም ሰሪዎች ሁሉ ምንዳ የሆነችው ገነት ምንኛ አማረች!
(137) 137. (እናንተ ያመናችሁ ሆይ!) ከእናንተ በፊት በእርግጥ ብዙ አልፈዋል። በምድር ላይ ሂዱና ያስተባባዮች ፍፃሜ እንዴት እንደነበረ ተመልከቱ።
(138) 138. ይህ ቁርኣን ለሰዎች ሁሉ ማብራርያ፤ ለጥንቁቆችም መመሪያና ገሳጭ ነው::
(139) 139. (እናንተ ያመናችሁ ሆይ!) እናንተ የበላዮች ናችሁና ትክክለኛ አማኞች እንደሆናችሁ አትድከሙ (አትስነፉ)። አትዘኑም።
(140) 140. አማኞች ሆይ! የመቁስል ጉዳት ቢያገኛችሁ ሌሎች ህዝቦችም መሰሉ የመቁሰል ጉዳት አግኝቷቸዋል። እንዲሁ ቀናትን በሰዎች መካከል እናፈራርቃቸዋለን:: አላህ እነዚያን በትክክል በሱ ያመኑትን ሊለይና ከእናንተም መካከል ሰማዕታትን ሊመርጥ እንዲህ አይነት ቀናት እንዲፈራረቁ ያደርጋል:: አላህም በዳዮችን ሁሉ አይወድምና::
(141) 141. አላህ እነዚያን በትክክል በእርሱ ያመኑትን ከኃጢአት ሊያጸዳና ከሓዲያንንም ሊያጠፋ ይህንን አደረገ።
(142) 142. (እናንተ ያመናችሁ ሆይ!) አላህ ከናንተ መካከል እነዚያን የታገሉትንና ታጋሾችን ሳይለይ ገነትን የምትገቡ መሰላችሁን?
(143) 143. በጦርነት ላይ መሞትን ሳታገኙት በፊት የምትመኙት ነበራችሁ:: እናንተም በአይናችሁ የምትመለከቱ ስትሆኑ በእርግጥ አያችሁት። (ታዲያ ለምን ሸሻችሁት?)
(144) 144. (መልዕክተኛችን) ሙሐመድ ከበፊቱ ብዙ መልዕክተኞች እንዳለፉት የሆነ መልዕክተኛ እንጂ አይደለም:: ታዲያ እሱ ቢሞት ወይ ቢገደል ወደ ኋላችሁ ትገለበጣላችሁን? ወደ ኋላው የሚቀለበስም አላህን ምንም አይጎዳም:: አላህ አመስጋኞቹን ተገቢዉን ይመነዳልና::
(145) 145. ማንኛዋም ነፍስ በተወሰነላት ጊዜ በአላህ ፈቃድ ቢሆን እንጂ አትሞትም። የቅርቢቱን ዓለም ምንዳ የሚፈልግን ሁሉ ከእርሷ እንሰጠዋለን:: የመጨረሻይቱን ዓለም ምንዳ የሚፈልግንም ከእርሷ እንሰጠዋለን:: አመስጋኞችንም በእርግጥ ተገቢውን እንመነዳለን::
(146) 146. ከነብያት ሊቃውንት ከእነሱ ጋር ሆነው የተዋጉ ብዙ አሉ። እናም በአላህ መንገድ ለሚደርስባቸው ነገር ምንም አልፈሩም:: አልደከሙም:: ለጠላት አልተዋረዱም:: አላህም ትዕግስተኞቹን ይወዳል::
(147) 147. ንግግራቸዉም «ጌታችን ሆይ! ኃጢአቶቻችንንና በነገራችን ሁሉ ወሰን ማለፋችንን ማርልን። ጫማዎቻችንንም አደላድል:: በከሓዲያን ሕዝቦች ላይም እርዳን።» ማለታቸው እንጂ ሌላ አልነበረም።
(148) 148. አላህ የቅርቢቱን ዓለም ምንዳና የመጨረሻይቱን መልካም ምንዳ ሰጣቸው:: አላህ በጎ አድራጊዎችን ሁሉ ይወዳልና::
(149) 149. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እነዚያን በአላህ የካዱትን ብትታዘዙ ወደ ኋላችሁ ይመልሷችኋል። ከከሳሪዎቹም ትሆናላችሁ።
(150) 150. ይልቁን አላህ ብቻ ረዳታችሁ ነው:: እርሱ ከረዳቶች ሁሉ በላጭ ነውና::
(151) 151. በእነዚያ በካዱት ልቦች ውስጥ አላህ በእሱ አስረጂ ያላወረደበትን ነገር በአላህ በማጋራታቸው ምክንያት ፍርሃትን እንጥላለን:: መኖሪያቸዉም የገሀነም እሳት ናት:: የበዳዮች መኖሪያ የሆነችው ገሀነምም መኖሪያነቷ ምን ትከፋ!
(152) 152. በእርግጥ አላህ በፈቃዱ ጠላቶቻችሁን በምትጨፈጭፏቸው ጊዜ ቃልኪዳንን በእርግጥ አረጋገጠላችሁ:: የምትወዱትንም ነገር ካሳያችሁ በኋላ በፈራችሁ፣ በትዕዛዙም በተጨቃጨቃችሁና ባመፃችሁም ጊዜ (ግን እርዳታውን ከለከላችሁ):: ከናንተ ውስጥ ቅርቢቱን ዓለም የሚሻ አለ:: ከናንተም ውስጥ የመጨርሻይቱን ዓለም የሚሻ አለ:: ከዚያም ሊሞክራችሁ ከእነርሱ አዞራችሁ:: በእርግጥም ለእናንተ ይቅርታ አደረገላችሁ:: አላህ ሁልጊዜም በአማኞች ላይ የችሮታ ባለቤት ነውና::
(153) 153. (የመልዕክተኛችን ሙሐመድ ባልደረቦች ሆይ!) መልዕክተኛው ከኋላችሁ ሁኖ እየጠራችሁ የማትዞሩ ሆናችሁ በርቀት በምትሸሹ ጊዜ የሆነውን አስታውሱ:: ባመለጣችሁ እድልና በደረሰባችሁም ነገር አለማዘንን ሊያስተምራችሁ በሀሳብ ላይ ሀሳብን አደረሰባችሁ:: አላህ በምትሰሩት ነገር ሁሉ ውሰጠ አዋቂ ነው::
(154) 154. ከዚያም ከጭንቅ በኋላ ጸጥታን ከናንተ ከፊሎችን የሚሸፍንን እንቅልፍ በእናንተ ላይ አወረደ:: ከፊሎችንም ነፍሶቻቸው በእርግጥ አሳሰቧቸው:: እውነት ያልሆነውን የመሀይምነትን መጠራጠር በአላህ ላይ ይጠራጠራሉ:: «በነገሩ ላይ ምንም የመወሰን መብት አለን? (የለንም።») ይላሉ:: (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «የመወሰን መብት ሁሉ የአላህ ብቻ ነው።» በላቸው:: ላንተ ግልጽ የማያደርጉትን በልቦቻቸው ውስጥ ይደብቃሉ:: «የመወሰን መብት ቢኖረን ኖሮ በዚህ ቦታ ላይ ባልተገደልን ነበር» ይላሉ:: (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «በቤታችሁ ውስጥ በሆናችሁም ኖሮ እነዚያ በእነርሱ ላይ መገደል የተጸፈባቸው ወደየመውደቂያቸው በወጡ ነበር።» በላቸው:: አላህ ፍርዱን ሊፈጽምና በደረቶቻችሁም ውስጥ ያለውን ሊፈትን በልቦቻችሁም ውስጥ ያለውን ነገር ሊገልጽ ይህንን ሰራ:: አላህ በደረቶች ውስጥ ያለውን ሁሉ ነገር ሳይቀር አዋቂ ነውና::
(155) 155.(የመልዕክተኛችን ባልደረቦች ሆይ!) እነዚያ ሁለቱ ቡድኖች በተገናኙ ቀን ከናንተ የሸሹትን ሰዎች በዚያ በሰሩት ከፊል ምክንያት ያሳሳታቸው ሰይጣን ነው:: አላህ ከእነርሱ በእርግጥ ይቅር ብሏል:: አላህ መሀሪና ለቅጣት የማይቸኩል ታጋሽ ነውና።
(156) 156. (እናንተ ያመናችሁ ሆይ!) እነደነዚያ በአላህ እንደካዱትና ስለ ወንድሞቻቸው በምድር ላይ በተጓዙና ወይም ዘማቾች በሆኑ ጊዜ እኛ ዘንድ በነበሩ ኖሮ ባልሞቱ ባልተገደሉም ነበር እንደሚሉት ሰዎች አትሁኑ:: አላህ በልቦቻቸው ውስጥ ጸጸት ያደርግባቸው ዘንድ ይህንን አሉ:: አላህ የፈለገውን ሕያው ያደርጋል:: የፈለገውን ይገድላልም:: አላህ የምትሰሩትን ነገር ሁሉ ተመልካች ነው::
(157) 157. (እናንተ ያመናችሁ ሆይ!) በአላህ መንገድ ላይ ስትዋጉ ብትገደሉ ወይም ብትሞቱ ከአላህ የሆነው ምህረትና እዝነት እነርሱ ከሚሰበስቡት ሀብት ሁሉ የእናንተ ምንዳ በላጭ ነው::
(158) 158. በጂሃድ ብትሞቱ ወይም ብትገደሉ ወደ አላህ ብቻ ትሰበሰባላችሁ::
(159) 159. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በአላህ ችሮታ ለዘብክላቸው:: አመለ መጥፎና ልበ ደረቅ በሆንክ ኖሮ ከአጠገብህ በተበተኑ ነበር:: ከእነርሱም ጥፋት ይቅር በል:: ለእነርሱም ከአላህ ምህረትን ለምንላቸው:: በሁሉም ነገር ላይ አማክራቸው:: ከዚያ ቁርጥ ሀሳብ ባደረገክ ጊዜ በአላህ ላይ ብቻ ተመካ:: አላህ በእርሱ ላይ ብቻ ተመኪዎችን ይወዳልና::
(160) 160. (ሙስሊሞች ሆይ!) አላህ ከረዳችሁ እናንተን የሚያሸንፍ የለም:: እርሱ ካዋረዳቸሁ ደግሞ ከእርሱ ማዋረድ በኋላ የሚረዳችሁ ያ ማን ነው? አማኞች በአላህ ላይ ብቻ ይመኩ።
(161) 161. የምርኮን ገንዘብ መደበቅ ከነብይ የሚሆን አይደለም። የምርኮን ገንዘብ የሚደብቅም በትንሳኤ ቀን የደበቀውን ነገር ተሸክሞ ይመጣል:: ከዚያ ነፍስ ሁሉ የስራዋን ዋጋ ትመነዳለች:: እነርሱም አይበደሉም።
(162) 162. የአላህን ውዴታ የተከተለ ሁሉ የአላህን ቁጣ እንዳተረፈና መኖሪያውም ገሀነም እንደሆነው ነውን? ገሀነም ማረፊያነቱ እጅግ ከፋ!
(163) 163. ሁሉም በአላህ ዘንድ ባለ ልዩ ልዩ ደረጃዎች ናቸው:: አላህ የሚሰሩትን ሁሉ ተመልካች ነውና::
(164) 164. አላህ በአማኞች ላይ ከመካከላቸው የሆነን፤ በእነርሱም ላይ አናቅጽን የሚያነብ፤ ከርክሰት የሚያጠራቸው፤ መጽሐፍንና ጥበብንም የሚያስተምራቸውን መልዕክተኛ በላከላቸው ጊዜ በእርግጥ ለገሰላቸው:: እነርሱም ከዚያ በፊት ግልጽ ስህተት ውስጥ ነበሩ::
(165) 165. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «እናንተ ያደረሳችሁትን ጥቃት ግማሽ በአገኛችሁ (በደረሰባችሁ) ጊዜ ይህ ከየት ነው የመጣብን አላችሁን? እርሱ ከነፍሶቻችሁ ዘንድ ነው:: አላህም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው።» በላቸው።
(166) 166. (የመልዕክተኛችን ባልደረቦች ሆይ!) ያ ሁለት ቡድኖች በተጋጠሙ ቀን የደረሰባችሁ በአላህ ፈቃድ ብቻ ነው:: የአማኞችን አቋም ሊፈትንና ማንነታቸውን ሊገልጽ ነው።
(167) 167. እነዚያንም የነፈቁትንና «ኑ በአላህ መንገድ ተጋደሉ ወይም ተከላከሉ።» የተባሉትን ሊገልጽ ነው ይህን ያደረገው። አስመሳዮቹም «ውጊያን ብናውቅ ኖሮ በተከተልናችሁ ነበር።» አሉ:: እነርሱም ያን ጊዜ ከእምነት ይልቅ ወደ ክህደት የቀረቡ ናቸው:: በልቦቻቸው የሌለውን በአፎቻቸው ይናገራሉ። አላህም የሚደብቁትን ሁሉ አዋቂ ነው።
(168) 168. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እነዚህ ከትግል ወደ ኋላ የቀሩ ሲሆኑ ለወንድሞቻቸው «እኛን በታዘዙን ኖሮ ባልተገደሉ ነበር።» ያሉ ናቸው:: «እውነተኞችም ከሆናችሁ እስቲ ከነፍሶቻችሁ ላይ ሞትን ገፍትሩ።» በላቸው።
(169) 169. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እነዚያንም በአላህ መንገድ የተገደሉትን ሰማዕታት ሙታን አድርገህ አትገምታቸው:: በእርግጥ እነርሱ ጌታቸው ዘንድ ሕያው ናቸውና:: ከጌታቸው ዘንድም ሲሳይ ይለገሳሉ::
(170) 170. አላህ ከችሮታው በሰጣቸው ነገር ተደሳቾች (ሲሆኑ ይመገባሉ):: በእነዚያም ከኋላቸው ገና ባልተከተሏቸውም (ባልሞቱትም እንደነርሱው ከተሰው) በእነርሱ ላይ ስጋትም ትካዜም የሌለባቸው ለመሆናቸው ይደሰታሉ።
(171) 171. በአላህ ጸጋ፤ ችሮታና የአማኞችን ምንዳ የማያጠፋ በመሆኑም ይደሰታሉ።
(172) 172. እነዚያን የመቁሰል አደጋ ከደረሰባቸው በኋላ ለአላህና ለመልዕክተኛው የታዘዙት ከእነርሱ መካከል በጎ ተግባርን ለሰሩና አላህንም ለፈሩት ሁሉ ታላቅ ምንዳ አለላቸው።
(173) 173. እነዚያም ሰዎች ለእነርሱ «ጠላቶች ለእናንተ ጦርን እንደገና አከማችተዋልና ፍሯቸው።» ያሏቸውና ይህም በእምነት ላይ እምነትን የጨመረላቸው ቃላቸዉም «በቂያችን አላህ ነው፤ እርሱም ምን ያምር መጠጊያ ነው!» ያሉ ናቸው።
(174) 174. ከዚያም የአላህን ጸጋና ችሮታ ይዘው ምንም ክፉ ነገር ሳይነካቸው በሰላም ተመለሱ:: የአላህን ውዴታም ተከተሉ:: አላህም የታላቅ ችሮታ ባለቤት ነውና::
(175) 175. ይህ የሚያስፈራራችሁ ሰይጣን ብቻ ነው። ወዳጆቹን ያስፈራራችኋል። (አማኞች ሆይ!) የሰይጣንን ወዳጆችን አትፍሯቸው:: ትክክለኛ አማኞች ከሆናችሁም እኔን ብቻ ፍሩኝ::
(176) 176. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) የእነዚያ ወደ ክህደት የሚቻኮሉ ሰዎች አድራጎት (ተግባር) አያሳዝንህ:: እነርሱ ፈጽሞ አላህን በምንም አይጎዱትምና:: አላህ በመጨረሻይቱ ዓለም ለእነርሱ እድልን ላያደርግ ይሻልና:: ለእነርሱም ታላቅ ቅጣት አለባቸው::
(177) 177. እነዚያ ክህደትን በእምነት የለወጡ ክፍሎች ሁሉ አላህን በምንም ነገር ፈጽሞ አይጎዱትም:: ለእነርሱም አሳማሚ ቅጣት አለባቸው::
(178) 178. እነዚያ በአላህ የካዱ ሰዎች ሁሉ እነርሱን ማዘግየታችንን ለነፍሶቻችን ደግ ነገር ነው ብለው አያስቡ:: እነርሱን የምናዘገያቸው ኃጢአትን እንዲጨምሩ ብቻ ነውና:: ለእነርሱም አዋራጅ ቅጣት አለባቸው::
(179) 179. (እናንተ ያመናችሁ ሆይ!) አላህ መጥፎውን ከመልካሙ እስከሚለይ ድረስ አማኞችን እናንተ ባላችሁበት ሁኔታ ላይ የሚተዋቸው አይደለም:: አላህም ሩቁን ነገር የሚያሳውቃችሁ አይደለም:: ግን አላህ ከመልዕክተኞቹ የሚሻውን ይመርጣል:: እናም በአላህና በመልዕክተኞቹም እመኑ:: ብታምኑና ብትጠነቀቁ ለእናንተ ታላቅ ምንዳ አለላችሁ::
(180) 180. እነዚያ አላህ ከችሮታው ከሰጣቸው ገንዘብ የሚነፍጉ ሰዎች ንፉግነት ደግ ተግባር አይምሰላቸው:: ይልቁንም እርሱ ለእነርሱ መጥፎ ባህሪ ነው:: ያንን በእርሱ የነፈጉበት ገንዘብ በትንሳኤ ቀን (እባብ ሆኖ) በአንገታቸው ይጠለቃሉ:: የሰማያትና የምድር ውርስ ለአላህ ብቻ ነው:: አላህ በምትሰሩት ነገር ሁሉ ውስጠ አዋቂ ነውና::
(181) 181. አላህ የእነዚያን «አላህ ድሃ ነው እኛ ግን ከበርቴዎች ነን።» ያሉትን ሰዎች ቃል በእርግጥ ሰማ:: ያንን ያሉትንና ነብያትን ያለ ህግ መግደላቸውንም በእርግጥ እንጽፋለን:: «የማቃጠልንም ስቃይ ቅመሱ።» እንላቸዋለን።
(182) 182. ያ ስቃይ እጃችሁ ባሳለፉት ስራና አላህም ለባሮቹ በዳይ ባለመሆኑ ነው::
(183) 183. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እነዚያ ይህን ቃል የተናገሩት: «ለማንኛዉም መልዕክተኛ እሳት የምትበላው ቁርባን እስከሚያመጣልን ድረስ በሱ እንዳናምን አላህ ወደ እኛ አዝዟል።» ያሉ ናቸው:: «ብዙ መልዕክተኞች ከእኔ በፊት በግልጽ ተዓምራትና በዚያ ባላችሁት ቁርባን በእርግጥ መጥተውላችኋል:: እውነተኞች ከሆናችሁ ታዲያ ለምን ገደላቸኃቸው?» በላቸው::
(184) 184. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ቢያስተባብሉህም ካንተ በፊትም በግልጽ ተዐምራት፣ በጽሁፎች፣ በብሩህ መጽሐፍም የመጡ መልዕክተኞችም በእርግጥ (በእነርሱ መሰሎች) ተስተባብለዋል::
(185) 185. ነፍስ ሁሉ ሞትን በእርግጥ ቀማሽ ናት:: ምንዳዎቻችሁንም የምትሞሉት በትንሳኤ ቀን ብቻ ነው:: ከእሳት እንዲርቅ ተደርጎ ገነት እንዲገባ የተደረገም በእርግጥ ምኞቱን አገኘ:: የቅርቢቱ ሕይወት ማታለያ እንጂ ሌላ አይደለችም::
(186) 186. (እናንተ ያመናችሁ ሆይ!) በገንዘቦቻችሁና በነፍሶቻችሁ ትፈተናላችሁ:: ከእነዚያ ከናንተ በፊት መጽሐፍን ከተሰጡትም ከእነዚያ በአላህ ካጋሩትም ቡድኖች ብዙ መጥፎ ነገሮችን ትሰማላችሁ:: ብትታገሱና ብትጠነቀቁ (በጣም ጥሩ ነው።) ይህ ተግባር ከታላላቅ ነገሮች አንዱ ነው።
(187) 187. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አላህ የእነዚያ መጽሐፍን የተሰጡትን ለሰዎች በእርግጥ «ልታብራሩት እንጂ ላትደብቁት» በማለት የያዘባቸውን ቃል ኪዳን አስታውስ:: እናም በጀርባዎቻቸው በኋላ ወረወሩት:: በእርሱም ጥቂትን ዋጋ ገዙበት:: የሚገዙትም ነገር ከፋ!
(188) 188. እነዚያን በሰሩት ነገር የሚደሰቱና ባልሰሩትም መመስገንን የሚወዱ ሰዎችን ከቅጣት በመዳን ላይ ናቸው ብለህ አታስባቸው:: ለእነርሱ አሳማሚ ቅጣት አለባቸውና::
(189) 189. የሰማያትና የምድር ንግስና ለአላህ ብቻ ነው:: አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነውና::
(190) 190. በሰማያትና በምድር መፈጠር፤ በሌሊትና በቀንም መተካካት ለባለ አእምሮዎች ሁሉ ታላላቅ ምልክቶች አሉት።
(191) 191. እነርሱም እነዚያ ቆመው ተቀምጠዉም በጎኖቻቸው ተጋድመዉም አላህን የሚያወሱ በሰማያትና በምድር አፈጣጠርም የሚያስተነትኑና (እንዲህም) የሚሉ ናቸው: «ጌታችን ሆይ! ይህን በከንቱ አልፈጠርከዉም ጥራት ይገባህ:: ከእሳትም ቅጣት ጠብቀን።
(192) 192. «ጌታችን ሆይ! አንተ እሳት የምታስገባው ሰው ሁሉ በእርግጥ አዋረድከው:: ለበደለኞች ምንም ረዳቶች የሏቸዉም።
(193) 193. «ጌታችን ሆይ! እኛ በጌታችሁ እመኑ በማለት ወደ እምነት የሚጠራን ጠሪ ሰማንና ወዲያዉኑ አመንም::ጌታችን ሆይ! ኃጢአቶቻችንንም ማርልን ክፉ ስራዎቻችንንም አብስልን:: ከንጹሆች ሰዎች ጋርም ግደለን::
(194) 194. «ጌታችን ሆይ! በመልዕክተኞቹ አማካኝነት የሰጠኸንን፤ የገባህልንን የተስፋ ቃል ስጠን:: በትንሳኤ ቀንም አታዋርደን:: (አታሳፍረን::) አንተ ቀጠሮን አታፈርስምና።»
(195) 195. እናም ጌታቸው «እኔ ከናንተ ውስጥ የወንድንም ሆነ የሴትን መልካም ስራ ወሮታ አላጠፋም:: ከፊላችሁ የከፊሉ አካል ነው።» በማለት ልመናቸውን ተቀበላቸው:: እነዚያ ለዲን ሲሉ የተሰደዱ፣ ከአገሮቻቸዉም በግፍ የተባረሩ፣ በመንገዴም (ሁከት የደረሰባቸው)፣ የተጠቁ፣ የተጋደሉ እና የተገደሉም ክፉ ስራዎቻቸውን አብስላቸዋለሁ:: በስሮቻቸዉም ወንዞች የሚፈሰባቸውን ገነቶች አስገባቸዋለሁ:: እነርሱም ከአላህ ዘንድ የሆነን ከፍተኛ ምንዳ ይመነዳሉ:: አላህ እርሱ ዘንድ መልካም ምንዳ አለና::
(196) 196. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) የእነዚያ በአላህ የካዱ ሰዎች በየአገሮች መንፈላሰስ አያታልህ።
(197) 197. አነስተኛ ጥቅም ነው። ከዚያ መኖሪያቸው ገሀነም ናት:: ገሀነም ደግሞ ማረፊያነቷ ምን ትከፋ!
(198) 198. እነዚያ ጌታቸውን የፈሩት ግን ከስሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸው ገነቶች በውስጧ ዘወታሪዎች ሲሆኑ አላህ ዘንድ የተሰጡ መስተንግዶዎች አሏቸው:: አላህ ዘንድ ያለውም ምንዳ ለበጎ ሰሪዎች ሁሉ በላጭ ነው::
(199) 199. ከመጽሐፉ ባለቤቶች መካከል አላህን ፈሪዎችና በአላህ አናቅጽም ጥቂትን ዋጋ የማይለውጡ ሲሆኑ በአላህና በዚያ ወደ እናንተ በተወረደው ቁርኣን በዚያም ወደ እነርሱ በተወረዱት ልዩ ልዩ መጽሐፍት የሚያምኑ ሰዎች አሉ:: እነዚያ ለእነርሱ በጌታቸው ዘንድ ተገቢው ምንዳቸው አለላቸው አላህ ምርመራው ፈጣን ነው::
(200) 200. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ከእሳት ቅጣት ትድኑ ዘንድ ታገሱ፣ ተበራቱም፣ በጦር ኬላ ላይ ሆናችሁም ሶላትን ተጠባበቁ:: አላህንም በትክክል ፍሩ::