45 - Al-Jaathiya ()

|

(1) 1. ሓ፤ሚይም፤

(2) 2. የመጽሐፉ መወረድ ሁሉን አሸናፊና ጥበበኛ ከሆነው ከአላህ ነው::

(3) 3. በሰማያትና በምድር ውስጥ ለአማኞች ሁሉ እርግጠኛ ምልክቶች አሉ::

(4) 4. (ሰዎች ሆይ!) እናንተን በመፍጠር እና ከተንቀሳቃሽ ነገሮች በምድር ላይ የሚበተነውን ሁሉ በመፍጠሩ ለሚያረጋግጡ ህዝቦች ሁሉ አያሌ ተአምራት አሉ::

(5) 5. በሌሊትና በቀን መተካካትም፤ አላህ ከሰማይ ባወረደው ሲሳይ (ዝናብ) በእርሱም ምድርን ከሞተች በኋላ ህያው በማድረጉ፤ ንፋሶችንም (በየ አቅጣጫው) በማዘዋወሩ ለሚያውቁ ህዝቦች ሁሉ በቂ ማስረጃዎች አሉ።

(6) 6. እነዚህ ባንተ ላይ በእውነት የምናነባቸው የሆኑ የአላህ ማስረጃዎች ናቸው:: ከአላህና ከማስረጃዎቹ በኋላ በየትኛው ንግግር ያምናሉ?

(7) 7. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ውሸታም፤ ኃጢአተኛ ለሆነ ሁሉ ወዮለት (ጥፋት ተገባው)

(8) 8. የአላህን አናቅጽ በእርሱ ላይ የሚነበቡለት ሲሆኑ ይሰማል:: ከዚያም የኮራ ሲሆን እንዳልሰማ ሆኖ በክህደቱ ላይ ይዘወትራል:: እናም እርሱን በአሳማሚ ቅጣት አብስረው::

(9) 9. ከአናቅጻችንም አንዲትን ነገር ባወቀ ጊዜ መሳለቂያ ያደርጋታል:: እነዚያ ለእነርሱ አዋራጅ ቅጣት አለባቸው::

(10) 10. ከፊታቸዉም ገሀነም አለች:: የሰበሰቡት ሀብትም ከእነርሱ ላይ ምንንም አይመልስላቸዉም:: ከአላህ ሌላም ረዳቶች ያደረጓቸው ሁሉ ምንንም አይጠቅሟቸዉም:: ለእነርሱም ታላቅ ቅጣት አለባቸው::

(11) 11. ይህ ቁርኣን መሪ ነው:: እነዚያም በጌታቸው አናቅጽ የካዱት ሁሉ ለእነርሱ ከብርቱ ቅጣት ድርሻቸው አለባቸው።

(12) 12. አላህ ያ ባህርን በውስጡ ታንኳዎች በፈቃዱ እንዲንሻለሉበት ከችሮታዉም እንድትፈልጉበት እንድታመሰግኑትም ለእናንተ የገራላችሁ ነው።

(13) 13. ለእናንተ በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ በመላ ከእርሱ ሲሆን ያገራላችሁ ነው። በዚህ ለሚያስተነትኑ ህዝቦች ሁሉ አያሌ ተዐምራት አሉበት።

(14) 14. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ለእነዚያ በአላህ ላመኑት «ለእነዚያ የአላህን ቀናት ለማይፈሩት ሰዎች ምህረት (ይቅርታ) አድርጉ» በላቸው:: (አላህ) ህዝቦችን ይሰሩት በነበሩት ነገር ይመነዳልና።

(15) 15. መልካምን የሰራ ሁሉ ጥቅሙ ለነፍሱ ነው:: ክፉንም ተግባር የሰራ ሁሉ ክፋቱ በእርሱው ላይ ነው:: ከዚያም ሁላችሁም ወደ ጌታችሁ ትመለሳላችሁ::

(16) 16. ለኢስራኢል ልጆችም መጽሐፍን፤ ሕግን እና ነብይነትን በእርግጥ ሰጠናቸው:: ከመልካም ሲሳዮችም ለገስንላቸው:: (በዘመናቸው ከነበሩት) የዓለማት ህዝብ ላይም አበለጥናቸው::

(17) 17. ከትዕዛዝም ግልጽ ነገሮችን ሰጠናቸው:: እውቀቱም ከመጣላቸው በኋላ በመካከላቸው ለምቀኝነት እንጅ ለሌላ አልተለያዩም:: (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህ በትንሳኤ ቀን በዚያ በእርሱ ይለያዩበት በነበሩት ነገር ሁሉ በመካከላቸው በትክክል ይፈርዳል::

(18) 18. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከዚያም ከሃይማኖት በትክክለኛው ሕግ ላይ አደረግንህ:: ስለዚህ ተከተለው:: የነዚያን የማያውቁትን ህዝቦች ዝንባሌዎች አትከተል::

(19) 19. እነርሱ ከአላህ ቅጣት ምንንም ካንተ አይገፈትሩልህምና። በደለኞችም ከፊላቸው ለከፊሉ ረዳቶች ናቸው:: አላህ የጥንቁቆቹ ወዳጅ ነውና::

(20) 20. ይህ (ቁርኣን) ለሰዎች የልብ ብርሃኖች ነው:: ለሚያረጋግጡትም ህዝቦች ሁሉ መሪና እዝነት ነው::

(21) 21. እነዚያ ኃጢአቶችን የሰሩ ሕይወታቸዉንም ሞታቸዉንም ልክ እንደነዚያ እንዳመኑት መልካሞችንም እንደሰሩት ልናደርጋቸው ያስባሉን? (አይስቡ):: ይህ ከሆነ ፍርዱ ምንኛ ከፋ፤

(22) 22. አላህም ሰማያትንና ምድርን በትክክል ፈጠረ:: እነርሱ የማይበደሉ ሲሆኑ ነፍስ ሁሉ በሰራችው ስራ ትመነዳ ዘንድ።

(23) 23. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ዝንባሌውን አምላኩ ያደረገውን አላህም ከእውቀት ጋር ያጠመመውን በጆሮውና በልቡም ላይ ያተመበትን በዓይኑም ላይ ሺፋን ያደረገበትን ሰው አየህን? ታዲያ ከአላህ በኋላ የሚያቀናው ማነው? አትገሰጹምን?

(24) 24. (ከሓዲያን) «እርሷም(ሕይወት) የቅርቢቱ ሕይወታችን ብቻ እንጂ ሌላ አይደለችም:: እንሞታለን:: ህያዉም እንሆናለን:: ከጊዜም (ማለፍ) በሰተቀር ሌላ አያጠፋንም» አሉ:: ለእነርሱም በዚህ በሚሉት ምንም እውቀት የላቸዉም:: እነርሱ የሚጠራጠሩ እንጂ ሌላ አይደሉም::

(25) 25. አናቅጻችንም ግልፆች ሆነው በእነርሱ ላይ በተነበቡላቸው ጊዜ የክርክራቸው ማስረጃ «እውነተኞች እንደሆናችሁ እስቲ የቀድሞ አባቶቻችንን አምጡ» ማለት እንጂ ሌላ አልነበረም።

(26) 26. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «አላህ ህያው ያደርጋችኋል ከዚያም ያሞታችኋልም:: ከዚያም በትንሳኤ ቀን ይሰበስባችኋል:: ይህም ጥርጥር የለበትም:: ግን አብዛኛዎቹ ሰዎች አያውቁም።» በላቸው::

(27) 27. የሰማያትና የምድር ግዛት የአላህ ብቻ ነው:: ሰዓቲቱም በምትከሰትበት ቀን ያን ጊዜ አጥፊዎች ሁሉ ይከስራሉ::

(28) 28. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ህዝቦችን ሁሉ ተንበርካኪ ሆነው ታያቸዋለህ:: ህዝብም ሁሉ ወደ ግል መጽሐፋቸው ይጠራሉ:: ይባላሉም: «ዛሬ ቀደም ሲል ትሰሩት የነበራችሁትን ነገር ትመነዳላችሁ

(29) 29. «ይህ መጽሐፋችን ነው:: በእናንተ ላይ በእውነት ይናገራል:: እኛ ያንን ትሰሩት የነበራችሁትን ሁሉ እናስገለብጥ ነበርንና» (ይባላሉ)::

(30) 30. እነዚያ ያመኑትና መልካሞችን የሰሩትማ ጌታቸው በእዝነቱ ውስጥ ያስገባቸዋል:: ይህ እርሱ ግልጽ የሆነ እድልን ማግኘት ነው::

(31) 31. እነዚያም የካዱትማ ለእነርሱ ይባላሉ: «አናቅጾቼ በእናንተ ላይ ይነበቡ አልነበሩምን? ኮራችሁም :: ከሓዲያን ህዝቦችም ነበራችሁ::

(32) 32. «የአላህ ቀጠሮ እውነት ነው:: በእርሷ መምጣት (ጥርጥር) የለም:: በተባለ ጊዜም 'ሰዓቲቱ ምን እንደሆነች አናውቅም መጠራጠርን የምንጠራጠር እንጂ ሌላ አይደለንም:: እኛም አረጋጋጮች አይደለንም' አላችሁ::» (ይባላሉ)

(33) 33. የሰሩዋቸው ኃጢአቶችም ለእነርሱ ይገለጹላቸዋል:: ያም በእርሱ ይሳለቁበት የነበሩት ቅጣት በእነርሱ ላይ ይወርድባቸዋል::

(34) 34. «በዱንያ የዚህንም ቀናችሁን መገናኘት እንደረሳችሁ ሁሉ ዛሬ እኛም እንተዋችኋለን:: መኖሪያችሁም እሳት ናት:: ለእናንተም ከረዳቶች ምንም የላችሁም» ይባላል።

(35) 35. «ይህ እናንተ የአላህን አናቅጽ መቀላጃ በማድረጋችሁና ቅርቢቱ ሕይወት ስለ አታለለቻችሁ ነው» ይባላሉ:: ዛሬ ከእርሷ አይወጡም:: እነርሱም በወቀሳ አይታለፉም::

(36) 36. ምስጋና ሁሉ ለሰማያት፤ ለምድርና ለዓለማት ጌታ ለሆነው ለአላህ ብቻ የተገባው ነው::

(37) 37. ኩራትም በሰማያትም ሆነ በምድር ለእርሱ ብቻ ነው:: እርሱ ሁሉን አሸናፊና ጥበበኛ ነውና::