(1) 1. ሓ፤ ሚይም፤
(2) 2. የመጽሐፉን መውረድ አሸናፊው አዋቂው ከሆነው ከአላህ ብቻ ነው::
(3) 3. ኃጢአት መሀሪና ጸጸትን ተቀባይ፤ ቅጣተ ብርቱ፤ የልግስና ባለቤት ከሆነው አላህ ብቻ የተወረደ ነው:: ከእርሱ በስተቀር (እውነተኛ) አምላክ የለም:: መመለሻዉም ወደ እርሱ ብቻ ነው::
(4) 4. በአላህ አንቀጾች እነዚያ የካዱት ቢኾኑ እንጅ ማንም (በመዝለፍ) አይከራከርም፡፡ በያገሮችም ውስጥ መዘዋወራቸው አይሸንግልህ፡፡
(5) 5. ከእነርሱ በፊት የኑህ ህዝቦች ከኋላቸዉም አህዛቦች አስተባበሉ:: ህዝቦችም ሁሉ መልዕክተኛቸውን ሊይዙ አሰቡ፤ በውሸትም በእርሱ እውነትን ሊያጠፉበት ተከራከሩ:: ያዝኳቸዉም። ታዲያ ቅጣቴ እንዴት ነበር?
(6) 6. ልክ እንደዚሁም የጌታህ ቃል በእነዚያ በአላህ በካዱት ላይ እነርሱ የእሳት ጓዶች ናቸው ማለት ተረጋገጠች::
(7) 7. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እነዚያ ዐርሹን የሚሸከሙት እነዚያም በዙሪያው ያሉት በጌታቸው ምስጋና ያወድሳሉ፤ በእርሱም ያምናሉ። ለነዚያ ላመኑትም (እንዲህ እያሉ) ምህረትን ይለምኑላቸዋል: «ጌታችን ሆይ! ነገሩን ሁሉ በእዝነትና በእውቀት ከበሃል፤ ስለዚህ ለእነዚያ ለተጸጸቱት መንገድህንም ለተከተሉት ምህረት አድርግላቸው፤ የእሳትንም ቅጣት ጠብቃቸው፤
(8) 8. «ጌታችን ሆይ! እነርሱም ከአባቶቻቸውና ከሚስቶቻቸዉም ከዝርዮቻቸዉም የበጀውን ሁሉ እነዚያንም ቃል የገባህላቸውን የመኖሪያ ገነቶች አስገባቸው፤ አንተ አሸናፊው ጥበበኛው ነህና::
(9) 9. «ከቅጣቶችም ጠብቃቸው፤ በዚያ ቀንም የምትጠብቀውን በእርግጥ አዘንክለት:: ይህም እርሱ ታላቅ ማግኘት ነው::»
(10) 10. እነዚያ በአላህ የካዱት ሰዎች «ወደ እምነት በምትጠሩና በምትክዱ ጊዜ አላህ (እናንተን) መጥላቱ ነፍሶቻችሁን (ዛሬ) ከመጥላታችሁ የበለጠ ነው።» በማለት ይጠራሉ::
(11) 11. «ጌታችን ሆይ! ሁለትን ሞት አሞትከን:: ሁለትንም ሕይወት ህያው አደረግከን:: በኃጢአቶቻችንም መሰከርን። ታዲያ (ከእሳት) ወደ መውጣት መንገድ አለን?» ይላሉ።
(12) 12. (ከሀዲያን ሆይ!) «ይሃችሁ እነሆ አላህ ብቻውን በተጠራ ጊዜ ስለ ካዳችሁ በእርሱም ተጋሪ ቢደረግ የምታምኑ ስለሆናችሁ ነው:: ስለዚህ ፍርዱ ከፍተኛ ታላቅ ለሆነው አላህ ብቻ ነው::» (ይባላሉ)
(13) 13. (ሰዎች ሆይ!) እርሱ ያ ለአምላክነቱ ምልክቶችን የሚያሳያችሁ፤ ለእናንተም ከሰማይ ሲሳይን የሚያወርድላችሁ ነው:: ወደርሱም የሚመለስ ሰው ቢሆን እንጂ ሌላው አይገሰጽም::
(14) 14. አላህንም ከሓዲያን ቢጠሉም (እንኳ) ሃይማኖትን ለእርሱ አጥሪዎች ሆናችሁ ተገዙ::
(15) 15. እርሱ ደረጃዎችን ከፍ አድራጊ የዐርሹ ባለቤት ነው:: የመገናኛውን ቀን ያስፈራራ ዘንድ ከባሮቹ በሚሻው ሰው ላይ ከትዕዛዙ ራዕይን ያወርዳል::
(16) 16. እነርሱ ከመቃብር በሚወጡበት ቀን ከእነርሱ ምንም ነገር በአላህ ላይ አይደበቅም:: «ንግስናው ዛሬ ለማን ነው?» ይባላል:: «ለአሸናፊው ለአንዱ አላህ ብቻ ነው» ይባላል::
(17) 17. «ዛሬ ነፍስ ሁሉ በሰራችው ስራ ትመነዳለች፤ ዛሬ በደል የለም:: አላህ በእርግጥ ምርመራው ፈጣን ነው።» ይባላል::
(18) 18. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ቅርቢቱንም የትንሳኤ ቀን ልቦች ጭንቀትን የተሞሉ ሆነው ላንቃዎች ዘንድ የሚደርሱበትን ጊዜ አስጠንቅቃቸው:: ለበዳዮች ምንም ወዳጅና ተሰሚ አማላጅ የላቸዉም::
(19) 19. አላህ የዓይኖችን ክዳት ልቦችም የሚደብቁትን ሁሉ ያውቃል::
(20) 20. አላህም በእውነት ይፈርዳል:: እነዚያም ከእርሱ ሌላ የሚገዟቸው በምንም አይፈርዱም:: አላህ እርሱ ሰሚው ተመልካቹ ነው::
(21) 21. የእነዚያን ከእነርሱ በፊት የነበሩትን ህዝቦች ፍፃሜ እንዴት እንደነበረ ይመለከቱ ዘንድ በምድር ላይ አይሄዱምን? በሀይልና በምድር ላይ በተዋቸው ምልክቶች ከእነርሱም ይበልጥ የበረቱ ነበሩ:: አላህም በኃጢአቶቻቸው ያዛቸው። ለእነርሱም ከአላህ ቅጣት ምንም ጠባቂ አልነበራቸዉም::
(22) 22. ይህ (መያዝ) እነርሱ መልዕክተኞቻቸው በተዓምራት ይመጡባቸው ስለ ነበሩና ስለካዱ ነው:: አላህም ያዛቸው። እርሱ ኃያል፤ ቅጣተ ብርቱ ነውና::
(23) 23. ሙሳንም በተዓምራቶቻችንና በግልጽ ማስረጃ በእርግጥ ላክነው::
(24) 24. ወደ ፈርዖን ወደ ሃማን እና ወደ ቃሩንም ላክነው:: «ድግምተኛ እና ውሸታም ነው» አሉ::
(25) 25. ከእኛ ዘንድ እውነትን ይዞ በመጣላቸውም ጊዜ: «የእነዚያን ከእርሱ ጋር ያመኑት ሰዎች ወንድ ልጆች ግደሉ፤ ሴቶቻቸውንም አስቀሩ።» አሉ፤ የከሓዲያንም ተንኮል በጥፋት ውስጥ እንጂ ሌላ አይደለም::
(26) 26. ፈርዖንም «ተዉኝ፤ ሙሳን ልግደል:: (ያድነው እንደሆነም) ጌታውን ይጥራ:: እኔ ሃይማኖታችሁን ሊለውጥ ወይም በምድር ውስጥ ጥፋትን ሊያሰራጭ እፈራለሁና።» አለ::
(27) 27. ሙሳም «እኔ በምርመራው ቀን ከማያምን ትዕቢተኛ ሁሉ በጌታየና በጌታችሁ ተጠበቅሁ።» አለ::
(28) 28. ከፈርዖን ቤተሰቦች አንድ እምነቱን የሚደብቅ ምዕመን ሰውም አለ: «ሰውዬው ከጌታችሁ በታዐምራቶች በእርግጥ የመጣላችሁ ሲሆን 'ጌታየ አላህ ነው' ስለሚል ትገድሉታላችሁን? ውሸታምም ቢሆን ውሸቱ በእርሱ ላይ ነው:: እውነተኛ ቢሆን ግን የእዚያ የሚያስፈራራችሁ ከፊሉ ያገኛችኋል:: አላህ እርሱ ያንን ድንበር አላፊና ውሸታም የሆነውን አይመራምና።
(29) 29. «ወገኖቼ ሆይ! በምድር ላይ አሸናፊዎች ስትሆኑ ዛሬ መንግስትነት የእናንተ ነው:: ታዲያ ከአላህ ቅጣት ቢመጣብን የሚያድነን ማን ነው?» አለ:: ፈርዖንም «የማየውን እንጂ አላመላክታችሁም፤ ቅኑን መንገድ እንጂ አልመራችሁም።» አላቸው።
(30) 30. ያ ያመነው ሰውም አለ፡- «እኔ በእናንተ ላይ የአህዛብን ቀን ብጤ እፈራላችኋለሁ።
(31) 31. «የ(ነብዩ) ኑህን ህዝቦች የዓድንና የሰሙድም የእነዚያን ከኋላቸው የነበሩትንም ህዝቦች ልማድ ብጤ እፈራላችኋለሁ:: አላህም ለባሮቹ መበደል የሚሻ ጌታ (ሆኖ) አይደለም::
(32) 32. «ወገኖቼ ሆይ! እኔ በእናንተ ላይ የመጠራሪያን ቀን እፈራለሁ::»
(33) 33. ወደ ኋላ ዞራችሁ በምትሸሹበት ቀን፤ ለእናንተ ከአላህ ቅጣት ምንም ጠባቂ የላችሁም፤ አላህም የሚያጠመው ሰው ለእርሱ ምንም አቅኚ የለዉም::
(34) 34. ዩሱፍም ከዚህ በፊት ግልጽ ማስረጃዎችን በእርግጥ አመጣላችሁ:: ከዚያ እርሱ ካመጣላችሁ ነገር ከመጠራጠር አልተወገዳችሁም:: በጠፋም ጊዜ «አላህ ከእርሱ በኋላ መልዕክተኛን በጭራሽ አይልክም» አላችሁ፤ አላህ እንደዚሁ ድንበር አላፊ ተጠራጣሪ የሆነን ሰው ያሳስታል።
(35) 35. እነዚያ የመጣላቸው አስረጅ ሳይኖር በአላህ ታዓምራቶች የሚከራከሩ (ክርክራቸው) አላህ ዘንድና እነዚያም ያመኑት ዘንድ መጠላቱ በጣም ተለቀ:: እንደዚሁ አላህ በኩሩ ጨካኝ ልብ ሁሉ ላይ ያትማል::
(36) 36. ፈርዖንም አለ፡- «ሃማን ሆይ! መንገዶችን እደርስ ዘንድ ረዥም ህንፃን ካብልኝ። የሰማያትን መንገዶች እደርስ ዘንድ።
(37) 37. «የሰማያትን መንገዶች እደርስ ዘንድ። ከዚያ ወደ ሙሳ አምላክ እመለከት ዘንድ። እኔም ውሸታም ነው ብዬ እጠረጥረዋለሁ።» አለ:: ልክ እንደዚሁ ለፈርዖን መጥፎ ስራው ተሸለመለት:: ከቅኑ መንገድም ታገደ:: የፈርዖንም ተንኮል በከሳራ ውስጥ እንጂ አይደለም::
(38) 38. ያ ያመነውም አለ፡- «ወገኖቼ ሆይ! ተከተሉኝ ቀጥታውን መንገድ እመራችኋለሁና::
(39) 39. «ወገኖቼ ሆይ! ይህች ቅርቢቱ ሕይወት የጥቂት ቀናት መጣቀሚያ ብቻ ናት፤ መጨረሻይቱ ዓለም ግን እርሷ ትክክለኛ መርጊያ አገር ናት::
(40) 40. «መጥፎን የሰራ ሰው ብጤዋን እንጅ አይመነዳም:: እርሱ ምዕመን ሆኖ ከወንድ ወይም ከሴት በጎ የሰራም እነዚያ ገነትን ይገባሉ:: በእርሷ ውስጥም ያለ ቁጥር ይለገሳሉ።
(41) 41. «ወገኖቼ ሆይ! ወደ መዳን የምጠራችሁ ስሆን ወደ እሳትም የምትጠሩኝ ስትሆኑ ለእኔ ምን አለኝ!
(42) 42. « (እናንተ) በአላህ ልክድና በእርሱም ለእኔ እውቀቱ የሌለኝ ነገር በእርሱ እንዳጋራ ትጠሩኛላችሁ! እኔ አሸናፊና መሀሪ ወደ ሆነው አላህ እጠራችኋለሁ።
(43) 43. «በእርግጥ ወደ እርሱ የምትጠሩኝ ጣዖት ለእርሱ በቅርቢቱም ሆነ በመጨረሻይቱ ዓለም ተሰሚ ጥሪ የለዉም። መመለሻችንም እርግጥ ወደ አላህ ብቻ ነው:: ወሰን አላፊዎችም እነርሱ የእሳት ጓዶች ናቸው።
(44) 44. «ወደ ፊትም ለእናንተ የምላችሁን ምክር (ቅጣትን በምታዩ ጊዜ) ታስታውሱታላችሁ:: ነገሬንም ሁሉ ወደ አላህ አስጠጋለሁ:: አላህ ባሮቹን ተመልካች ነውና።»
(45) 45. ካሴሯቸዉም መጥፎዎች አላህ ጠበቀው፡፡ በፈርዖን ቤተሰቦችም ላይ ክፉ ቅጣት ሰፈረባቸው::
(46) 46. እሳት በጧትና በማታ በእርሷ ላይ ይቀርባሉ፡፡ ሰዓቲቱም በምትሆንበት ቀን «የፈርዖንን ቤተሰቦች ብርቱን ቅጣት ገሀነምን አስገቧቸው» ይባላል።
(47) 47. በእሳት ውስጥ የሚከራከሩበትን ጊዜ አስታውስ: ደካማዎቹም ለነዚያ ለኮሩት «እኛ ለእናንተ ተከታዮች ነበርንና እናንተ አሁን ከእሳት ከፊሉን ከእኛ ላይ ገፍታሪዎች ናችሁን?» ይላሉ::
(48) 48. እነዚያም የኮሩት «እኛ ሁላችንም በውስጧ ነን አላህ በባሮቹ መካከል በእርግጥ ፈርዷል» ይላሉ::
(49) 49. እነዚያም በእሳት ውስጥ ያሉት ለገሀነም ዘበኞች «ጌታችሁን ለምኑልን፤ ከእኛ ላይ ከቅጣቱ ለአንድም ቀን ያቃልልን።» ይላሉ።
(50) 50. ዘበኞቹም «መልዕክተኞቻችሁ በታዐምራቶች ይመጡላችሁ አልነበሩምን?» ይላሉ ከሓዲያንም «እንዴታ መጥተውልናል እንጅ፤ ግን አሰተባበልናቸው።» ይላሉ። «እንግዲያውስ ጸልዩ የከሓዲያንም ጸሎት በከንቱ እንጂ አይደለም።» ይሏቸዋል፡:
(51) 51. እኛ መልክተኞቻችንን እነዚያንም ያመኑትን በቅርቢቱ ሕይወትም ምስክሮች በሚቆሙበት ቀንም በእርግጥ እንረዳለን።
(52) 52. በደለኞችን ምክንያታቸው በማይጠቅማቸው ቀን እንረዳለን። ለነርሱም ርግማን አላቸው:: ለነርሱም መጥፎ አገር አላቸው::
(53) 53. ሙሳንም መምሪያ በእርግጥ ሰጠነው:: የኢስራኢልንም ልጆች መጽሐፍን አወረስናቸው::
(54) 54. ለባለ አእምሮዎች መሪና ገሳጭ ሲሆን፤
(55) 55. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ታገስም የአላህ ተስፋ እውነት ነውና፤ ለስህተትህም ምህረትን ለምን፤ ከቀትር በኋላም በማለዳም ጌታህን ከማመስገን ጋር አጥራው::
(56) 56. እነዚያ የመጣላቸው አስረጅ ሳይኖር በአላህ አናቅጽ የሚከራከሩ በልቦቻቸው ውስጥ እነርሱ ደራሾች ያልሆኑት ኩራት ብቻ እንጂ ምንም የለም:: በአላህም ብቻ ተጠበቅ፤ እነሆ እርሱ ሁሉን ሰሚና ሁሉን ተመልካች ነውና::
(57) 57. ሰማያትንና ምድርን መፍጠር ሰዎችን ከመፍጠር ይልቅ ታላቅ ነው:: ግን አብዛሀኞቹ ሰዎች አያውቁም::
(58) 58. ዐይነ ስዉርና የሚያይ እነዚያም አምነው መልካሞችን የሰሩትና መጥፎ ሰሪው አይስተካከሉም። በጣም ጥቂትን ብቻ ትገስፃላችሁ::
(59) 59. ሰዓቲቱ በእርግጥ መጪ ናት:: በእርሷ ጥርጥር የለም:: ግን አብዛሀኞቹ ሰዎች አያምኑም::
(60) 60. (ባሮቼ ሆይ!) ጌታችሁም አለ: «ለምኑኝ እቀበላችኋለሁና። እነዚያ እኔን ከመገዛት የሚኮሩት ተዋራጆች ሆነው ገሀነም በእርግጥ ይገባሉ።»
(61) 61. አላህ ያ ለእናንተ ሌሊትን በውስጡ ልታርፉበት ጨለማ፤ ቀንኑ ደግሞ ልትሰሩበት የሚያሳይ ብርሃን ያደረገላችሁ ነው:: አላህ በሰዎች ላይ በእርግጥ የታላቅ ችሮታ ባለቤት ነውና:: ግን አብዛሀኞቹ ሰዎች አያመሰግኑም::
(62) 62. ይሃችሁ ጌታችሁ አላህ ነው:: የነገሩ ሁሉ ፈጣሪ ነው:: ከእርሱ ሌላ አምላክ የለም:: ታዲያ ከእምነት ወዴት ትመለሳላችሁ::
(63) 63. ልክ እንደዚሁ እነዚያ በአላህ አናቅጽ ይክዱ የነበሩት ከእምነት ይመለሳሉ::
(64) 64. (ሰዎች ሆይ)! አላህ ያ ምድርን መርጊያ ሰማይንም ጣሪያ ያደረገላችሁ ነው፡፡ የቀረፃችሁም ቅርፃችሁንም ያሳመረ፤ ከጣፋጭ ሲሳዮችም የሰጣችሁ ነው:: ይሃችሁ ጌታችሁ አላህ ነው። የዓለማትም ጌታ አላህ ላቀ::
(65) 65. እርሱ ብቻ ሁል ጊዜ ህያው ነው:: ከእርሱ ሌላ አምላክ የለም:: ሃይማኖትንም ለርሱ ያጠራችሁ ስትሆኑ «ምስጋና ሁሉ ለዓለማት ጌታ ለሆነው ለአላህ ብቻ ይገባው›› የምትሉ ሆናችሁ ተገዙት::
(66) 66. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «እኔ ከጌታዬ አስረጂዎች በመጡልኝ ጊዜ እነዚያን ከአላህ ሌላ የምትገዙዋቸውን እንዳልገዛ ተከልክያለሁ፤ ለዓለማትም ጌታ ብቻም እንድገዛ ታዝዣለሁ።» በላቸው::
(67) 67. (ሰዎች ሆይ!) እርሱ (አላህ) ያ ከዐፈር ከዚያም ከፍትወት ጠብታ ከዚያም ከረጋ ደም የፈጠራችሁ ነው:: ከዚያም ህፃን አድርጎ ያወጣችኋል:: ከዚያም ጥንካሬያችሁን ትደርሱ ዘንድ፤ ከዚያም ሽማግሌዎች ትሆኑ ዘንድ ያቆያችኋል:: ከናንተም ውስጥ ከዚህ በፊት የሚሞት አለ:: ይህንንም ያደረገው ኑራችሁ የተወሰነ ጊዜም ልትደርሱ ታውቁም ዘንድ ነው::
(68) 68. እርሱ (አላህ) ያ ህያው የሚያደርግና የሚያሞትም ነው:: አንዳችን ነገር በሻም ጊዜ ለእርሱ የሚለው ሁን ነው ወዲያዉም ይሆናል::
(69) 69.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ወደ እነዚያ በአላህ አናቅጽ ወደሚከራከሩት ከእምነት እንዴት እንደሚመለሱ አታይምን?
(70) 70. ወደ እነዚያ በመጽሐፉ በዚያም መልዕክተኞቻችንን በእርሱ በላክንበት ወዳስተባበሉበት አታይምን? ወደፊትም ያውቃሉ::
(71) 71. እንዘዝላዎቹና ሰንሰለቶቹ በአንገቶቻቸው ላይ በተደረጉ ጊዜ (በእርሷ) ይጎተታሉ።
(72) 72. በገሀነም ውስጥ ይጎተታሉ፤ ከዚያም በእሳት ውስጥ ይማገዳሉ::
(73) 73. ከዚያም ለእነርሱ ይባላሉ፡- «(በአላህ) ታጋሯቸው የነበራችሁት የታሉ?
(74) 74. ከአላህ ሌላ የምታጋሩዋቸው (የት አሉ)?» «ከእኛ ተሰወሩብን፤ ከቶ ከዚህ በፊት ምንም የምንገዛ አልነበርንም» ይላሉ:: ልክ እንደዚሁ አላህ ካሐዲያንን ያሳስታል::
(75) 75. «ይህ (ቅጣታችሁ) ያላአግባብ በምድር ውስጥ ትደሰቱ በነበራችሁትና ትንበጣረሩ በነበራችሁት ነው።
(76) 76. የገሀነምን በሮች ውስጧ ዘወታሪዎች ስትሆኑ ግቡ።» (ይባላሉ)። የትዕቢተኞችም መኖሪያ (ገሀነም) ምን ትከፋ!
(77) 77. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ታገስም:: የአላህ ቀጠሮ እውነት ነውና፤ የዚያንም የምናስፈራራቸውን ከፊሉን በህይወትህ ብናሳይህ መልካም ነው:: ወይም ሳናሳይህ ብንገድልህ ወደ እኛ ይመለሳሉ::
(78) 78. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ካንተ በፊትም መልዕክተኞችን በእርግጥ ልከናል። ከእነርሱ ባንተ ላይ የተረክንልህ አለ:: ከእነርሱም ባንተ ላይ ያልተረክነውም አለ:: ለማንኛዉም መልዕክተኛ በአላህ ፈቃድ ካልሆነ በስተቀር ተዓምርን ሊያመጣ አይገባዉም:: የአላህም ትዕዛዝ በመጣ ጊዜ በእውነት ይፈረዳል:: እዚያ ዘንድም አጥፊዎች ይከስራሉ::
(79) 79. አላህ ያ ለእናንተ ግመልን ከብትንና ፍየልን ከእርሷ ከፊሏን ልትጋልቡ የፈጠረላችሁ ነውና:: ከእርሷም ትበላላችሁ::
(80) 80. ለእናተም በርሷ ውስጥ ጥቅሞች አሏችሁ:: በእርሷም ላይ ዕቃን በመጫን በልቦቻችሁ ያሰባችሁትን ጉዳይ ትደርሱ ዘንድ ፈጠረላችሁ። በእርሷም ላይ በመርከቦችም ላይ ትሳፈራላችሁ::
(81) 81. ተዓምራትንም ያሳያችኋል:: ታዲያ ከአላህ ተዓምራት መካከል የትኛውን ትክዳላችሁ?
(82) 82. የእነዚያም ከእነርሱ በፊት የነበሩትን ህዝቦች ፍፃሜ እንዴት እንደነበር ይመለከቱ ዘንድ በምድር ላይ አይሄዱምን ? ከእነርሱ ይበልጥ ብዙዎች በኃይልና በምድር ላይ በተዋቸው ምልክቶችም በጣም ብርቱዎች ነበሩ:: ያም ይሰሩት የነበሩት ለእነርሱ ምንም አልጠቀማቸዉም::
(83) 83. መልዕክተኞቻቸዉም ተዓምራትን ባመጡላችሁ ጊዜ እነርሱ ዘንድ ባለው ዕውቀት ተደሰቱ:: በእርሱ ይሳለቁበት የነበሩት ቅጣትም በእነርሱ ላይ ሰፈረባቸው::
(84) 84. ብርቱ ቅጣታችንንም ባዩ ጊዜ «በአላህ አንድነት አምነናል በእርሱም እናጋራ በነበርነው ጣዖታት ክደናል» አሉ::
(85) 85. ብርቱ ቅጣታችንን ባዩ ጊዜ ማመናቸዉም የሚጠቅማቸው አልነበረም:: የአላህን ደንብ ያችን በባሮቹ ውስጥ ያለፈችውን ተጠንቀቁ:: በዚያ ጊዜም ከሓዲያን ከሰሩ::