33 - Al-Ahzaab ()

|

(1) 1. አንተ ነብይ ሆይ! አላህን ፍራ:: ከሓዲያንንና አስመሳዮችንም አትታዘዝ:: አላህ ሁሉን አዋቂና ጥበበኛ ነውና::

(2) 2. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከጌታህም ወደ አንተ የሚወረደውን ብቻ ተከተል:: አላህ በምትሰሩት ሁሉ ውስጠ አዋቂ ነውና::

(3) 3. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በአላህ ላይ ተመካ:: መመኪያነትም በአላህ ብቻ በቃ።

(4) 4. (ሙስሊሞች ሆይ!) አላህ ለአንድ ሰው በሆዱ ውስጥ ሁለትን ልቦች አላደረገም:: እነዚያን «እንደናቶቻችን ጀርባዎች ይሁኑብን» የምትሏቸውን ሚስቶቻችሁንም እናቶቻችሁ አላደረገም:: ልጅ በማድረግ የምታስጠጓቸውንም ልጆቻችሁ አላደረገም:: ይህ በአፎቻችሁ የምትሉት ቃላችሁ ብቻ ነው:: አላህ እውነትን ይናገራል:: ትክክለኛውን መንገድም ይመራል::

(5) 5. (ሙስሊሞች ሆይ!) (ልጅ በማድረግ የምታስጠጓቸውን) በአባቶቻቸው ስም በማስጠጋት ጥሯቸው:: እርሱ አላህ ዘንድ ትክክለኛው መንገድ ነውና:: አባቶቻቸውን ባታውቁም በሃይማኖት ወንድሞቻችሁና ዘመዶቻችሁ ናቸው:: በተሳሳታችሁበት ነገርም በእናንተ ላይ ምንም ኃጢአት የለባችሁም:: ልቦቻችሁ አውቀው በሰራችሁት ስህተት ግን ኃጢአት አለባችሁ:: አላህ መሀሪና አዛኝ ነውና::

(6) 6. ነብዩ (ሙሐመድ) ለአማኞች ከነፍሶቻቸው ይበልጥ ቀራቢ ነው:: ሚስቶቹም እናቶቻቸው ናቸው:: የዝምድና ባለቤቶችም ከፊላቸው በከፊሉ ላይ (ለውርስ) በአላህ መጽሐፍ ውስጥ ከአማኞችና ከስደተኞች ይልቅ የተገባቸው ናቸው:: ለወዳጆቻችሁ በኑዛዜ መልካም ስራን ብትሰሩ ግን ይፈቀዳል:: ይህ በአላህ መጽሐፉ ውስጥ ቀድሞውኑ የተመዘገበ ነው::

(7) 7. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከነብዮችም ካንተም፤ ከኑህም፤ ከኢብራሂምም፤ ከሙሳም፤ ከመርየም ልጅ ዒሳም የጠበቀ ቃልኪዳናቸውን በያዝን ጊዜ (የሆነውን አስታውስ):: ከእነርሱም የከበደን ቃል ኪዳን ያዝን::

(8) 8. አላህ እውነተኞችን ከእውነታቸው ሊጠይቃቸው (ይህንን ሰራ):: ለከሓዲያንም አሳማሚን ቅጣት አዘጋጀ::

(9) 9. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ብዙ ሰራዊት በመጣባችሁና በእነርሱ ላይ ንፋስንና በአይናችሁ ያላያችሁትን ሰራዊት በላክን ጊዜ ያደረገላችሁን ጸጋ አስታውሱ:: አላህም የምትሰሩትን ተመልካች ነው።

(10) 10. ከበላያችሁም ከናንተ በታችም በመጡባችሁ፤ ዓይኖችም በቃበዙ፤ ልቦችም ወደ ላንቃዎች በደረሱና በአላህም መጥፎ ጥርጣሬዎችን በጠረጠራችሁ ጊዜ ያደረገላችሁን ጸጋ (አስታውሱ)::

(11) 11. እዚያ ዘንድ አማኞች ተሞከሩ:: ብርቱን መንቀጥቀጥም ተንቀጠቀጡ::

(12) 12. መናፍቆችና እነዚያ በልቦቻቸው ውስጥ በሽታ ያለባቸው ሰዎች ሁሉ «አላህና መልዕክተኛው ማታለልን እንጂ ሌላን አልቀጠሩንም።» በሚሉም ጊዜ ያደረገላችሁን ውለታ አስታውሱ::

(13) 13. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከእነርሱም የሆነ ቡድን «የየስሪብ ሰዎች ሆይ! ለእናንተ ስፍራ የላችሁምና ተመለሱ።» ባሉ ጊዜ (የሆነውን አስታውሱ):: ከእነርሱም መካከል ከፊሎቹ ነውረኛ ሳይሆኑ «ቤቶቻችን ነውረኛ ናቸው።» በማለት ነብዩን ከጦሩ ለመመለስ ፈቃድን ይጠይቃሉ:: መሸሽን እንጂ ሌላን አይፈልጉም::

(14) 14. በእርሱም ላይ በቤቶቻቸው ከየቀበሌዋ ከጠላት በተገባባትና ከዚያም ከኢስላም መመለስን በተጠየቁ ኖሮ በፍጥነት በሰሯት ነበር ፡፡ በእሷ ጥቂትን ጊዜ እንጂ አይቆዩም ነበር ፡፡

(15) 15. ጀርባዎችንም ላያዞሩ ከዚያም በፊት በእርግጥ አላህን ቃል ኪዳን የገቡ ነበሩ:: የአላህም ቃል ኪዳን የሚጠየቁበት ትልቅ ሀላፊነት ነው::

(16) 16. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «ከሞት ወይም ከመገደል ብትሸሹ መሸሻችሁ ፈጽሞ አይጠቅማችሁም:: ያን ጊዜም ጥቂትን እንጂ የምትጣቀሙ አትደረጉም።» በላቸው።

(17) 17. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) (ሙስሊምቸ ሆይ!) «አላህ በእናንተ ላይ ክፉን ነገር ቢሻ ያ ከአላህ የሚጠብቃችሁ ማን ነው? ወይም ለእናንተ እዝነትን ቢፈልግ ክፉ የሚያመጣባችሁ ማን ነው?» በላቸው። ከአላህም ሌላ ለእነርሱ ወዳጅም ሆነ ረዳት አያገኙም።

(18) 18. ከናንተ ውስጥ የሚያደናቅፉትን ለወንድሞቻቸዉም «ወደ እኛ ኑ» የሚሉትን፤ ውጊያንም ጥቂትን እንጂ የማይመጡትን በእርግጥ አላህ ያውቃቸዋል::

(19) 19. (አማኞች ሆይ!) በእናንተ ላይ እርዳታን የነፈጉ ሆነው እንጂ የማይመጡትን፤ ሽብሩም በመጣ ጊዜ እንደዚያ ከሞት መከራ በእርሱ ላይ የሚሸፍን አደጋ እንደ ወደቀበት ዓይኖቻቸው ወዲያና ወዲህ የምትንከራተት ሆና ወደ አንተ ሲመለከቱ ታያቸዋለህ:: ሽብሩም በሄደ ጊዜ በገንዘብ ላይ የሚሳሱ ሆነው በተቡ ምላሶች ይነድፏችኋል:: እነዚያ አላመኑም:: ስለዚህ አላህ ስራዎቻቸውን አበላሸ:: ይህም በአላህ ላይ ገር ነው።

(20) 20. (መናፍቆች) አህዛብን አልሄዱም ብለው ያስባሉ አህዛቦችም ቢመጡ እነርሱ በዘላኖች ውስጥ በገጠር የራቁ ሊሆኑ ይመኛሉ:: (ከዚያም) ከወሬዎቻችሁ ይጠይቃሉ:: በእናንተ ውስጥ በነበሩም ኖሮ ጥቂትን እንጂ አይዋጉም ነበር::

(21) 21. (አማኞች ሆይ!) ከናንተ መካከል አላህንና የመጨረሻውን ቀን የሚከጅል ለሆነና አላህንም በብዙ ለሚያወሳ ሰው ሁሉ በአላህ መልዕክተኛ መልካም መከተል አላችሁ::

(22) 22. አማኞችም አህዛብን ባዩ ጊዜ «ይህ አላህና መልዕክተኛው የቀጠሩን ነው:: አላህና መልዕክተኛዉም እውነትን ተናገሩ።» አሉ:: ይህ እምነትንና መታዘዝንም እንጂ ሌላን አልጨመረላቸዉም::

(23) 23. ከአማኞች መካከል በእርሱ ላይ ለአላህ ቃል ኪዳን የገቡበትን በእውነት የፈጸሙ ወንዶች አሉ። ከእነርሱም ስለቱን የፈጸመ ለሃይማኖቱ የተገደለም አለ:: ከእነርሱም መካከል ገና የሚጠባበቅ አለ:: የገቡትን ቃል መለወጥንም አለወጡም::

(24) 24. አላህ እውነተኞችን በእውነተኛነታቸው ሊመነዳ፤ አስመሳዮችንም ቢፈልግ ሊቀጣ ወይም ቢመለሱ በእነርሱ ላይ ጸጸታቸቸውን ሊቀበል ይህን አደረገ:: አላህ መሃሪና አዛኝ ነውና::

(25) 25. እነዚያንም በአላህ የካዱትን በቁጭታቸው የተሞሉ መልካምን ነገር ያላገኙ ሆነው አላህ መለሳቸው:: አማኞቹንም አላህ መጋደልን በቃቸው:: አላህም ብርቱና ሁሉን አሸናፊ ነውና::

(26) 26. እነዚያንም ከመጽሐፉ ባለቤቶች አህዛቦችን የረዷቸውን (ቁረይዟን) ከምሽጎቻቸው አወረዳቸው:: በልቦቻቸዉም ውስጥ መባባትን ጣለባቸው። ከፊሉን ትገድላላችሁ፤ ከፊሉንም ትማርካላችሁ::

(27) 27. ምድራቸውንም ቤቶቻቸውንም ገንዘቦቻቸውንም ገና ያልረገጣችኋትንም ምድር አወረሳችሁ:: አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነውና::

(28) 28. አንተ ነብይ ሆይ! ለሚስቶችህ (እንዲህ) በላቸው: «ቅርቢቱን ህይወትና ጌጧን የምትፈልጉ እንደ ሆናችሁ ኑ:: አጣቅማችኋለሁና መልካምንም መፍታት እፈታችኋለሁና::

(29) 29. «አላህንና መልዕክተኛውን የመጨረሻይቱን አገርም የምትፈልጉ ከሆናችሁ እነሆ አላህ ከናንተ ለመልካም ሰሪዎቹ ትልቅን ምንዳ አዘጋጅቷል።»

(30) 30. እናንተ የነብዩ ሚስቶች ሆይ! ከናንተ ውስጥ ግልጽ የሆነን መጥፎ ስራ የምትሰራ ሴት ቅጣቷ ሁለት እጥፍ ሆኖ ይነባበርባታል:: ይህም በአላህ ዘንድ ገር ነው::

(31) 31. ከናንተም መካከል ለአላህና ለመልዕክተኛው የምትታዘዝ መልካም ስራንም የምትሰራ ሴት ምንዳዋን ሁለት ጊዜ እንሰጣታለን:: ለእርሷም የከበረን ሲሳይ አዘጋጅተንላታል።

(32) 32. እናንተ የነቢዩ ሚስቶች ሆይ! እንደ ማናቸዉም ሴቶች አይደላችሁም:: አላህን ብትፈሩ ትበልጣላችሁ። በልቡ ውስጥ በሽታ ያለበት እንዳይከጅል በንግግር እንኳን አትለስልሱም:: መልካምንም ንግግር ተናገሩ።

(33) 33. በቤቶቻችሁም ውስጥ እርጉ:: እንደ ፊተኛይቱ መሃይምነት ጊዜ መገላለጥም (በመጌጥ) አትገለጡ:: ሶላትንም በደንቡ ስገዱ:: ዘካንም ስጡ:: አላህንና መልክተኛውንም ታዘዙ:: የነብዩ ቤተሰቦች ሆይ! አላህ የሚሻው ከናንተ ላይ ርክሰትን ሊያስወግድና ማጥራትንም ሊያጠራችሁ ብቻ ነው::

(34) 34. ከአላህ አናቅጽና ከጥበቡም በቤቶቻችሁ የሚነበበውን አስታውሱ:: አላህ እዝነቱ ረቂቅና ውስጠ አዋቂ ነውና::

(35) 35. ሙስሊም ወንዶችና ሙስሊም ሴቶች፤ ምእምናንና ምዕመናትም፤ ታዛዦች ወንዶችና ታዛዦች ሴቶችም፤ እውነተኞች ወንዶችና እውነተኞች ሴቶችም፤ ታጋሽ ወንዶችና ታጋሽ ሴቶችም፤ አላህን ፈሪ ወንዶችና አላህን ፈሪ ሴቶችም፤ መጽዋች ወንዶችና መጽዋች ሴቶችም፤ ጿሚ ወንዶችና ጿሚ ሴቶችም፤ ካልተፈቀደ ስራ ብልቶቻቸውን ጠባቂ ወንዶችና ጠባቂ ሴቶችም፤ አላህን በብዙ አውሺ ወንዶችና አውሺ ሴቶችም አላህ ለእነርሱ ምህረትንና ታላቅን ምንዳ አዘጋጅቶላቸዋል::

(36) 36. አላህና መልዕክተኛው በአንድ ነገር ላይ በወሰኑ ጊዜ ለምዕምናንና ለምዕመናት ከተነገራቸው ከመቀበል ዉጭ ምንም ምርጫ ሊኖራቸው አይገባም:: የአላህንና የመልክተኛውን ትእዛዝ የጣሰ ሰው ሁሉ ግልጽ የሆነን መሳሳት በእርግጥ ተሳሳተ::

(37) 37. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ለዚያም አላህ በእርሱ ላይ ለለገሰለትና አንተም (ነጻ በማውጣት) በእርሱ ላይ ለለገስክለት ሰው አላህ ገላጩ የሆነን ነገር በነፍስህ ውስጥ የምትደብቅና አላህን ልትፈራው ይልቅ የተገባው ሲሆን ሰዎችን የምትፈራ ሆነህ «ሚስትህን ያዝ:: አላህንም ፍራ» በምትል ጊዜ (የሆነዉን አስታውስ):: ዘይድም ከእርሷ ጉዳዩን በፈጸመ ጊዜ በምዕመኖች ላይ ልጅ አድርገው ባስጠጓቸው ሰዎች ሚስቶች ከእነርሱ ጉዳይን በፈጸሙ ጊዜ በማግባት ችግር እንዳይደርስባቸው እርሷን አጋባንህ (ዳርንህ):: የአላህም ትእዛዝ ተፈጻሚ ነው::

(38) 38. በነብዩ ላይ አላህ ለእርሱ በፈረደው ነገር ምንም ችግር ሊኖርበት አይገባም:: በእነዚያ ከዚያ በፊት ባለፉት ነብያት አላህ ደነገገው። የአላህም ትእዛዝ የተፈረደ ፍርድ ነው::

(39) 39. ለእነዚያ የአላህን መልዕክቶች ለሚያደርሱና ለሚፈሩት ከአላህ በስተቀርም አንድንም ለማይፈሩት ተደነገገ። ተቆጣጣሪነትም በአላህ በቃ::

(40) 40. (እናንተ ያመናችሁ ሆይ!) ሙሐመድ ከወንዶቻችሁ የአንዱም ሰው አባት አይደለም:: ግን የአላህ መልዕክተኛና የነብያት መደምደሚያ ነው:: አላህ በነገሩ ሁሉ አዋቂ ነው::

(41) 41. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ብዙ ማውሳትን አውሱት::

(42) 42. በቀኑ መጀመሪያና መጨረሻም አጥሩት::

(43) 43. እርሱ ያ በእናንተ ላይ እዝነትን የሚያወርድ ነው:: መላእክቶችም እንደዚሁ ምህረትን የሚለምኑላችሁ ናቸው:: ከጨለማዎች ወደ ብርሃን ያወጣችሁ ዘንድ (ያዝንላችኋል):: ለትክክለኛ አማኞችም በጣም አዛኝ ነው::

(44) 44. በሚገናኙበት ቀን መከባበሪያቸው ሰላም መባባል ነው:: ለእነርሱም የከበረን ምንዳ አዘጋጅቶላቸዋል::

(45) 45. አንተ ነብይ ሆይ! እኛ መስካሪ አብሳሪና አስፈራሪ አድርገን ላክንህ::

(46) 46. ወደ አላህም በፈቃዱ ጠሪ፣ አብሪና ብርሃን አድርገን ላክንህ::

(47) 47. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አማኞችንም ከአላህ ዘንድ ለእነርሱ ታላቅ ችሮታ ያላቸው መሆኑን አብስራቸው::

(48) 48. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከሓዲያንና አስመሳዮችንም አትታዘዛቸው ማሰቃየታቸውንም (ለአላህ) ተው:: በአላህም ላይ ተጠጋ:: በመጠጊያነትም አላህ በቃ::

(49) 49. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ምዕመናትን ባገባችሁና ከዚያም ሳትነኳቸው በፊት በፈታችኋቸው ጊዜ ለናንተ በእነርሱ ላይ የምትቆጥሩዋት ዒዳ ምንም የላችሁም:: ሆኖም አጣቅሟቸው (ጉርሻ ስጧቸው):: መልካም ማሰናበትንም አሰናብቷቸው::

(50) 50. አንተ ነብይ ሆይ! እነዚያን መህሮቻቸውን የሰጠሃቸውን ሚስቶችህን፤ አላህ ባንተ ላይ ከመለሰልህም ሴቶች መካከል እነዚያን እጅህ የጨበጠቻቸውን ምርኮኞች ሴቶች፤ እነዚያን ካንተ ጋር የተሰደዱትን የአጎቶችህንና፤ የአክስቶችህን ሴት ልጆች (እንደዚሁም) የእናትህ ወንድም ሴት ልጆችና የእናትህ እህት ሴት ልጆች ማግባትን ላንተ ፈቅደንልሃል:: ማንኛዋም በአላህ ያመነች ሴት ራሷን ለነብዩ ብትሰጥ ነብዩ ሊያገባት የፈለገ እንደ ሆነ ከአማኞች ሌላ ላንተ ብቻ የተሰጠ መብት ሲሆን ፈቀድንልህ:: በአማኞች ላይ በሚስቶቻቸውና እጆቻቸው በጨበጧቸው ባሮች ነገር ግዴታ ያደረግንባቸውን በእርግጥ አውቀናል:: ባንተ ላይ ችግር እንዳይኖር ያለፉትን ፈቀድንልህ:: አላህ መሃሪና አዛኝ ነውና::

(51) 51. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከእነርሱ መካከል የምትፈልጋትን ታቆያለህ :: የምትፈልጋትንም ወደ አንተ ታስጠጋለህ:: በመፍታት ከአራቅሃትም የፈለግሃትን በመመለስ ብታስጠጋ ባንተ ላይ ኃጢአት የለብህም:: ይህ ዓይኖቻቸው ወደ መርጋት ወደ አለማዘናቸዉም ለሁሉም በሰጠሃቸው ነገር ወደ መውደዳቸዉም በጣም የቀረበ ነው:: አላህም በልቦቻችሁ ውስጥ ያለውን ሁሉ ያውቃል:: አላህ ሁሉን አዋቂና ታጋሽ ነው::

(52) 52. ከእነዚህ በኋላ እጅህ ከጨበጠቻቸው ባሮች በስተቀር ሴቶች ላንተ አይፈቅዱልህም ከሚስቶችም መልካቸው ቢደንቅህም እንኳን በእነርሱ ልትለውጥ አይፈቀድልህም። አላህ በነገሩ ሁሉ ተጠባባቂ ነው::

(53) 53. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! መድረሱን የማትጠባበቁ ስትሆኑ ወደ ምግብ ካልተፈቀደላችሁ በስተቀር የነብዩን ቤቶች በምንም ጊዜ አትግቡ ግን በተጠራችሁ ጊዜ ግቡ በተመገባችሁም ጊዜ ወዲያውኑ ተበተኑ:: ለወግ የምትጫወቱ ሆናችሁም አትቆዩ:: ይሃችሁ ነብዩን በእርግጥ ያስቸግራል:: ከናንተም ያፍራል። ግን አላህ ከእውነት አያፍርም:: እቃንም ለመዋስ በጠየቃችኋቸው ጊዜ ከመጋረጃ ኋላ ሆናችሁ ጠይቋቸው። ይሃችሁ ለልቦቻችሁም ለልቦቻቸዉም የበለጠ ንጽህና ነው:: የአላህንም መልክተኛ ልታስቸግሩ ሚስቶቹንም ከእርሱ በኋላ ምንጊዜም ልታገቡ ለእናንተ አይገባችሁም። ይሃችሁ አላህ ዘንድ ከባድ ኃጢአት ነው::

(54) 54. ማንኛውንም ነገር ብትገልጹ ወይም ብትደብቁት በእርሱ ይመነዳችኋል:: አላህ ነገሩን ሁሉ አዋቂ ነውና::

(55) 55. (የነብዩ ሚስቶች) በአባቶቻቸው፣ በወንዶች ልጆቻቸዉም፣ በወንድሞቻቸውም፣ በወንድሞቻቸው ወንዶች ልጆችም፣ በእኅቶቻቸው ወንዶች ልጆችም፣ ምዕመናት በሆኑት በሴቶቻቸዉም በጨበጧቸዉም ባሮች (አጠገብ ቢገለጡ) በእነርሱ ላይ ምንም ኃጢአት የለባቸዉም:: (ሴቶች ሆይ!) (ታዘዙ):: አላህን ፍሩ:: አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ መስካሪ ነውና፡

(56) 56. አላህና መላዕክቱ በነብዩ (ሙሐመድ) ላይ የአክብሮት እዝነትን ያወርዳሉ:: እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በእርሱ ላይ የአክብሮት እዝነትን አውርዱ:: የማክበርን ሰላምታንም ሰላም በሉ::

(57) 57. እነዚያ አላህንና መልክተኛውን የሚያስከፉ በቅርቢቱ ዓለምም ሆነ በመጨረሻይቱ ዓለም አላህ ረግሟቸዋል:: ለእነርሱም አዋራጅን ቅጣት ደግሶላቸዋል::

(58) 58. እነዚያም አማኞችና ምዕመናትን ባልሰሩት ነገር በመዝለፍ የሚያሰቃዩ ዕብለትንና ግልጽ ኃጢአትን በእርግጥ ተሸከሙ::

(59) 59. አንተ ነብይ ሆይ ! ለሚስቶችህ ለሴቶች ልጆችህም ለትክክለኛ አማኞች ሚስቶችም ከመከናነቢያዎቻቸው በላያቸው ላይ እንዲለቁ ንገራቸው። ይህ እንዳይታወቁና በባለጌዎች እንዳይደፈሩ ለመሆን በጣም የቀረበ ነው:: አላህ መሃሪና አዛኝ ነውና::

(60) 60. አስመሳዮችና እነዚያ በልቦቻቸው ውስጥ (የአመንዝራነት) በሽታ ያለባቸው በመዲናም ውስጥ (በወሬ) አሸባሪዎቹ ከዚህ ስራቸው ባይከለከሉ በእነርሱ ላይ በእርግጥ እንቀሰቅስሃለን ከዚያ በእርሷ ውስጥ ጥቂትን እንጂ አይጎራበቱህም::

(61) 61. የተረገሙ ሆነው እንጂ አይጎራበቱህም:: በየትም ስፍራ ቢገኙ ይያዛሉ:: መገደልንም ይገደላሉ::

(62) 62. እነዚህ ህጎች በእነዚያ ከዚህ በፊት ባለፉት ህዝቦች ላይ የደነገጋቸው የአላህ ድንጋጌ ናቸው:: ለአላህም ድንጋጌዎች ደግሞ ፈጽሞ መለወጥን አታገኝም::

(63) 63. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ሰዎች ከሰዓቲቱ ይጠይቁሃል:: «እውቀቷ አላህ ዘንድ ብቻ ነው።» በላቸው:: የሚያሳውቅህም ምንድን ነው! ሰዓቲቱ በቅርብ ጊዜ ልትሆን ይከጀላል::

(64) 64. አላህ ከሓዲያንን በእርግጥ ረግሟቸዋል። ለነርሱም የተጋገመችን እሳት አዘጋጅቷል::

(65) 65. በእርሷ ውስጥ ዘለዓለም ዘውታሪዎች ሲሆኑ ወዳጅም ረዳትም አያገኙም::

(66) 66. ፊቶቻቸው በእሳት ውስጥ በሚገለባበጡ ቀን «ዋ ምኞታችን! አላህን በተገዛን መልክተኛውንም በታዘዝን ኖሮ» እያሉ ይጸጸታሉ::

(67) 67. ይላሉም «ጌታችን ሆይ! እኛ ጌቶቻችንንና ታላላቆቻችንን ታዘዝን መንገዱንም አሳሳቱን።

(68) 68. «ጌታችን ሆይ! ከቅጣቱ እጥፍን ስጣቸው ታላቅን እርግማንም እርገማቸው::»

(69) 69. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እንደ እነዚያ ሙሳን እንዳሰቃዩት ሰዎች አትሁኑ ካሉትም ነገር ሁሉ አላህ አጠራው:: አላህም ዘንድ ባለሞገስ ነበር::

(70) 70. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ፍሩ:: ትክክለኛን ንግግርም ተናገሩ::

(71) 71. ስራዎቻችሁን ለእናንተ ያበጅላችኋልና ኃጢአቶቻችሁንም ለእናንተ ይምርላችኋል:: አላህንና መልዕክተኛውን የሚታዘዝ ሁሉ በእርግጥ ታላቅን እድል አገኘ::

(72) 72. እኛ አደራን በሰማያት በምድር እና በተራራዎች ላይ አቀረብናት:: መሸከሟንም እንቢ አሉ ከእርሷም ፈሩ። ሰው ግን ተሸከማት እርሱ በጣም በደለኛና ተሳሳች ነውና::

(73) 73. ወንዶች አስመሳዮችንና ሴቶች አስመሳዮችን ወንዶች አጋሪዎችንና ሴቶች አጋሪዎችንም አላህ ሊቀጣ በምዕምናንና በምዕመናትም ላይ አላህ ንስሃን ሊቀበል (አደራዋን ሰው ተሸከማት):: አላህ መሃሪና አዛኝ ነውና::