23 - Al-Muminoon ()

|

(1) 1.ምእምናን ፍላጎታቸውን ሁሉ በእርግጥ አገኙ (ተሳካላቸው)::

(2) 2. እነዚያም በስግደታቸው ውስጥ አላህን ፈሪዎች የሆኑት፤

(3) 3. እነዚያም ከመጥፎ ነገር ሁሉ የራቁ::

(4) 4. እነዚያም ዘካን በአግባቡ ሰጪዎች፤

(5) 5. እነዚያም እነርሱ ብልቶቻቸውን ጠባቂዎች የሆኑት፤

(6) 6. በሚስቶቻቸው ወይም እጆቻቸው በያዟቸው ሴት ባሪያዎች ላይ ካልሆነ በቀር (ብልቶቻቸውን ጠባቂ የሆኑት)፤ እነርሱ በነዚህ የማይወቀሱ ናቸውና።

(7) 7. ከዚህ ሌላ በሆነ መንገድ (ስሜታቸዉን ሊያረኩ) የፈለጉ ሰዎች እነዚያ እነርሱ የአላህን ወሰን አላፊዎች ናቸው::

(8) 8. እነዚያም ለአደራዎቻቸውና ለቃል ኪዳናቸው ጠባቂዎች፤

(9) 9. እነዚያም በስግደቶቻቸው ላይ (ሁለንተናዋን) የሚጠባበቁ የሆኑት

(10) 10. እነዚያ ወራሾቹ እነርሱ ናቸው::

(11) 11. እነዚያ ፊርደውስን (ላዕላይ ገነትን) የሚወርሱ ናቸው:: እነርሱ በእርሷ ውስጥ ዘውታሪዎች እነርሱ ብቻ ናቸው::

(12) 12. በእርግጥ ሰውን (አደምን) ከነጠረ ጭቃ ፈጠርነው::

(13) 13. ከዚያም በተጠበቀ መርጊያ ውስጥ የፍትወት ጠብታ አደረግነው::

(14) 14. ከዚያም ጠብታዋን (በአርባ ቀን) የረጋ ደም አድርገን ፈጠርን፤ የረጋውንም ደም ቁራጭ ስጋ አድርገን ፈጠርን፤ ቁራጭዋንም ስጋ አጥንቶች አድርገን ፈጠርን:: አጥንቶችንም ስጋን አለበስናቸው። ከዚያም (በዉስጡ ነፍስን በመዝራት) ሌላ ፍጥረት አድርገን አስገኘነው:: ከቅርፅ ሰጪዎችም ሁሉ በላጭ የሆነው አላህ ከሁሉ ላቀ።

(15) 15. (ሰዎች ሆይ!) ከዚያም እናንተ ከዚህ በኋላ በእርግጥ ሟቾች ናችሁ::

(16) 16. ከዚያም እናንተ በትንሳኤ ዕለት ትቀሰቀሳላችሁ::

(17) 17. በእርግጥም ከበላያችሁ ሰባትን ሰማያት ፈጠርን:: ከፍጥረቶቹም ዘንጊዎች አይደለንም::

(18) 18. ከሰማይም ውሃን በልክ አወረድን:: በምድርም ውስጥ አስቀመጥነው:: እኛም እርሱን በማስወገድ ላይ በእርግጥ ቻዮች ነን::

(19) 19. በእርሱም ከዘምባባዎችና ከወይኖች አትክልቶችን ለእናንተ አስገኘንላችሁ:: በውስጧ ለእናንተ ብዙ ፍራፍሬዎች አሏችሁ:: ከእርሷም ትበላላችሁ::

(20) 20. ከሲና ተራራም የምትወጣ ዛፍ በቅባትና ለበይዎች መባያ በሚሆን ዘይት ተቀላቅላ የምትበቅልን አስገኘንላችሁ::

(21) 21. (ሰዎች ሆይ!) እናንተም በግመል፤ በከብት በፍየልና በበግ መገምገሚያ አላችሁ:: በሆዶችዋ ውስጥ ካለው ወተት እናጠጣችኋለን:: ለእናንተም በእርሷ ብዙ ጥቅሞች አሏችሁ:: ከእርሷም ትበላላችሁ::

(22) 22. በእርሷም ላይና በመርከብም ላይ ትጫናላችሁ::

(23) 23. ኑሕን ወደ ህዝቦቹ በእርግጥ ላክነው። ወዲያዉም «ህዝቦቼ ሆይ! አላህን ብቻ ተገዙ:: ከእርሱ ሌላ ምንም አምላክ የላችሁም:: አትጠነቀቁምን?» አላቸው።

(24) 24. ከህዝቦቹም እነዚያ ታላላቆቹ ሰዎች አሉ: «ይህ ብጤያችሁ ሰው እንጂ ሌላ አይደለም። በእናንተ ላይ መብለጥን ይፈልጋል። አላህም ቢፈልግ ኖሮ መላእክትን ባወረደ ነበር። ይህንንም የሚለውን በመጀመሪያዎቹ አባቶቻችን አልሰማንም።

(25) 25. «እርሱ እብደት ያለበት ሰው እንጂ ሌላ አይደለም:: በእርሱም እስከ ጊዜው ድረስ ተጠባበቁ።» አሉ።

(26) 26. ኑሕም «ጌታዬ ሆይ! ስለ አስተባበሉኝ እርዳኝ።» አለ።

(27) 27. ወደ እርሱ እንዲህ ስንል ላክን: «በተመልካችነታችንና በትእዛዛችን ታንኳን ስራ። ከዚያ ትእዛዛችን በመጣና ምድጃው (እቶኑ) በፈለቀ ጊዜ በውስጧ ከሁሉም ነገር ሁለት ሁለት ዓይነቶችንና ቤተሰቦችህን ከእነርሱ መካከል ጠፊ በመሆኑ ቃል ያለፈበት ብቻ ሲቀር አስገባ። በእነዚያ ራሳቸውን በአላህ በመካድ በበደሉት ሰዎች ጉዳይ አታነጋግረኝ። እነርሱ በውኃ ተሰማጪዎች ናቸውና።

(28) 28. አንተም አብረውህ ካሉት ፍጡሮች ጋር በታንኳይቱ ላይ በተደላደልክ ጊዜ በል: «ምስጋና ሁሉ ለዚያ ከበደለኛ ህዝቦች ላዳነን አላህ ይገባው።

(29) 29. «ጌታዬ ሆይ! ብሩክ የሆነን ማውረድ አውርደኝ:: አንተም ከአደላዳዮች ሁሉ በላጭ ነህና።» በል።

(30) 30. በዚህ ውስጥ ለሃያልነታችን አያሌ ተዓምራት አሉበት:: እነሆ እኛ (የኑሕን ሰዎች) ፈታኞች ነበርን::

(31) 31. ከዚያ ከኋላቸው ሌሎችን የክፍለ ዘመናት ህዝቦች አስገኘን::

(32) 32. በውስጣቸዉም ከእነርሱ የሆኑን መልዕክተኛ አላህን ተገዙ ከእርሱ ሌላ ትክክለኛ አምላክ የላችሁም:: አትጠነቀቁምን? በማለት ላክን።

(33) 33. ከህዝቦቹም እነዚያ የካዱት ሰዎች በመጨረሻይቱም ቀን መገናኘት ያስተባበሉት በቅርቢቱም ህይወት ያቀማጠልናቸው ታላላቅ ሰዎች አሉ: «ይህ ብጤያችሁ ሰው እንጂ ሌላ አይደለም። ከምትበሉት ምግብ ይበላል፤ ከምትጠጡትም ውሃ ይጠጣል።

(34) 34. «የናንተው ብጤያችሁ የሆነን ሰው ብትታዘዙ በእርግጥ የተሞኛችሁ ናችሁ።

(35) 35. «‹እናንተ ሞታችሁ አፈርና አጥንቶችም በሆናችሁ ጊዜ እናንተ ከመቃብር ትወጣላችሁ› በማለት ያስፈራራችኋልን?

(36) 36. «ያ የምትስፈራሩበት ነገር ከእውነት ራቀ፤ በጣም ራቀ

(37) 37. «እርሷ (ህይወት) ማለት ቅርቢቱ ህይወታችን ብቻ እንጂ ሌላ አይደለችም:: እንሞታለን። ህያዉም እንሆናለን። እኛም ፈጽሞ ተቀስቃሾች አይደለንም" (አሉ)

(38) 38. «እርሱ በአላህ ላይ ውሸትን የቀጠፈ ሰው እንጂ ሌላ አይደለም:: እኛም በእርሱ አማኞች አይደለንም።» አሉ።

(39) 39. መልዕክተኛዉም «ጌታዬ ሆይ! ስላስተባበሉኝ በእነርሱ ላይ እርዳኝ።» አለ።

(40) 40. አላህም «ከጥቂት ጊዜ በኋላ በጥፋታቸው በእርግጥ ተጸጻቾች ይሆናሉ።» አለው።

(41) 41. ወዲያዉም (የጥፋት) ጩኸቲቱ በእውነት ያዘቻቸው፤ እንደ ጎርፍ ግብስባሽም አደረግናቸው:: ለበደለኞች ህዝቦችም ከእዝነት መራቅ ተገባቸው::

(42) 42. ከዚያም ከእነርሱ በኋላ ሌሎችን የክፍለ ዘመናት ህዝቦች አስገኘን::

(43) 43. ማንኛይቱም ህዝብ ጊዜዋን አትቀድምም:: ከጊዜያቸዉም አይቆዩምም::

(44) 44. ከዚያም መልዕክተኞቻችንን በተከታታይ ላክን፤ ማንኛይቱንም ህዝብ መልእክተኛዋ በመጣላት ቁጥር አስተባበሉት። ከፊላቸውንም በከፊሉ በጥፋት አስከታተልን፤ ወሬዎችም አደረግናቸው፤ ለማያምኑም ህዝቦች ከእዝነታችን መራቅ ተገባቸው።

(45) 45. ከዚያ ሙሳንና ወንድሙን ሃሩንን በተአምራታችንና በግልጽ ማስረጃ ላክናቸው::

(46) 46. ወደ ፈርዖንና ወደ ጭፍሮቹ ላክናቸው። ድሮውም የኮሩና የተንበጣረሩ ህዝቦችም ነበሩ።

(47) 47. «ህዝቦቻቸው ለኛ ተገዢዎች ሆነው ሳሉ ብጤያችን ለሆኑ ሰዎች እናምናለን?» አሉ።

(48) 48. አስተባበሏቸዉም፤ ከጠፊዎችም ሆኑ::

(49) 49. ሙሳንም ነገዶቹ ይመሩ ዘንድ መጽሐፍን በእርግጥ ሰጠነው::

(50) 50. የመርየምን ልጅ ዒሳንና እናቱንም ተዓምር አደረግናቸው:: የመደላደልና የምንጭ ባለቤት ወደ ሆነች ከፍተኛ ስፍራም አስጠጋናቸው::

(51) 51. እናንተ መልእክተኞች ሆይ! ከተፈቀዱት ምግቦች ሁሉ ብሉ:: በጎ ስራንም ስሩ:: እኔ የምትሰሩትን ሁሉ አዋቂ ነኝና::

(52) 52. ይህችም በአንድ አምላክ የማመን ህግጋት አንድ መንገድ ስትሆን ሃይማኖታችሁ ናት:: እኔም ጌታችሁ ነኝና ፍሩኝ::

(53) 53. ከዚያም ተከታዮቻቸው ሃይማኖታቸውን በመካከላቸው ክፍልፍሎች አድርገው ቆራረጡ፤ ህዝቦች ሁሉ እነርሱ ዘንድ ባለው ሃይማኖት ተደሳቾች ናቸው::

(54) 54. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እስከ ጊዜያቸዉም ድረስ በጥመታቸው ውስጥ ተዋቸው::

(55) 55. ከገንዘብና ከልጆች በእርሱ የምንጨምርላቸውን ያስባሉን?

(56) 56. በበጎ ነገሮች የምንቻኮልላቸው እንደሆነ ያስባሉን? አይደለም፤ ይህ ሁሉ እነርሱን ለማዘናጋት መሆኑን አያውቁም።

(57) 57. እነዚያ እነርሱ ጌታቸውን ከመፍራት የተነሳ ተጨናቂዎች የሆኑት፤

(58) 58. እነዚያም እነርሱ በጌታቸው ተዓምራት የሚያምኑት፤

(59) 59. እነዚያም በጌታቸው የማያጋሩት፤

(60) 60. እነዚያም የሚሰጡትን ነገር ሁሉ እነርሱ ወደ ጌታቸው ተመላሾች መሆናቸውን ልቦቻቸው የሚፈሩ ሆነው የሚሰጡ ናቸው::

(61) 61. እነዚያ በመልካም ስራዎች ይጣደፋሉ:: እነርሱም ለርሷ ቀዳሚዎች ናቸው::

(62) 62. ማንኛይቱንም ነፍስ የችሎታዋን ያህል እንጂ አናስገድዳትም:: እኛም ዘንድ በእውነት የሚናገር መጽሐፍ አለ:: እነርሱም አይበደሉም::

(63) 63. በእውነቱ ከሓዲያን ልቦቻቸው ከዚህ መጽሐፍ በዝንጋታ ውስጥ ናቸው:: ለእነርሱም ከዚህ ሌላ እነርሱ ለእርሷ ሰሪዎችዋ የሆኑ መጥፎ ስራዎች አሏቸው::

(64) 64. ቅምጥሎቻቸውንም በቅጣት በያዝናቸው ጊዜ ወዲያውኑ እነርሱ ይወተውታሉ::

(65) 65. (ይባላሉም) «ዛሬ አትወትውቱ፤ እናንተ ከእኛ ዘንድ አትረዱምና።

(66) 66. «አንቀፆቼ በእናንተ ላይ በእርግጥ ይነበቡላችሁ ነበር። እናንተ ግን በተረከዞቻችሁ ላይ ወደ ኋላችሁ ትመለሱ ነበር።

(67) 67. «በእርሱ (በክልሉ ቤት) ኩሩዎች ሌሊት ተጫዋቾች (ቁርኣንንም) የምትተው ሆናችሁ (ትመለሱ ነበር)።» ይባላሉ።

(68) 68. የቁርኣንን ንግግርን አያስተነትኑምን? ወይስ ለመጀመሪያዎቹ አባቶቻቸው ያልመጣ ነገር መጣባቸውን?

(69) 69. ወይስ መልዕክተኛቸውን አላወቁምን? ስለዚህ እነርሱ በእርሱ ከሓዲያን ናቸውን?

(70) 70. ወይስ «በእርሱ ዕብደት አለበት» ይላሉን? እብድ አይደለም። እውነትን ይዞ መጣላቸው:: አብዛኞቻቸዉም ግን እውነትን ጠይዎች ናቸው።

(71) 71. እውነታው (አላህ) ዝንባሌዎቻቸውን በተከተለ ኖሮ ሰማያትና ምድር በውስጣቸዉም ያለው ሁሉ በእርግጥ በተበላሸ ነበር:: ይልቁንም ክብራቸው ያለበትን ቁርኣን አመጣንላቸው:: እነርሱም ክብራቸውን ዘንጊዎች ናቸው::

(72) 72. ወይስ (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ግብርን ትጠይቃቸዋለህን? የጌታህም ችሮታ ከሁሉም በላጭ ነው:: እርሱም ከሰጪዎች ሁሉ በላጭ ነው::

(73) 73.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አንተ ወደ ቀጥተኛው መንገድ በእርግጥ ትጠራቸዋለህ::

(74) 74. እነዚያም በመጨረሻይቱ ዓለም የማያምኑት ሰዎች ግን ከትክክለኛው መንገድ ተዘንባዮች ናቸው።

(75) 75. ባዘንላቸውና በእነርሱ ያለውን ጉዳትም ባነሳንላቸው ኖሮ በጥመታቸው ውስጥ የሚዋዥቁ ሆነው ይዘወትሩ ነበር::

(76) 76. በእርግጥም በቅጣት ያዝናቸው:: ታዲያ ለጌታቸው አልተናነሱም:: የሚዋደቁም አይደሉም።

(77) 77. በእነርሱም ላይ የብርቱ ቅጣት ባለቤት የሆነ ደጃፍን በከፈትንባቸው ጊዜ እነርሱ ያን ጊዜ በእርሱ ተስፋ ቆራጮች ናቸው::

(78) 78. እርሱም ያ መስሚያዎችን፤ ማያዎችንና ልቦችን ለእናንተ የፈጠረላችሁ ነው:: ጥቂትን እንጂ አታመሰግኑም::

(79) 79. እርሱም ያ በምድር ውስጥ የበተናችሁ ነው:: በመጨረሻም ጊዜ ወደ እርሱም ትሰበሰባላችሁ::

(80) 80. እርሱም ያ ህያው የሚያደርግ የሚገድልም ነው:: የሌሊትና የቀን መተካካትም የእርሱ ነው :: አታውቁምን?

(81) 81. ይልቁንም የመካ ከሓዲያን ልክ የፊተኞቹ ህዝቦች እንዳሉት ብጤ አሉ::

(82) 82. አሉም: «በሞትንና አፈርና አጥንቶች በሆንን ጊዜ እኛ እንደገና ተቀስቃሾች ነን?

(83) 83. «ይህንን ሁኔታ እኛም ሆነ ከእኛ በፊት የነበሩት አባቶቻችን በእርግጥ ተቀጥረናል፤ ይህ የመጀመሪያዎቹ ሰዎች ተረቶች እንጂ ሌላ አይደለም።» አሉ።

(84) 84. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «ምድርና በውስጧ ያለው ሁሉ የማን ነው? የምታውቁ ከሆናችሁ እስቲ ንገሩኝ።» በላቸው።

(85) 85. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «በእርግጥ የአላህ ነው።» ይሉሃል። «ታዲያ አትገሠጹምን?» በላቸው።

(86) 86. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «የሰባቱ ሰማያት ጌታ የታላቁም ዐርሽ ጌታ ማን ነው?» በላቸው።

(87) 87. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «በእርግጥ አላህ ነው።» ይሉሃል፤ «እንግዲያ አትፈሩትምን?» በላቸው።

(88) 88. «የነገሩ ሁሉ ግዛት በእጁ የሆነ፤ እርሱ የሚጠብቅ በእርሱ ላይ የማይጠበቅ ማን ነው? የምታውቁ ከሆናችሁ (እስቲ መልሱልኝ)» በላቸው።

(89) 89. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «በእርግጥ አላህ ነው።» ይሉሃል፤ «ታዲያ እንዴት ትታለላላችሁ?» በላቸው።

(90) 90. ይልቁንም እውነትን አመጣንላቸው እነርሱም በመካዳቸው ውሸታሞች ናቸው::

(91) 91. አላህ ምንም ልጅን አልያዘም አልወለደም:: ከእርሱም ጋር አንድም አምላክ የለም:: ሌላ አምላክ በነበረማ አምላኩ ሁሉ የፈጠረውን ነገር በማስተዳደር ከሌላው በተለየ ነበር:: ከፊላቸዉም በከፊሉ ላይ በነገሰ ነበር:: አላህ ከሓዲያን እሱን ከሚመጥኑበት መግለጫ ሁሉ ጠራ::

(92) 92. ሩቁንና ቅርቡን ሁሉ አዋቂ ነው:: በእርሱ ከሚያጋሩትም ሁሉ ከፍ አለ::

(93) 93. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በል: «ጌታዬ ሆይ! የሚስፈራሩበትን ቅጣት ብታሳየኝ፤

(94) 94. «ጌታዬ ሆይ! በበደለኞች ህዝቦች ውስጥ አታድርገኝ።» በል።

(95) 95. እኛ የምናስፈራራቸውን ነገር ልናሳይህ በእርግጥ ቻዮች ነን::

(96) 96. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በዚያች እርሷ መልካም በሆነችው ጠባይ መጥፎይቱን ነገር መልስ:: እኛ ከሓዲያን የሚሉትን ሁሉ አዋቂዎች ነንና::

(97) 97. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) (እንዲህ) በል: «ጌታዬ ሆይ ከሰይጣናት ጉትጎታዎች ባንተ እጠበቃለሁ።

(98) 98. «ጌታዬ ሆይ! ወደ እኔ ከመጣዳቸው ከመቅረባቸውም ባንተው እጠበቃለሁ።» በል።

(99) 99. አንዳቸውን ሞት በመጣበት ጊዜ ይላል: «ጌታዬ ሆይ! ወደ ምድረ ዓለም መልሱኝ።

(100) 100. «ችላ ብዬ የተውኩትን በጎ ስራ ልሰራ እከጅላለሁና።» (ይላል)(ይህን ከማለት ይከልከል):: እርስዋ እርሱ ተናጋሪዋ የሆነች ቃል (ብቻ) ናት:: ከበስተፊታቸዉም እስከሚቀሰቀሱበት ቀን ድረስ ግርዶ አለ::

(101) 101. በቀንዱም በተነፋ ጊዜ በዚያ ቀን በመካከላቸው ዝምድና የለም። አይጠያየቁምም::

(102) 102.ሚዛኖቻቸው የከበዱላቸው ሰዎች እነዚያ እነርሱ ፍላጎታቸውን ያገኙ ናቸው::

(103) 103. እነዚያ ሚዛኖቻቸዉም የቀለሉባቸው ሰዎች እነዚያ እነርሱ ነፍሶቻቸውን ያከሰሩ ናቸው፤ በገሀነም ውስጥ ዘውታሪዎች ናቸው::

(104) 104. ፊቶቻቸውን እሳት ትገርፋቸዋለች:: እነርሱም በእርሷ ውስጥ ከንፈሮቻቸው የተኮማተሩ ናቸው::

(105) 105. «አንቀፆቼ በእናንተ ላይ የሚነበቡላችሁና በእነርሱ የምታስተባብሉ አልነበራችሁምን?» ይባላሉ።

(106) 106. (እነርሱም) ይላሉ: «ታላቁ ጌታችን ሆይ! በእኛ ላይ መናጢነታችን አሸነፈችንና ጠማማ ህዝቦች ነበርን።

(107) 107. «ጌታችን ሆይ! ከእርሷ አውጣንና ወደ ዱንያ መልሰን:: ከዚህ በኋላ ወደ ክህደት ብንመለስ እኛ በዳዮች ነን።» ይላሉ።

(108) 108. አላህም ይላቸዋል: «ወራዶች ሆናችሁ በውስጧ አርፋችሁ ኑሩ እንጂ ፍጹም አታናግሩኝ።

(109) 109. «እነሆ ከባሮቼ መካከል ‹ጌታችን ሆይ! አምነናልና ማረን:: እዘንልንም:: አንተ ከአዛኞች ሁሉ ይበልጥ አዛኝ ነህ› የሚሉ ክፍሎች ነበሩ።

(110) 110. «እኔንም ማውሳትን እስካስረሷችሁ ድረስም ማላገጫ አድርጋችሁ ያዛችኋቸው:: በእነርሱም ላይ ትስቁባቸው ነበር።

(111) 111. «እኔ ዛሬ በትዕግስታቸው ምክንያት ፍላጎታቸውን የሚያገኙት እነርሱን ብቻ በማድረግ መነዳኋቸው።» ይላቸዋል።

(112) 112. «በምድር ውስጥ ስንትን አመታትን ቆያችሁ?» ይላቸዋል።

(113) 113. «አንድ ቀንን ወይም ከፊል ቀንን ቆየን:: ቆጣሪዎችንም ጠይቅ» ይላሉ።

(114) 114. ይላቸዋልም: «እናንተ የቆያችሁትን መጠን የምታውቁ ብትሆኑ ኖሮ (በእሳት ውስጥ ከምትቆዩት ጊዜ አንጻር) ጥቂትን ጊዜ እንጂ አልቆያችሁም።

(115) 115. «የፈጠርናችሁ ለከንቱ መሆኑን እናንተም ወደ እኛ የማትመለሱ መሆናችሁን ጠረጠራችሁን? (ለከንቱ የፈጠርናችሁ መሰላችሁን?)።» (ይባላሉ።)

(116) 116. የእውነቱ ንጉስ አላህ ከፍተኛነት ተገባው:: ከእርሱ ሌላ ትክክለኛ አምላክ የለም:: የዚያ የሚያምረው ዐርሽ ጌታም እሱ ብቻ ነው::

(117) 117. ከአላህ ጋር ሌላን አምላክ በእርሱ ማስረጃ የሌለውን የሚገዛ ሁሉ ምርመራው እጌታው ዘንድ ብቻ ነው:: እነሆ ከሓዲያን አይድኑም።

(118) 118. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «ጌታዬ ሆይ! ማር:: እዘንም:: አንተም ከአዛኞች ሁሉ በላጭ ነህና።» በል፡: