42 - Ash-Shura ()

|

(1) 1. ሓ፤ሚይም፤

(2) 2. ዐይን፤ ሲን፤ ቃፍ::

(3) 3. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ልክ እንደዚሁ በዚህ ምዕራፍ ውስጥ እንዳለው አሸናፊውና ጥበበኛው አላህ ወደ አንተ ያወርዳል:: ወደ እነዚያም ካንተ በፊት ወደ ነበሩት ህዝቦችም አውርዷል::

(4) 4. በሰማያትና በምድር ዉስጥ ያለው ሁሉ የእርሱ ብቻ ነው:: እርሱም የበላዩ ታላቁ ነው::

(5) 5. ከአላህ ፍራቻ የተነሳ ሰማያት ከበላያቸው ሊቀደዱ ይቀርባሉ፤ መላእክትም ጌታቸውን እያመሰገኑ ያጠራሉ:: በምድር ላለው ፍጡርም ምህረትን ይለምናሉ:: (ሙስሊሞች ሆይ!) አስተዉሉ:: መሀሪውና አዛኙ አላህ ነው::

(6) 6. እነዚያም ከእርሱ ሌላ ጣዖታትን ረዳቶች አድርገው የያዙ ሁሉ አላህ በእነርሱ ላይ ተጠባባቂ ነው:: አንተም በእነርሱ ላይ ሀላፊ አይደለህም::

(7) 7. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ልክ እንደዚሁም የከተሞች እናት የሆነችውን የመካን ሰዎችና በአካባቢዋ ያሉትን ህዝቦች ልታስፈራራ የመሰብሰቢያውንም ቀን በእርሱ ጥርጣሬ የሌለበት ሲሆን ልታስጠነቅቅ በዐረበኛ ቋንቋ የሆነን ቁርኣንን ወደ አንተ አወረድን:: ከእነርሱም ከፊሉ በገነት ውስጥ ከፊሉም ደግሞ በእሳት ውስጥ ነው::

(8) 8. አላህ በፈለገ ኖሮ ሰዎችን በአንድ ሃይማኖት ላይ የሆኑ አንድ ህዝብ ባደረጋቸው ነበር:: ግን የሚፈልገውን ሰው በእዝነቱ ውስጥ ያስገባዋል:: በዳዮች ሁሉ ምንም ወዳጅና ረዳት የላቸዉም::

(9) 9. ከእርሱ ሌላ ረዳቶች ያዙን? (እነርሱ ረዳቶች አይደሉም) ትክክለኛ ረዳት አላህ ብቻ ነው:: እርሱ ሙታንን ህያው ያደርጋል:: እርሱም በሁሉም ነገር ላይ ቻይ ነውና::

(10) 10. (ሰዎች ሆይ!) «ያ የተለያያችሁበት ነገር ሁሉ ፍርዱ ወደ አላህ ብቻ ነው:: እርሱ (አላህ) ጌታዬ ነው:: በእርሱ ላይ ተመካሁ:: ወደ እርሱም ብቻ እመለሳለሁ» በላቸው::

(11) 11. ሰማያትንና ምድርን የፈጠረው አላህ ከነፍሶቻችሁ ሴቶችን ከቤት እንሰሳዎችም አይነቶችን (ወንዶችና ሴቶችን) ለእናንተ ፈጠረላችሁ:: በዚህ ድርጊቱም ያባዛችኋል:: የሚመስለው ምንም ነገር የለም:: እርሱ ሁሉን ነገር ሰሚና ሁሉን ተመልካች ነው::

(12) 12. የሰማያትና የምድር (ድልቦች) መክፈቻዎች የእርሱ ብቻ ናቸው:: ሲሳይን ለሚፈልገው ሰው ያሰፋል:: ለሚፈልገዉም ያጠባል:: እርሱ ሁሉን ነገር አዋቂ ነውና::

(13) 13. (ሰዎች ሆይ!) ለእናንተ ከሃይማኖት ያንን በእርሱ ኑህን ያዘዘበትን ያንንም ወደ አንተ ያወረድነውን ያንንም ኢብራሂምን፤ ሙሳንና ዒሳንም በእርሱ ያዘዝንበት የሆነውን ሃይማኖትን በትክክል አቋቁሙ በእርሱም ላይ አትለያዩ በማለት ደነገገላችሁ::(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በአላህ አጋሪዎች ያ ወደ እርሱ የምትጠራቸው ነገር (ኢስላም) ከበዳቸው:: አላህ የሚፈልገውን ሰው ወደ እርሱ እምነት ይመርጣል:: የሚመለስንም ሰው ወደ እርሱ ይመራል::

(14) 14. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) የሃይማኖት ሰዎች እውቀት ከመጣላቸው በኋላ በመካከላቸው ባለ ወሰን አላፊነት እንጂ በሌላ አልተለያዩም:: እስከተወሰነ ጊዜ በማቆየት ከጌታህ ያለፈች ቃል ባልነበረች ኖሮ በእነርሱ መካከል አሁኑኑ በተፈረደ ነበር:: እነዚያም ከኋላቸው መጽሐፍን እንዲወርሱ የተደረጉት ከእርሱ በእርግጥ ባወላዋይ ጥርጣሬ ውስጥ ናቸው::

(15) 15. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ወደ እዚህ መንገድም ጋኔንንና ሰዎችን ጥራ:: ልክ እንደታዘዝከዉም ቀጥ በል:: ዝንባሌያቸውን አትከተል:: «ከመጽሐፍም አላህ ባወረደው ሁሉ አመንኩ:: በመካከላችሁ በፍርድ ላስተካክልም ታዘዝኩ:: አላህ ጌታችን ጌታችሁም ነው:: ለእኛ ስራዎቻችን አሉን:: ለእናንተም እንዲሁ ስራዎቻችሁ አሏችሁ:: በእኛና በእናንተ መካከል ክርክር የለም:: አላህ በመካከላችን ይሰበስባል:: መመለሻው ወደ እርሱ ብቻ ነው።» በላቸው::

(16) 16. እነዚያም በአላህ ሃይማኖት ተቀባይነት ካገኘ በኋላ የሚከራከሩት ሰዎች ማስረጃዎቻቸው በጌታቸው ዘንድ ብልሹ (ዉድቅ) ናቸው:: በእነርሱም ላይ የአላህ ቁጣ አለባቸው (ወደቀባቸው):: ለእነርሱም ብርቱ ቅጣት አለባቸው::

(17) 17. አላህ ያ መጽሐፉን በእውነት ያወረደ ነው:: ሚዛንንም ልክ እንደዚሁ ያወረደ ነው:: ሰዓቲቱ ምን አልባት ቅርብ ብትሆንስ ምን አሳወቀህ?

(18) 18. እነዚያ በእርሷ የማያምኑት በእርሷ ያቻኩላሉ:: እነዚያ በአላህ ያመኑት ግን ከእርሷ ፈሪዎች ናቸው:: እርሷ እውነት መሆኗንም በትክክል ያውቃሉ:: (ሙስሊሞች ሆይ!) አስተውሉ:: እነዚያ በሰዓቲቱ የሚከራከሩ ሰዎች ሁሉ በእርግጥ ከእውነት በራቀ ስህተት ውስጥ ናቸው::

(19) 19. አላህ ለባሮቹ በጣም ሩህሩህ ነው:: ለሚፈልገው ሰውም ሁሉ በሰፊው ሲሳይን ይሰጣል:: እርሱም ብርቱዉ እና አሸናፊው ነው::

(20) 20. በስራው የኋለኛይቱን ዓለም አዝመራ የሚፈልግ ሰው ሁሉ ለእርሱ በአዝመራው ላይ ሌላን እንጨምርለታለን:: የቅርቢቱን ዓለም አዝመራ የሚፈልግ ሰው ግን በእርሷ የተወሰነለትን ብቻ እንሰጠዋለን:: ለእርሱም በኋለኛይቱ ዓለም ምንም ድርሻ የለዉም::

(21) 21. ከሓዲያን ከአላህ ያልተፈቀደውን ሃይማኖት የደነገጉ ተጋሪዎች ለእነርሱ አሏቸውን? የፍርዱ ቃል ባልነበረ ኖሮ በመካከላቸው ወዲያውኑ በተፈረደ ነበር:: በደለኞችም አሳማሚ ቅጣት በእርግጥ አለባቸው::

(22) 22. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በደለኞችን በሰሩት ስራ ዋጋ በትንሳኤ ቀን ፈሪዎች ሆነው ታያቸዋለህ:: እርሱም በእነርሱ ላይ የማይቀር ወዳቂ ነው:: (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እነዚያም በአላህ ያመኑና መልካም ስራን የሰሩ ሁሉ በገነት ጨፌዎች ዉስጥ ናቸው:: ለእነርሱም በጌታቸው ዘንድ የሚፈልጉት ሁሉ አለላቸው:: ይህ ታላቅ ችሮታ ነው::

(23) 23. (ይህ ታላቅ ችሮታ) ያ አላህ እነዚያን በትክክል ያመኑትንና መልካሞችን የሰሩት ባሮቹን የሚያበስርበት ነው::(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) መልዕክቴን በማድረሴ ላይ የዝምድና ውዴታየን እንጂ ሌላ ዋጋ አልጠይቃችሁም በላቸው:: መልካም ስራ የሚሰራ ሰው ሁሉ ለእርሱ በእርሷ ላይ መልካምን ነገርን እንጨምርለታለን:: አላህ መሀሪ እና አመስጋኝ ነውና::

(24) 24. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ይልቁንም «በአላህ ላይ ውሸትን ቀጠፈ» ይላሉን? አላህም ቢፈልግ በልብህ ላይ ያትማል:: አላህ ውሸትን ያብሳል:: እውነትንም በቃላቱ ያረጋግጣል:: እርሱ በይፋ የተነገሩት ቀርቶ በልቦች ውስጥ ያለውን ሁሉ አዋቂ ነውና::

(25) 25. እርሱም አላህ ያ ሁልጊዜም ከባሮቹ ንስሀን የሚቀበል ኃጢአቶችንም ይቅር የሚል የምትሰሩትንም ሁሉ የሚያውቅ ጌታ ነው::

(26) 26. እነዚያም በአላህ ያመኑትና መልካም ተግባሮችን የሰሩትን ልመናቸውን ይቀበላል:: ከችሮታዉም ይጨምርላቸዋል:: ከሓዲያንም ለእነርሱ ብርቱ ቅጣት አለባቸው::

(27) 27. አላህም ለባሮቹ ሁሉ ሲሳይን በዘረጋ ኖሮ በምድር ውስጥ ሁሉም ወሰን ባለፉ ነበር:: ግን የሚፈልገውን በልክ ያወርዳል:: እርሱ በባሮቹ ውስጠ አዋቂ፤ ተመልካች ነውና::

(28) 28. አላህ ያ ተስፋ ከቆረጡ በኋላ ዝናብን የሚያወርድ ችሮታውንም የሚዘረጋ ነው:: እርሱም ረዳቱና ምስጉኑ ነውና::

(29) 29. ሰማያትንና ምድርን መፍጠሩ ከተንቀሳቃሽም በሁለቱ ውስጥ የበተነውን ፍጡር መፍጠሩ ከአስደናቂ ምልክቶቹ ከፊሎቹ ናቸው:: እርሱም በሚፈልግ ጊዜ እነርሱን በመሰብሰብ ላይ ቻይ ነው::

(30) 30. (ሰዎች ሆይ!) ማንኛዉም መከራ (ያገኛችሁ ነገር) እጆቻችሁ በሰሩት ኃጢአት ምክንያት ብቻ ነው:: ብዙውንም ይቅር ይላል::

(31) 31. (ሰዎች ሆይ!) እናንተ በምድር ውስጥ የምትሳኑን (አምላጮች) አይደላችሁም:: ለእናንተም ከአላህ ሌላ ወዳጅም ሆነ ረዳት ምንም የላችሁም::

(32) 32. በባህር ላይ እንደ ጋራዎች ሆነው ተንሻላዮቹ መርከቦችም ከአስደናቂ ምልክቶቹ ናቸው::

(33) 33. ቢፈልግ ንፋሱን የረጋ ያደርገዋል:: ከዚያም መርከቦች በባህሩ ጀርባ ላይ የረጉ ይሆናሉ:: በዚህ ውስጥ በጣም ታጋሽ፤ አመስጋኝ ለሆኑ ሁሉ በእርግጥም ብዙ ተዓምራት አሉ::

(34) 34. ወይም ተሳፋሪዎች በሰሩት ኃጢአት ምክንያት እነርሱን በባህሩ በማስመጥ ያጠፋቸዋል:: ከብዙ ጥፋቶችም ይቅርታ ያደርጋል።

(35) 35. ከእነርሱ መካከል እነዚያን በአናቅጻችን የሚከራከሩትን ሰዎች ለማወቅ (ያጠፋቸዋል):: ለእነርሱም ከእርሱ ሌላ ምንም መሸሻ የላቸዉም::

(36) 36. (ሰዎች ሆይ!) የተሰጣችሁት ነገር ሁሉ የቅርቢቱ ሕይወት መጠቃቀሚያ ብቻ ነው:: በአላህ ዘንድ ያለው ምንዳ ግን ለእነዚያ በትክክል በእሱ ላመኑትና በጌታቸው ላይ ብቻ ለሚመኩት ሁሉ በላጭና ሁልጊዜ ነዋሪ ነው::

(37) 37. ለእነዚያም ታላላቅ ሃጢያቶችንና ዝሙትን የሚርቁ፤ በተቆጡም ጊዜ የሚምሩ ለሆኑት፤

(38) 38. ለእነዚያም የጌታቸውን ጥሪ ለተቀበሉት፤ ሶላትንም ላዘወተሩት፤ በነገራቸው ላይም በመካከላቸው መመካከር ልምዳቸው ለሆነው፤ ከሰጠናቸዉም ሲሳይ ለሚለግሱት፤

(39) 39. ለእነዚያም በደል በደረሰባቸው ጊዜ በመሰሉ የሚመልሱ ለሆኑት (በላጭና ነዋሪ ነው)::

(40) 40. የመጥፎ ነገሮች ሁሉ ዋጋው ተመሳሳዩ መጥፎ ነው:: ይቅር ያለና ያሳመረ ሰው ደግሞ ምንዳው በአላህ ላይ ብቻ ነው:: እርሱ በደለኞችን አይወድምና::

(41) 41. እነዚያ ከተበደሉ በኋላ በመሰሉ የተበቀሉ በእነርሱ ላይ ምንም የወቀሳ መንገድ የለባቸዉም::

(42) 42. የወቀሳ መንገዱ በእነዚያ ሰዎችን በሚበድሉት እና በምድር ውስጥም ያለ ህግ ወሰንን በሚያልፉት ሰዎች ላይ ብቻ ነው:: እነዚያ ለእነርሱ አሳማሚ ቅጣት አለባቸው::

(43) 43. የታገሰና ምህረት ያደረገ፤ ይህ ተግባር በእጅጉን ተፈላጊ ከሆኑ ነገሮች አንዱ ነው::

(44) 44. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አላህ የሚያጠመውን ሰው ከእርሱ ማጥመም በኋላ ለእርሱ ምንም ወዳጅ የለዉም:: በደለኞችም ቅጣትን ባዩ ጊዜ «ለመመለስ መንገድ አለን?» የሚሉ ሲሆኑ ታያቸዋለህ::

(45) 45. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከውርደት የተነሳ ፈሪዎች ሆነው በዓይን ስርቆት ወደ እሳት እያስተዋሉ በእርሷ ላይ የሚቀርቡ ሁነው ታያቸዋለህ:: እነዚያም በአላህ ያመኑት፡- «በእርግጥ ከሳሪዎች ማለት እነዚያ ነፍሶቻቸውንና ቤተሰቦቻቸውን በትንሳኤ ቀን የከሰሩት ናቸው» ይላሉ:: (ሙስሊሞች ሆይ!) አስተዉሉ:: በደለኞች በእርግጥ ዘወታሪ ስቃይ ውስጥ ናቸው::

(46) 46. ለእነርሱም ከአላህ ሌላ የሚረዷቸው ረዳቶች ምንም አልነበሯቸዉም:: አላህ የሚያጠመው ሰው ሁሉ ለእርሱ ወደ እውነት የሚመለስበት ምንም መንገድ የለዉም::

(47) 47. ያ ከአላህ ከመጣ መላሽ የሌለለው ቀን ከመምጣቱ በፊት ለጌታችሁ ታዘዙ:: በዚያ ቀን ለእናንተ ምንም መጠጊያም ሆነ መቃወም የላችሁም።

(48) 48. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ቢዞሩም (ወቀሳ የለብህም::) በእነርሱ ላይ ጠባቂ አድረገን አላክንህምና:: ባንተ ላይ ማድረስ እንጂ ሌላ የለብህም:: እኛም ሰውን ከእኛ የሆነን ጸጋ ባቀመስነው ጊዜ በእርሷ ይደሰታል:: እጆቻቸው ባስቀደሙት ኃጢአት ምክንያት መከራ ብትደርስባቸው ደግሞ ተስፋ ይቆርጣሉ:: ሰው በጣም ውለታን ከሓዲ ነውና::

(49) 49. የሰማያትና የምድር ንግስና የአላህ ብቻ ነው:: የሚፈልገውን ይፈጥራል:: ለሚፈልገው ሴቶችን ልጆች ይሰጣል:: ለሚፈልገዉም ወንዶችን ይሰጣል::

(50) 50. ወይም ወንዶችንና ሴቶችን አድርጎ ያጠናዳቸዋል:: የሚፈልገውንም መካን ያደርገዋል:: እርሱ ሁሉን አዋቂና ሁሉን ቻይ ነውና::

(51) 51. ሰውን አላህ በራዕይ ወይም ከግርዶሹ ወዲያ ወይም መልዕከተኛን በመላክና በፈቃዱ የሚፈልገውን ነገር የሚያወርድለት ቢሆን እንጂ በገሀድ ሊያናግረው ተገቢው አይደለም:: እርሱ የበላይና ጥበበኛ ነውና::

(52) 52. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ልክ እንደዚሁ ወደ አንተ ከትዕዛዛችን ሲሆን ሂወት የሆነውን (ቁርአን) አወረድነው:: መጽሐፉም ሆነ እምነቱ ምን እንደሆነ የምታውቅ አልነበርክም:: ግን ቁርኣንን ከባሮቻችን የምንሻውን ሰው በእርሱ የምንመራበት ብርሃን አደረግነው:: አንተም ወደ ቀጥተኛው መንገድ በእርግጥ ትመራለህ::

(53) 53. ወደዚያ በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የእርሱ ወደ ሆነው ወደ አላህ መንገድ (ትመራለህ):: ሙስሊሞች ሆይ! አስተውሉ:: ነገሮች ሁሉ ወደ አላህ ብቻ ይመለሳሉ::