26 - Ash-Shu'araa ()

|

(1) 1. ጣ፤ሲን፤ሚይም::

(2) 2. እነዚህ ግልጽ የሆነው መጽሀፍ አናቅጽ ናቸው::

(3) 3.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከሓዲያን አማኞች ባለ መሆናቸው በቁጭት ነፍስህን እንዳታጠፋ ይፈራልሃል (ያሰጋል)::

(4) 4. ብንሻ ኖሮ በእነርሱ ላይ ከሰማይ ተዓምርን እናወርድና አንገቶቻቸው (መሪዎቻቸው) ለእርሷ ተዋራጆች እናደርጋለን::

(5) 5. ከአር-ረህማን ዘንድ አዲስ የተወረደ ተግሳፅ አይመጣላቸዉም:: ከእርሱ የሚሸሹ ቢሆኑ እንጂ::

(6) 6. በእርግጥም አስተባበሉ:: የዚያም በእርሱ ይሳለቁበት የነበሩት ወሬዎች ፍጻሜ ይመጣባቸዋል::

(7) 7.ወደ ምድርም በውስጧ ከመልካም በቃይ ጎሳ ብዙን እንዳበቀልን አላዩምን።

(8) 8. በዚህ አስደናቂ ምልክት አለበት፤ አብዛኞቻቸዉም ትክክለኛ አማኞች አልነበሩም።

(9) 9. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህ በትክክል ሁሉን አሸናፊና አዛኝ ነው::

(10) 10. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህም ሙሳን «ወደ እነዚያ በደለኛ ህዝቦች ሂድ።» በማለት በጠራው ጊዜ የሆነውን አስታውስ።

(11) 11. «ወደ ፈርዖን ህዝቦች አላህን አይፈሩምን?»

(12) 12. ሙሳም «ጌታዬ ሆይ! እኔ ያስተባብሉኛል ብዬ እፈራለሁ።

(13) 13. «ልቤም ይጠባል፤ ምላሴም ይንተባተባል። ስለዚህ ወደ ሃሩንም ላክ።

(14) 14. «በተጨማሪም ለእነርሱም በእኔ ላይ (የደም) ወንጀል አላቸው:: ስለዚህ እንዳይገድሉኝም እፈራለሁ።» አለ።

(15) 15. አላህ አለ: «ተው! አይነኩህም ሁለታችሁም በተአምሮታችን ታጅባችሁ ሂዱ። እኛ ከናንተ ጋር ሁነን ሰሚዎች ነንና።

(16) 16. «ወደ ፈርዖንም ሂዱና። በሉትም: ‹እኛ የዓለማት ጌታ መልዕክተኞች ነን።

(17) 17. «‹የኢስራኢልን ልጆችም ከእኛ ጋር ልቀቅልን።›» (በሉት)

(18) 18. ፈርዖንም አለ፡ «ልጅ ሆንህ በእኛ ውስጥ አላሳደግንህምን? በእኛ ውስጥም ከዕድሜህ ብዙ ዓመታትን አልተቀመጥክምን?

(19) 19. «ያችን የሰራሃትን ስራስ አልሰራህምን? አንተ ከውለታ ቢሶች ነህ።» (አለ)

(20) 20. ሙሳም አለ፡ «ያን ጊዜ እኔም ከተሳሳቱት ሆኜ ሰራኋት።

(21) 21. «በፈራኋችሁም ጊዜ ከናንተ ሸሸሁ። ጌታዬም ለእኔ ጥበብን ሰጠኝ:: ከመልዕክተኞችም አደረገኝ:።

(22) 22. «ይህችም የኢስራኢልን ልጆች ባሪያ በማድረግህ በእኔ ላይ የምትመጻድቅባት ጸጋ ናት።»

(23) 23. ፈርዖን: «ሙሳ ሆይ! ላከኝ የምትለው የዓለማት ጌታ ምንድን ነው?» አለ።

(24) 24. ሙሳ፡- «የሰማያት የምድርና በመካከላቸዉም ያለው ፍጡር ሁሉ ጌታ ነው። የምታረጋግጡ ብትሆኑ ነገሩ ይህ ነው።» አለው።

(25) 25. ፈርዖንም ዙሪያውን ላሉት ሰዎች: «አትሰሙምን?» አለ።

(26) 26. ሙሳ፡- «ጌታችሁና የመጀመሪያዎቹ አባቶቻችሁም ጌታ ነው።» አለ።

(27) 27. ፈርዖን፡- «ያ ወደ እናንተ የተላከው መልዕክተኛችሁ በእርግጥ ዕብድ ነው።» አለ።

(28) 28. ሙሳ፡- «(አላህ) የምስራቅና የምዕራብ በመካከላቸዉም ያለው ነገር ሁሉ ጌታ ነው:: ታውቁ እንደሆናችሁ (እመኑበት)።» አለ።

(29) 29. ፈርዖን: «ከእኔ ሌላ አምላክን ብትይዝ በእውነቱ ከእስረኞቹ አደርግሃለሁ።» አለ።

(30) 30. ሙሳ፡- «ግልጽ የሆነ አስረጅ ባመጣም እንኳን?» አለው።

(31) 31. ፊርዓውን «እንግዲያውስ ከእውነተኞች እንደሆንክ አስረጁን አምጣው።» አለ።

(32) 32. በትሩንም ጣለ:: እርሷም ወዲያውኑ ግልጽ እባብ ሆነች::

(33) 33 እጁንም አወጣ እርሷም ወዲያውኑ ለተመልካቾች ነጭ (የምታበራ) ሆነች::

(34) 34. ፈርዖንም በዙሪያው ላሉት መማክርት አለ: «ይህ በእርግጥ አዋቂ ድግምተኛ ነው።

(35) 35. «ከምድራችሁ በድግምት ሊያወጣችሁ ይፈልጋልና ምንን ታዛላችሁ?» አላቸው።

(36) 36. እነርሱም አሉ: «እርሱንና ወንድሙን አቆያቸው:: ወደየከተሞቹ ሁሉ ሰብሳቢዎችን ላክ።

(37) 37. «በጣም አዋቂ ድግምተኞችን ሁሉ ያመጡልሃልና።» አሉ።

(38) 38. ድግምተኞችም በታወቀ ቀን ቀጠሮ ተሰበሰቡ::

(39) 39. ለሰዎቹም ተባለ: «እናንተ ተሰብስባችኋልን?

(40) 40. «ድግምተኞቹን እነርሱ አሸናፊዎች ቢሆኑ እንከተል ዘንድ» ተባለ።

(41) 41. ድግምተኞቹም በመጡ ጊዜ ለፈርዖን: «እኛ አሸናፊዎች ብንሆን ለእኛ ዋጋ አለን?» አሉት።

(42) 42. እርሱም( ፈርዖን) «አዎን። እናንተ ያን ጊዜ እኔ ዘንድ ከባለሟሎቹ ትሆናላችሁ።» አላቸው።

(43) 43. ሙሳ ለእነርሱ: «የምትጥሉትን ጣሉ።» አላቸው።

(44) 44. ገመዶቻቸውንና በትሮቻቸውንም ጣሉ:: «በፈርዖንም ክብር ይሁንብን። እኛ በእርግጥ አሸናፊዎች ነን።» አሉ።

(45) 45. ሙሳም ብትሩን ጣለ:: ወዲያዉም እርሷ የሚያስመስሉትን ሁሉ ትውጣለች::

(46) 46. ከዚያም ድግምተኞቹ ሰጋጆች ሆነው ሱጁድ አደረጉ(ወረዱ)

(47) 47. እነርሱም አሉ፡- «በዓለማት ጌታ አመንን።

(48) 48. «በሙሳና በሃሩን ጌታ (አመንን)።» (አሉ)

(49) 49. ፈርዖንም «ለእናንተ ሳልፈቅድላችሁ በፊት ለእርሱ አመናችሁን? እርሱ ያ ድግምትን ያስተማራችሁ ታላቃችሁ ነው። ወደፊትም በእርግጥ የሚያገኛችሁን ታውቃላችሁ:: እጆቻችሁንና እግሮቻችሁን ቀኝና ግራን (በማናጋት) በማፈራረቅ እቆራርጣችኋለሁ:: ሁላችሁንም እሰቅላችኃለሁ።» አለ።

(50) 50. እነርሱም አሉ፡- «ጉዳት የለብንም እኛ ወደ ጌታችን ተመላሾች ነን።

(51) 51. «እኛ የምዕምናን መጀመሪያ በመሆናችን ጌታችን ኃጢአቶቻችንን ለኛ ሊምር እንከጅላለን።»

(52) 52. ወደ ሙሳም «ባሮቼን ይዘህ ሌሊት ሂድ እናንተ የሚከተሏችሁ ናችሁና።» ስንል ላክን።

(53) 53. ፈርዖንም በየከተሞቹ ሰብሳቢዎችን (እንዲህ ሲል) ላከ::

(54) 54. «እነዚህ ጥቂቶቹ ቡድኖች ናቸው።

(55) 55. «እነርሱም ለእኛ አስቆጪዎች ናቸው።

(56) 56. «እኛም ብዙዎች ጥንቁቆች ነን።» አለ።

(57) 57. አወጣናቸዉም፤ ከአትክልቶችና ከምንጮች::

(58) 58. ከድልቦችም ከመልካም መቀመጫዎችም፤

(59) 59. ልክ እንደዚሁ ለኢስራኢል ልጆች አወረስናትም::

(60) 60. ጸሐይዋ ስትወጣም ተከተሏቸው::

(61) 61. ሁለቱ ቡድኖችም በተያዩ ጊዜ የሙሳ ጓዶች «እኛ (የፈርዖን ሰዎች) የሚደርሱብን ነን።» አሉ።

(62) 62. ሙሳ «በፍፁም! ጌታዬ ከእኔ ጋር ነው። በእርግጥ ይመራኛል።» አለ።

(63) 63. ወደ ሙሳም «ባህሩን በበትርህ ምታው።» ስንል ላክንበት:: ከዚያ መታውና ተከፈለ፤ ክፍሉም ሁሉ እንደ ታላቅ ጋራ ሆነ::

(64) 64. እዚያም ዘንድ ሌሎችን አቀረብን::

(65) 65. ሙሳንና ከእርሱ ጋር ያሉትንም ሰዎች ሁሉንም አዳን::

(66) 66. ከዚያም ሌሎቹን አሰመጥን::

(67) 67. በዚህ ውስጥ ታላቅ ተዐምር አለበት፤ አብዛሀኞቻቸዉም ትክክለኛ አማኞች አልነበሩም።

(68) 68. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህ አላህ እርሱ አሸናፊና አዛኝ ነው::

(69) 69. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በእነርሱም (በህዝቦችህ) ላይ የኢብራሂምን ወሬ አንብብላቸው::

(70) 70. ለአባቱና ለህዝቦቹ «ምንን ትገዛላችሁ?» ባለ ጊዜ።

(71) 71. «ጣኦታትን እንገዛለን:: እርሷንም በመገዛት ላይ እንቆያለን።» አሉ።

(72) 72. ኢብራሂም አለ፡- «በጠራችኋቸው ጊዜ ይሰሟችኋልን?

(73) 73. «ወይስ ይጠቅሟችኋልን? ወይስ ይጎዷችኋልን?»

(74) 74. «የለም! ነገር ግን አባቶቻችን ልክ እንደዚሁ ሲሰሩ አገኘን(ና እኛም እነርሱን እንከተላለን።») አሉት።

(75) 75. እርሱም አለ: «ትገዙት የነበራችሁትን አስተዋላችሁን?

(76) 76. «እናንተም የቀድሞዎቹ አባቶቻችሁም እየተገዛችሁት ያለውን።

(77) 77. «እነርሱም ጣኦቶቹ ለእኔ ጠላቶች ናቸው:: የዓለማት ጌታ ብቻ ሲቀር:: እርሱማ ወዳጄ ነው።

(78) 78. «እርሱ ያ የፈጠረኝ ነው:: እርሱም ይመራኛል።

(79) 79. «ያም እርሱ የሚያበላኝና የሚያጠጣኝም ነው።

(80) 80. «በታመምኩም ጊዜ እርሱ ያሽረኛል።

(81) 81. «ያም የሚገድለኝ ከዚያም ህያው የሚያደርገኝ ነው።

(82) 82. «ያም በፍርዱ ቀን ኃጢአቴን ሊምርልኝ የምከጅለው ነው።» (አለ)

(83) 83. (ኢብራሂምም) «ጌታዬ ሆይ! እውቀትን ስጠኝ በደጋጎቹም ሰዎች አስጠጋኝ።

(84) 84. «በኋለኞቹም ህዝቦች ውስጥ ለእኔ መልካም ዝናን አድርግልኝ።

(85) 85. «የጸጋይቱን ገነት ከሚወርሱትም ሰዎች አድርገኝ።

(86) 86. «ለአባቴም ኃጢያቱን ማር። እርሱ ከተሳሳቱት ነበርና።

(87) 87. «በሚቀሰቀሱበት ቀንም አታዋርደኝ።

(88) 88. «ገንዘብም ሆነ ልጆች በማይጠቅሙበት ቀን፤

(89) 89. «ወደ አላህ በንጹህ ልብ የመጣ ቢሆን አንጂ።»

(90) 90. ገነትም ለጥንቁቆቹ በምትቀረብበት ቀን፤

(91) 91. ገሀነምም ለጠማሞቹ በምትገለጽበት ቀን::

(92) 92. ለእነርሱም «እነዚያ ትገዟቸው የነበራችሁት የት ናቸው?

(93) 93. « ከአላህ ሌላ ሲሆኑ (ትገዟቸው የነበራችሁ) ይረዱዋችኋልን? ወይስ ለራሳቸው ይረዳሉን?» በሚባል ቀን።

(94) 94. በውስጧም እነርሱና ጠማሞች በፊቶቻቸው ተጥለው ይንከባለላሉ::

(95) 95 የሰይጣንም ሰራዊቶች መላዉም ይጣላሉ::

(96) 96. እነርሱም በርሷ ውስጥ የሚከራከሩ ሆነው ይላሉ:

(97) 97. «በአላህ እንምላለን፤ እኛ በግልጽ መሳሳት ውስጥ ነብርን።

(98) 98. «በዓለማት ጌታ ባስተካከልናችሁ ጊዜ።

(99) 99. «አመጸኞቹም እንጅ ሌላ አላሳሳተንም።

(100) 100. «ከአማላጆችም ለኛ ምንም የለንም።

(101) 101. «አዛኝ ወዳጅም የለንም።

(102) 102 «ለእኛም አንዲት ጊዜ እንኳን የመመለስ እድል በኖረንና ከትክክለኛ አማኞች በሆን እንመኛለን።» ይላሉ።

(103) 103. በዚህ ውስጥ አስደናቂ ግሣጼ አለበት:: አብዛሀኞቻቸዉም ትክክለኛ አማኞች አልነበሩም::

(104) 104. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህም እርሱ በእርግጥ ሁሉን አሸናፊዉና አዛኙ ነው::

(105) 105. የኑህ ህዝቦች መልዕክተኞችን አስተባበሉ::

(106) 106. ወንድማቸው ኑህ ለእነርሱ ባላቸው ጊዜ፡ «አትጠነቀቁምን?

(107) 107. «እኔ ለእናንተ ታማኝ መልዕክተኛ ነኝ።

(108) 108. «አላህንም ፍሩ ታዘዙኝም።

(109) 109. «በእርሱም ላይ ምንም ዋጋ አልጠይቃችሁም:: ዋጋዬ ከዓለማት ጌታ ብቻ እንጂ በሌላ ላይ አይደለም።

(110) 110. «አላህንም ፍሩ። ታዘዙኝም።»

(111) 111. እነርሱም «ወራዶቹ ብቻ የተከተሉህ ሆነህ ላንተ እናምናለን?» አሉት።

(112) 112. እርሱም አላቸው፡- «ይሰሩት በነበሩት ነገር ምን ዕውቀት አለኝና?

(113) 113. «ምርመራቸው በጌታዬ ላይ እንጅ በሌላ ላይ አይደለም:: ብታውቁ ኖሮ ይህንን ትረዱት ነበር።

(114) 114. «እኔ አማኞችን አባራሪ አይደለሁም።

(115) 115. «እኔም እኮ ግልጽ አስፈራሪ እንጂ ሌላ አይደለሁም።» (አለ)

(116) 116. «ኑህ ሆይ! ከምትለው ባትከለከል በእርግጥ ከሚወገሩት ትሆናለህ።» አሉት።

(117) 117. እርሱም አለ፡- «ጌታየ ሆይ! ህዝቦቼ አስተባበሉኝ።

(118) 118. «በእኔና በእነርሱም መካከል ተገቢ ፍርድን ፍረድ:: ከእነርሱ አድነኝም:: ከእኔ ጋር ያሉትን አማኞችም አድን።»

(119) 119. እርሱንም ሆነ ከእርሱ ጋር ያሉትን ሁሉ በተሞላው መርከብ ውስጥ አዳንን::

(120) 120. ከዚያም በኋላ ቀሪዎቹን አሰመጥን።

(121) 121. በዚህ ውስጥ ታላቅ ግሣጼ አለበት፤ አብዛሀኞቻቸዉም ትክክለኛ አማኞች አልነበሩም::

(122) 122. ጌታህም እርሱ በእርግጥ ሁሉን አሸናፊዉና አዛኙ ነው::

(123) 123. ዓድ መልዕክተኞችን አስተባበለች፤

(124) 124. ወንድማቸው ሁድ ለእነርሱ ባላቸው ጊዜ: «አትጠነቀቁምን?

(125) 125. «እኔ ለእናንተ ታማኝ መልዕክተኛ ነኝ።

(126) 126. «አላህን ብቻ ፍሩ ታዘዙኝም።

(127) 127. «በእርሱም ላይ ምንም ዋጋ አለምናችሁም:: ዋጋዬ በዓለማት ጌታ ላይ ብቻ እንጅ በሌላ ላይ አይደለም።

(128) 128. «የምትጫወቱ ሆናችሁ በከፍተኛ ስፍራ ሁሉ ላይ ምልክት ትገነባላችሁን?

(129) 129. «የውሃ ማጠራቀሚያዎችንና ህንፃዎችንም ለዘላለም መኖርን የምትከጅሉ ሆናችሁ ትሰራላችሁን?

(130) 130. «በቀጣችሁም ጊዜ ጨካኞች ሆናችሁ ትቀጣላችሁን?

(131) 131. «አላህንም ፍሩ። ታዘዙኝም።

(132) 132. «ያንንም በምታውቁት ጸጋ ያጣቀማችሁን ጌታን (አላህን) ፍሩ።

(133) 133. «በእንስሳዎችና በልጆችም ያጣቀማችሁ።

(134) 134. «በአትክልቶችና በምንጮችም ያጣቀማችሁን ጌታን (አላህን) ፍሩ።

(135) 135. «እኔ በእናንተ ላይ የታላቅን ቀን ቅጣት እፈራለሁና።»

(136) 136. እነርሱም አሉ: «ብትገስጽም ወይም ከገሳጮች ባትሆንም በእኛ ላይ እኩል ነው።

(137) 137. «(ያለንበትን አንለቅም)። ይህ የፊተኞቹ ሰዎች መንገድ እንጂ ሌላ አይደለም።

(138) 138. «እኛም የምንቀጣ አይደለንም።» አሉ።

(139) 139. አስተባበሉትም፤ አጠፋናቸዉም፤ በዚህም ውስጥ እርግጠኛ ግሣጼም አለበት:: አብዛኞቻቸዉም ምዕምናን አልነበሩም::

(140) 140. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህም እርሱ በእርግጥ አሸናፊውና አዛኙ ነው::

(141) 141. የሰሙድ ህዝቦች መልዕክተኞችን አስተባበሉ::

(142) 142. ወንድማቸው ሷሊህ ለእነርሱ ባላቸው ጊዜ: «አትጠነቀቁምን?

(143) 143. «እኔ ለእናንተ ታማኝ መልዕክተኛ ነኝ።

(144) 144. «አላህን ፍሩ ታዘዙኝም።

(145) 145. «በእርሱም ላይ ምንም ዋጋ አልለምናችሁም:: ዋጋዬ በዓለማት ጌታ ላይ ብቻ እንጂ በሌላ ላይ አይደለም።

(146) 146. «በዚያ እዚህ ባለው ጸጋ ውስጥ የረካችሁ ሆናችሁ ትቀራላችሁን?

(147) 147. «በአትክልቶችና በምንጮች ውስጥ

(148) 148. «በአዝመራዎችም ፍሬዋ የበሰለ በሆነች ዘንባባም ውስጥ ትቀራላችሁን?

(149) 149. «ብልሆች ሆናችሁ ከጋራዎች ቤቶችንም ትጠርባላችሁ።

(150) 150. «አላህንም ፍሩ፤ ታዘዙኝም።

(151) 151. «የወሰን አላፊዎችንም ትዕዛዝ አትከተሉ።

(152) 152. «የእነዚያን በምድር ላይ የሚያጠፉትንና የማያበጁትን (ትዕዛዝ አትከተሉ)።» (አለ)

(153) 153. እነርሱም አሉ: «አንተ በብዙ ከተደገመባቸው ሰዎች ብቻ ነህ።

(154) 154. «አንተ ብጤያችን ሰው እንጂ ሌላ አይደለህም። ከእውነተኞችም ከሆንክ ተዐምርን አምጣ።» (አሉ)

(155) 155. እርሱም አለ: «ይህች ግመል ናት:: ለእርሷ የመጠጥ ፋንታ አላት:: ለእናንተም የታወቀ ቀን ፋንታ አላችሁ፤

(156) 156. «በክፉም አትንኳት የታላቅ ቀን ቅጣት ይይዛችኋልና።»

(157) 157. ወጓትም:: ወዲያው ተጸፃቾች ሆነው አነጉ::

(158) 158. ቅጣትም ያዛቸው በዚህም ውስጥ አያሌ ግሣጼ አለበት:: አብዛኞቻቸዉም አማኞች አልነበሩም::

(159) 159. ጌታህም እርሱ በእርግጥ ሁሉን አሸናፊውና አዛኙ ነው።

(160) 160. የሉጥ ህዝቦች መልዕክተኞችን አስተባበሉ::

(161) 161. ወንድማቸው ሉጥ ለእነርሱ ባለ ጊዜ: «አትጠነቀቁምን?

(162) 162. «እኔ ለእናንተ ታማኝ መልዕክተኛ ነኝ።

(163) 163. «አላህንም ፍሩ ታዘዙኝም።

(164) 164. «በእርሱም ላይ ምንም ዋጋ አለምናችሁም:: ዋጋዬ በዓለማት ጌታ ላይ እንጅ በሌላ ላይ አይደለም::

(165) 165. «ከዓለማት ሰዎች መካከል የተለየ ወንዶችን ትገናኛላችሁን?

(166) 166. «ከሚስቶቻችሁም ጌታችሁ ለእናንተ የፈጠረላችሁን ትተዋላችሁን? በእውነት እናንተ ወሰን አላፊዎች ህዝቦች ናችሁ።» (አለ)

(167) 167. እነርሱም አሉ: «ሉጥ ሆይ! ከዚህ ነገርህ ባትከለከል በእርግጥ በሀይል ከአገር ከሚወጡት ትሆናለህ።»

(168) 168. እርሱም አለ: «እኔ ስራችሁን ከሚጠሉት ሰዎች አንዱ ነኝ።

(169) 169. «ጌታዬ ሆይ! እኔንም ሆነ ቤተሰቦቼን እኒህ ህዝቦች ከሚሰሩት ስራ ቅጣት አድነን።»

(170) 170. እርሱንም ሆነ ቤተሰቦቹንም በጠቅላላ አዳንናቸው።

(171) 171. በቀሪዎቹ ውስጥ የሆነች አሮጊት ስተቀር (እርሷ ግን ጠፋች)::

(172) 172. ከዚያም ሌሎቹን አጠፋን።

(173) 173. በእነርሱም ላይ የድንጋይን ዝናብን አዘነብንባቸው:: የተስፋራሪዎችም ዝናብ ከፋ::

(174) 174. በዚህ ውስጥ አስደናቂ ተዐምር አለበት:: አብዛኞቻቸዉም ምዕምናን አልነበሩም::

(175) 175. ጌታህ እርሱ አሸናፊውና አዛኙ ነው።

(176) 176. የአይካ ሰዎች መልዕክተኞችን አስተባበሉ::

(177) 177. ወንድማቸው ሹዐይብ ለእነርሱ ባላቸው ጊዜ: «አትጠነቀቁምን?

(178) 178. «እኔ ለእናንተ ታማኝ መልዕክተኛ ነኝ።

(179) 179. «አላህን ፍሩ፤ ታዘዙኝም።

(180) 180. «በእርሱም ላይ ምንም ዋጋ አልጠይቃችሁም፤ ዋጋዬ በዓለማት ጌታ ላይ እንጂ በሌላ ላይ አይደለም።

(181) 181. «ስፍርንም ሙሉ:: ከአጎዳዮችም አትሁኑ።

(182) 182. «በትክክለኛ ሚዛንም መዝኑ።

(183) 183. «ሰዎችንም ነገሮቻቸውን አታጉድሉባቸው:: በምድርም ላይ አጥፊዎች ሆናችሁ አታበላሹ።

(184) 184. «ያንንም የፈጠራችሁን የቀድሞዎቹንም ፍጡሮች የፈጠረውን ፍሩ።» (ባለ ጊዜ የሆነውን አስታውስ)

(185) 185. እነርሱም አሉ: «ሹዓይብ ሆይ! አንተ በብዛት ከተደገመባቸው ሰዎች አንዱ ነህ።

(186) 186. «አንተም ብጤያችን ሰው እንጂ ሌላ አይደለህም:: እነሆ ከውሸታሞች ነህ ብለን እንጠረጥርሃለን፤

(187) 187. «ከእውነተኞችም እንደሆንክ በእኛ ላይ ከሰማይ ቁራጭን ጣልብን።» (አሉ)

(188) 188. «ጌታዬ የምትሰሩትን ሁሉ አዋቂ ነው።» አላቸው።

(189) 189. አስተባበሉትም የጥላይቱ ቀን ቅጣትም ያዛቸው፤ እርሱ የከባድ ቀን ቅጣት ነበርና::

(190) 190. በዚህ ውስጥ አስደናቂ ተዐምር አለበት:: አብዛዛቻቸዉም አማኞች አልነበሩም::

(191) 191. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህም እርሱ በእርግጥ አሸናፊዉንና አዛኙ ነው::

(192) 192. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እርሱም (ቁርኣን) በእርግጥ ከዓለማት ጌታ የተወረደ ነው::

(193) 193. እርሱን ታማኙ መንፈስ ጂብሪል አወረደው::

(194) 194. ከአስፈራሪዎች ነብያት ትሆን ዘንድ በልብህ ላይ አወረደው፤

(195) 195. ግልጽ በሆነ ዐረብኛ ቋንቋ፤ (አወረደው)

(196) 196. እርሱም (ቁርኣን) በቀድሞዎቹ መጽሐፍት ውስጥ የተወሳ ነው::

(197) 197. የኢስራኢል ልጆች ሊቃውንት የሚያውቁት መሆኑ ለእነርሱ (ለመካ ከሓዲያን) ምልክት አይሆናቸዉም?

(198) 198. ከአዕጀሞች ባንዱ ላይ ባወረድነዉም ኖሮ

(199) 199. በእነርሱ ላይ ቢያነበዉም በእርሱ አማኞች አይሆኑም ነበር::

(200) 200. እንድዚሁ ማስተባበልን በተንኮለኞች ልቦች ውስጥ አስገባነው::

(201) 201. አሳማሚ ቅጣትን እስከሚያዩ ድረስ በእርሱ አያምኑም::

(202) 202. እነርሱ የማያውቁ ሲሆኑ ቅጣቱ ድንገት እስከሚመጣባቸዉም ድረስ (አያምኑም)::

(203) 203. በመጣባቸው ጊዜ: «እኛ የምንቆይ ነን?» እስከሚሉም (አያምኑም)

(204) 204. በቅጣታችን ያቻኩላሉን?

(205) 205. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ! ) አየህን? ብዙ ዓመታትን ብናጣቅማቸው::

(206) 206. ከዚያም ያ ይስፈራሩበት የነበሩት ቢመጣባቸው

(207) 207. ይጣቀሙበት የነበሩት ሁሉ ከእነርሱ ምንም አያብቃቃቸዉም::

(208) 208. አንዲትንም ከተማ ለእርሷ አስፈራሪዎች ያሏት (እና ያስተባበለች) ሆና እንጂ አላጠፋንም::

(209) 209. ይህች ግሣጼ ናት:: በዳዮችም አልነበርንም::

(210) 210. ሰይጣናትም እርሱን ቁርኣንን አላወረዱትም::

(211) 211. ለእነርሱም አይገባቸዉም፤ አይችሉምም::

(212) 212. እነርሱ የመላዕክትን ንግግር ከመስማት የተከለከሉ ናቸው።

(213) 213. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከአላህም ጋር ሌላን አምላክ አትገዛ:: ከሚቀጡት ትሆናለህና::

(214) 214. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ቅርቦች ዘመዶችህንም አስጠንቅቅ::

(215) 215. (ሙሐመድ ሆይ!) ከምዕምናንም ለተከተሉህ ሰዎች ክንፍህን ዝቅ አድርግ ልዝብ ሁን::

(216) 216. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እንቢ ካሉህ «እኔ ከምትሰሩት ወንጀል ሁሉ ንጹህ ነኝ።» በላቸው።

(217) 217. (ሙሐመድ ሆይ!) አሸናፊና አዛኝ በሆነው ጌታህ ላይም ተጠጋ::

(218) 218. በዚያ ለሶላት በምትቆም ጊዜ በሚያይህ::

(219) 219. በሰጋጆች ውስጥ መዘዋወርህንም (በሚያየው ጌታህ ላይ ተጠጋ::)

(220) 220. እነሆ እርሱ (አላህ) ሁሉ ሰሚና ሁሉን አዋቂ ነውና።

(221) 221. ሰይጣናት በማን ላይ እንደሚወርዱ ልንገራችሁን?

(222) 222. በውሸታም ኃጢአተኛ ሁሉ ላይ ይወርዳሉ::

(223) 223. የሰሙትን ወደ ጠንቋዮች ይጥላሉ:: አብዛኞቻቸዉም ውሸታሞች ናቸው::

(224) 224. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ባለ ቅኔዎችንም ጠማማዎች ይከተሏቸዋል::

(225) 225. እነርሱ (በንግግር) ሸለቆ ሁሉ የሚዋልሉ መሆናቸውን አታይምን?

(226) 226. እነርሱም የማይሰሩትን ነገር የሚናገሩ መሆናቸውን አታይምን::

(227) 227. እነዚያ ያመኑና መልካም ስራዎችን የሰሩ አላህን በብዛት ያወሱ ከተበደሉም በኋላ (በቅኔ) የተከላከሉ ሲቀሩ፤ (እነርሱ አይወቀሱም)። እነዚያም የበደሉ ከሞቱ በኋላ እንዴት ያለን መመለስ እንደሚመለሱ በእርግጥ ያውቃሉ::