32 - As-Sajda ()

|

(1) 1. አሊፍ፤ ላም፤ ሚይም፤

(2) 2. የመጽሐፉ መወረድ ጥርጥር የለበትም:: የወረደዉም ከዓለማቱ ጌታ ነው::

(3) 3. ይልቁንም «ቀጠፈው» ይላሉን? አይደለም:: (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እርሱ ከጌታህ የሆነ እውነት ነው:: በእርሱ ካንተ በፊት ከአስፈራሪ ነቢይ ያልመጣባቸውን ሕዝቦች በእርሱ ልታስፈራራበት ያወረደልህ ነው:: እነርሱ ሊመሩ ይከጀላልና::

(4) 4. አላህ ያ! ሰማያትንና ምድርን በመካከላቸውም ያለውን ሁሉ በስድስት ቀናት ውስጥ የፈጠረ ከዚያም ለክብሩ በሚስማማ መልኩ በዐርሹ ላይ ከፍ ያለ ነው:: ከእርሱ ሌላ ለእናንተ ወዳጅም አማላጅም ምንም የላችሁም:: አትገሰጹምን?

(5) 5. ነገሩን ሁሉ ከሰማይ ወደ ምድር ያዘጋጃል፤ ከዚያም ከምትቆጥሩት (ዘመን) ልኩ ሺህ ዓመት በሆነ ቀን ውስጥ ወደ እርሱ ይወጣል::

(6) 6. ይህንን ያደረገው ሩቁንም ቅርቡንም ሁሉ አዋቂው፤ ሁሉን አሸናፊና አዛኙ ጌታ ነው::

(7) 7. ያ የፈጠረውን ነገር ሁሉ ያሳመረው:: የሰውንም ፍጥረት ከጭቃ የጀመረው ነው::

(8) 8. ከዚያም ዘሮቹን ከተንጣለለ ከደካማ ውሃ የፈጠረ ነው::

(9) 9. ከዚያም ቅርጹን አስተካከለው:: በእርሱ ውስጥም ከመንፈሱ ነፍስ ዘራበት:: ለናንተም ጆሮዎችን ዓይኖችንና ልቦችንም አደረገላችሁ። በጣም ጥቂትን ብቻ ታመሰግናላችሁ።

(10) 10. «በምድርም ውስጥ በስብሰን በጠፋን ጊዜ እኛ በአዲስ መፈጠር ውስጥ እንሆናለን?» አሉ:: በእውነቱ እነርሱ በጌታቸው መገናኘት ከሓዲያን ናቸው::

(11) 11. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «በእናንተ ላይ የተወከለው መልአከ ሞት ይገድላችኋል:: ከዚያም ወደ ጌታችሁ ትመለሳላችሁ።» በላቸው።

(12) 12. አመጸኞችም በጌታቸው ዘንድ ራሶቻቸውን ያቀረቀሩ ሆነው፡‐ «ጌታችን ሆይ! አየን። ሰማንም። መልካምን እንሠራለንና (ወደ ምድረ ዓለም) መልሰን እኛ አረጋጋጮች ነን» የሚሉ ሲሆኑ ብታይ ኖሮ( አስደንጋጭን ነገር ታይ ነበር)

(13) 13 በሻንም ኖሮ ነፍስን ሁሉ ቅንነቷን(እምነቷን) በሰጠናት ነበር:: ግን ገሀነምን ከአጋንንትና ከሰዎች የተሰበሰቡ ሆነው በእርግጥ እሞላለሁ ማለት ቃሉ ከእኔ ተረጋግጧል::

(14) 14. ይህንንም ቀናችሁን መገናኘትን በመርሳታችሁ ምክንያት ቅጣትን ቅመሱ! እኛ ተውናችሁ። ትሰሩት በነበራችሁትም ጥፋት ዘውታሪን ቅጣት ቅመሱ ይባላሉ::

(15) 15. በአናቅጻችን የሚያምኑት እነዚያ በእርሷ በተገሰጹ ጊዜ ሰጋጆች ሆነው የሚወድቁትና እነርሱም የማይኮሩ ሆነው በጌታቸው ምስጋና (ተጎናጽፈው) የሚያወድሱት ሰዎች ብቻ ናቸው። {1}
{1} እዚህጋ ሱጁዱትላዋ (የንባብ ሱጁድ) መድረግ ያስፈልጋል። በሶላት ውስጥም ከሶላት ውጪም መድረጉ ይወደዳል።

(16) 16. ጌታቸውን ለመፍራትና ለመከጀል የሚጠሩት ሆነው ጎኖቻቸው ከመጋደሚያ ቦታዎቻቸው ይርቃሉ:: ከሰጠናቸዉም ጸጋ ይለግሳሉ::

(17) 17. ይሰሩት በነበሩት ለመመንዳት ከዓይኖች መርጊያ ለእነርሱ የተደበቀላቸውን ጸጋ ማንኛይቱም ነፍስ አታውቅም::

(18) 18. አማኝ የሆነ ሰው አመጸኛ እንደሆነ ሰው ነውን? አይስተካከሉም::

(19) 19. እነዚያ ያመኑና መልካሞችን የሰሩማ ለነሱ ይሰሩት በነበሩት ምክንያት መስተንግዶ ሲሆኑ መኖሪያ ገነቶች አሏቸው::

(20) 20. እነዚያ ያመጹትማ መኖሪያቸው እሳት ናት:: ከእርሷ መውጣትን በፈለጉ ቁጥር በእርሷ ውስጥ ይመለሳሉ ለእነርሱም «ያንን በእርሱ ታስተባብሉበት የነበራችሁትን የእሳት ቅጣት ቅመሱ» ይባላሉ።

(21) 21. ይመለሱ ዘንድ ከትልቁ ቅጣት በፊት (በዚህ ዓለም) ትንሹን ቅጣት በእርግጥ እናቀምሳቸዋለን::

(22) 22. በጌታዉም አናቅጽ ከተገሰጸና ከዚያም ከተዋት ሰው ይበልጥ በደለኛ ማነው? (የለም) እኛ ከተንኮለኞቹ ሁሉ ተበቃዮች ነን::

(23) 23.ሙሳን መጽሐፍን በእርግጥ ሰጠነው:: (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እርሱን ከመገናኘትህም በመጠራጠር ውስጥ አትሁን:: ለኢስራኢል ልጆችም መሪ አደረግነው::

(24) 24. በታገሱና በተዓምራታችን የሚያረጋግጡ በሆኑም ጊዜ ከእነርሱ በትዕዛዛችን የሚመሩ መሪዎችን አደረግን::

(25) 25. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህ በዚያ ይለያዩበት በነበሩት ነገር ሁሉ በትንሳኤ ቀን በመካከላቸው በፍርድ ይለያል::

(26) 26. ከክፍለ ዘመናት ሰዎች ብዙዎችን ያጠፋን መሆናችን በመኖሪያዎቻቸው የሚሄዱ ሲሆኑ እነርሱ አልተገለጸላቸዉምን? በዚህ ውስጥ አያሌ ምልክቶች አሉበት:: አይሰሙምን?

(27) 27. እኛ ውሃን ወደ ደረቅ ምድር የምንነዳ እንስሶቻቸውና ነፍሶቻቸው ከእርሱ የሚበሉለትንም አዝመራ በእርሱ የምናወጣ መሆናችንን አያዩምን? አይመለከቱምን?

(28) 28. «ከእውነተኞችም እንደ ሆናችሁ ይህ ፍርድ መቼ ነው።» ይላሉ።

(29) 29. «በፍርዱ ቀን እነዚያን የካዱትን ሰዎች እምነታቸው አይጠቅማቸዉም:: እነርሱም ጊዜን አይሰጡም።» በላቸው።

(30) 30. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እነርሱን ተዋቸው:: ተጠባበቅም:: እነርሱም ተጠባባቂዎች ናቸውና::