(1) 1. ጧሃ፤
(2) 2.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ቁርኣንን አንድትቸገር ባንተ ላይ አላወረድንም::
(3) 3. አላህን ለሚፈራ ሁሉ መገሠጫ ይሆን ዘንድ እንጂ
(4) 4. ቁርኣን ምድርንና የላይኛዎቹን (የተከበሩ) ሰማያትን ከፈጠረ አምላክ ተወረደ::
(5) 5.እርሱ አዛኙ ጌታ (አር-ረህማን) በዐርሹ ላይ ከፍ አለ::
(6) 6. በሰማያት፤በምድርና በመካከላቸዉም ያለው ከአፈር በታችም ያለው ሁሉ የእርሱ ብቻ ነው::
(7) 7. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በንግግር ብትጮህ (አላህ ከጩኸቱ የተብቃቃ ነው።) እርሱ ምስጢርን ከዚያም በጣም የተደበቀንም ያውቃልና::
(8) 8.አላህ ከእርሱ ሌላ አምላክ የለም:: ለእርሱ መልካሞች የሆኑ አያሌ ስሞች አሉት::
(9) 9.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) የሙሳ ወሬ (ታሪክ) መጥቶሃልን (ደርሶሃልን)?
(10) 10. እሳትን ባየና ለቤተሰቦቹ «(እዚህ) ቆዩ:: እኔ እሳትን አየሁ፤ ከእርሷ ችቦን ላመጣላችሁ ወይም እሳቲቱ ዘንድ መሪን ላገኝ እከጅላለሁ።» ባለ ጊዜ የሆነውን አስታውስ::
(11) 11. እናም ወደ እርሷ በመጣ ጊዜ (እንዲህ) በማለት ተጠራ: «ሙሳ ሆይ!
(12) 12. «እኔ ጌታህ ነኝ። ጫማዎችህን አውልቅ፤ አንተ በተቀደሰው ሸለቆ በጡዋ ነህና።
(13) 13. «እኔም መረጥኩህ ስለ ሆነም የሚወረድልህን ነገር በደንብ አዳምጥ።
(14) 14. «እኔ አላህ ነኝ። ያለ እኔ ትክክለኛ አምላክ የለምና እኔን ብቻ ተገዛኝ:: ሶላትንም እኔን ለማውሳት በአግባቡ ስገድ።
(15) 15. «ነፍስ ሁሉ በምትሰራው ነገር ትመነዳ ዘንድ ሰዓቲቱ በእርግጥ መጪ ናት። የትንሳኤውን ወሬ ልደብቃት እቀርባለሁ።
(16) 16. (ሙሳ ሆይ!) «በእርሷ የማያምንና ዝንባሌውን የሚከተል ሰው ሁሉ ከእርሷ አያግድህ ትጠፋለህና።
(17) 17. (ሙሳ ሆይ!) «ይህችም በቀኝ እጅህ ያለችው ምንድን ናት?» (ተባለ)።
(18) 18. «እርሷ በትሬ ናት:: በእርሷም እደገፍባታለሁ:: በእርሷም ለፍየሎቼ ቅጠልን አረግፍባታለሁ:: በእርሷ ሌሎች ጉዳዮችም አሉኝ።» አለ።
(19) 19. አላህም «ሙሳ ሆይ! እስቲ ጣላት።» አለው።
(20) 20.ሙሳም ጣላትና፤ ወዲያዉም እርሷ የምትሮጥ እባብ ሆነች::
(21) 21.አላህም አለው: «ሙሳ ሆይ! ያዛት አትፍራም ወደ መጀመሪያ ጠባይዋ እንመልሳታለን።
(22) 22. «እጅህንም ወደ ብብትህ አስገባ:: ሌላ ተዓምር ስትሆን ያለ ምንም ችግር ነጭ ሆና ትወጣለችና::
(23) 23. (ሙሳ ሆይ!) «ከተዓምራቶቻችን ታላቋን እናሳይህ ዘንድ ይህን ፈጸምን::
(24) 24. (ሙሳ ሆይ!) «ወደ ፈርዖን ሂድ:: እርሱ ወሰን (ድንበር) አልፏልና።»
(25) 25. ሙሳም አለ: «ጌታዬ ሆይ! ልቤን አስፋልኝ።
(26) 26. «ጉዳዬንም አግራልኝ።
(27) 27. «የምላሴን መኮላተፍም አስወግድልኝ።
(28) 28. «ንግግሬን ይረዱ ዘንድ።
(29) 29. «ከቤተሰቦቼም ለእኔ ረዳትን አድርግልኝ።
(30) 30. «ወንድሜን ሃሩንን
(31) 31. «ኃይሌንም በእርሱ አበርታልኝ::
(32) 32. «በነገሬም አጋራው።
(33) 33. «በብዛት እንድናጠራህና
(34) 34. «በብዛት እንድናወሳህ
(35) 35. «አንተ በእኛ ነገር አዋቂ ነህና።»
(36) 36. አላህም አለ: «ሙሳ ሆይ! ልመናህ በእርግጥ ተቀባይነትን አገኝቷል።
(37) 37. «ሙሳ ሆይ! በሌላም ጊዜ ባንተ ላይ በእርግጥ ውለታን ውለናል::
(38) 38. «ለእናትህ በራእይ ባሳወቅን ጊዜ ነው።
(39) 39. «‹ሕፃኑን በሳጥኑ ውስጥ አስገቢው እርሱንም (ሳጥኑን) በባህር ላይ ጣይው፤ ባህሩም በዳርቻው ይጥለዋል (ይተፋዋል):: ለእኔም ለእርሱም ጠላት የሆነ ሰው ይይዘዋልና› በማለት (ባሳወቅን ጊዜ ለገስንልህ)። ልትወደድና በዐይኔ እይታ (በእኔም ጥበቃ) ታድግ ዘንድ ባንተ ላይም ከእኔ የሆነ መወደድን ጣልኩብህ::
(40) 40. «እህትህ በምትሄድና ‹የሚያሳድገውን ሰው ላመላክታችሁን?› ባለች ጊዜ (መወደድን ጣልኩብህ):: ወደ እናትህም ዓይኗ እንዲረጋና እርሷ እንዳታዝንም መለስንህ:: ነፍስንም ገደልክ ከጭንቅም አዳንንህ:: ፈተናዎችንም ፈተንህ:: በመድየን ቤተሰቦችም ውስጥ ብዙ ዓመታትን ተቀመጥክ:: ከዚያ ሙሳ ሆይ! በተወሰነ ጊዜ ላይ መጣህ::
(41) 41. «ለራሴም ለመልዕክተኝነት መረጥኩህ::
(42) 42. «አንተና ወንድምህ በተዓምራቴ ሆናችሁ ሂዱ:: እኔንም ከማውሳትም አትቦዝኑ::
(43) 43. «ወደ ፈርዖን ሂዱ:: እርሱ ወሰን አልፏልና::
(44) 44. «እርሱ ምን አልባትም ይገሰጥ ወይም ይፈራ ዘንድ:: ለእርሱ ለስላሳን ቃል ተናገሩት።»
(45) 45. «ጌታችን ሆይ! በእኛ ላይ ክፋት በመስራት መቸኮሉን ወይም ኩራትን መጨመሩን እንፈራለን።» አሉ።
(46) 46. አላህም አለ: «እኔ በእርግጥ ከናንተ ጋር ነኝና አትፍሩ:: የሚለውንም ሁሉ እሰማለሁ። የሚፈጸመዉንም አያለሁም።
(47) 47. እናም ወደ እርሱም ሂዱና (እንዲህ) በሉት: ‹እኛ የጌታህ መልዕክተኞች ነንና የኢስራኢልን ልጆች ሁሉ ከእኛ ጋር ልቀቅ። አታሰቃያቸዉም:: ከጌታህ በሆነው ተዓምር በእርግጥ መጥተንሃልና:: ሰላምም ቀጥታን በተከተለ ሁሉ ላይ ይሁን።
(48) 48. «‹እነሆ የአላህ ቅጣት እውነትን ባስተባበለና እምቢ ባለ ሰው ላይ እንደሆነ በእርግጥ አያሌ መልዕክት ተወረደልን።› በሉት።»
(49) 49. ፈርዖንም «ሙሳ ሆይ! ጌታችሁ ማነው?» አለ።
(50) 50. «ጌታችን ያ ለፍጥረቱ ሁሉ የሚያስፈልገውን ቅርጹንና ባህሪውን የሰጠው ከዚያም ሁሉንም ለተፈጠረለት የመራው ነው።» አለው።
(51) 51. ፈርዖንም «የመጀመሪያይቱ ዘመናት ህዝቦች ሁኔታስ ምንድን ነው?» አለ::
(52) 52. ሙሳም «የዚህ ዕውቀት እጌታዬ ዘንድ በመጽሐፍ የተመዘገበ ነው:: ጌታዬ አይሳሳትም አይረሳምም።» አለው።
(53) 53. ያ ምድርን ለእናንተ ምንጣፍ ያደረገላችሁ በእርሷም ውስጥ ለእናንተ መንገድን ያገራላችሁ ውሃንም ከሰማይ ያወረደላችሁ ነው። በእርሱም ከተለያየ በቃይ ዓይነቶችን አወጣንላችሁ።
(54) 54. ለራሳችሁ ብሉ:: እንስሳዎቻችሁንም አግጡ:: (ባዮች ሆነን አወጣንላችሁ።) በዚህ ውስጥ ለአእምሮ ባለቤቶች ሁሉ በእርግጥ ተዐምራት አለበት።
(55) 55. (ሰዎች ሆይ!) ከእርሷ (ከምድር) ፈጠርናችሁ:: ወደ እርሷም ውስጥ እንመልሳችኋለን:: ከእርሷም በሌላ ጊዜ እናወጣችኋለን::
(56) 56.ተዓምራቶቻችንንም ሁሏንም ለፈርዖን በእርግጥ አሳየነው:: አስተባበለም:: እምቢም አለ::
(57) 57. አለም: «ሙሳ ሆይ! ከምድራችን በድግምትህ ልታወጣን መጣህብን?
(58) 58. «መሰሉንም ድግምት እናመጣብሃለን:: በእኛና ባንተም መካከል እኛም አንተም የማንጥሰው የሆነ ቀጠሮን በመካከለኛ ስፍራ አድርግልን።» አለ::
(59) 59.ሙሳም: «ቀጠሯችሁ ያ የማጌጫው የበአሉ ቀን ነው። ሰዎችም ረፋድ ላይ እንዲሰበሰቡ ይሁን።» አለ።
(60) 60. ፈርዖንም ዞረ:: ተንኮሉን ሰበሰበ:: ከዚያ መጣ::
(61) 61.ሙሳም ለእነርሱ: «ወዮላችሁ በአላህ ላይ ውሸትን አትቅጠፉ:: በቅጣት ያጠፋችኋልና:: የቀጠፈም ሰው በእርግጥ አፈረ።» አላቸው።
(62) 62. (ድግምተኞቹ) በመካከላቸውም ነገራቸውን ተጨቃጨቁ፡፡ ውይይትንም ደበቁ፡፡
(63) 63. አሉም: «እነዚህ በእርግጥ ደጋሚዎች ናቸው:: ከምድራችሁ በድግምታቸው ሊያወጧችሁ በላጪቱንም መንገዳችሁን ሊያስወግዱባችሁ ይሻሉ።
(64) 64. «ተንኮላችሁንም አጠንክሩ:: ከዚያም ተሰልፋችሁ ኑ:: ዛሬ ያሸነፈም ሰው ምኞቱን አገኘ።» ተባባሉ።
(65) 65. «ሙሳ ሆይ! በመጀመሪያ ትጥላለህ ወይስ እኛ እንጣል? (ምረጥ)» አሉ።
(66) 66. ሙሳም «እናንተ በመጀመሪያ ጣሉ።» አላቸው። ጣሉም:: ወዲያዉም ገመዶቻቸውና ዘንጎቻቸው ከድግምታቸው የተነሳ የሚሮጡ እባቦች ሆነው (መስለው) ወደ እርሱ ተመሰሉበት።
(67) 67.ሙሳም በውስጡ ፍርሃት አደረበት::
(68) 68. አልነውም: «አትፍራ። የበላዩ አንተ ነህና።
(69) 69. «በቀኝ እጅህ ያለችውን ብትር ጣል:: ያንን የሰሩትን ሁሉ ትውጣለችና። ያ የሰሩት ሁሉ የድግምተኛ ተንኮል ብቻ ነውና:: ድግምተኛም በመጣበት ስፍራ ሁሉ አይቀናዉም::»
(70) 70. ድግምተኞቹም ሱጁድ ወረዱ: «በሃሩንና በሙሳ ጌታ አመንን።» አሉ::
(71) 71. (ፈርዖንም) «ለእናንተ ሳልፈቅድላችሁ በፊት ለእርሱ አመናችሁለትን! እርሱ በእርግጥ ያ ድግምትን ያስተማራችሁ መሪያችሁ ነው:: እጆቻችሁንና እግሮቻችሁን (በማናጋት) ግራንና ቀኝን በማፈራረቅ እቆራርጣችኋለሁ:: በዘምባባም ግንዶች ላይ እሰቅላችኋለሁ:: የማንኛችን ቅጣት በጣም ብርቱና የሚቆይ መሆኑን በዚያ ጊዜ ታውቃላችሁ።» አላቸው።
(72) 72. አሉትም: «ከመጡልን ተዓምራትና ከዚያ ከፈጠረን አምላክ ፈጽሞ አናስበልጥህም:: እናም የምትፈርደውን ፍረድ:: የምትፈርደው በዚህች በአነስተኛይቱ ህይወት ብቻ ላይ ነውና።
(73) 73. «ኃጢአቶቻችንንና ከድግምትም እንድንፈጽመው ያስገደድከንን ይምረን ዘንድ እኛ በጌታችን አምነናል:: አላህ በጣም በላጭ ነው:: ቅጣቱም ሆነ ምንዳው በጣም የሚዘወትር ነው።» አሉ።
(74) 74. ከሃዲ ሆኖ ወደ ጌታው የሚመጣ (የሚሞት) ሰው ሁሉ ለእርሱ ገሀነም አለችለት:: በውስጧም አይሞትም ህያዉም አይሆንም::
(75) 75.እነዚያ በጎ ስራዎችን የሰሩና አማኝ ሆነው ወደ ጌታቸው የመጡ ሰዎች ደግሞ እነዚያ ለእነርሱ ከፍተኛ ደረጃዎች አሏቸው::
(76) 76.ከስሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸው የመኖሪያ ገነቶች በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲሆኑ አሏቸው:: ይህም አይነቱ ክፍያ ለተጥራራ ሁሉ ምንዳው ነው::
(77) 77. ወደ ሙሳም «ባሮቼን ይዘህ በሌሊት ሂድ:: ለእነርሱም በባህር ውስጥ ደረቅ መንገድን አድርግላቸው:: ፈርዖን ያገኘኛል ብለህ አትፍራ:: ከመስመጥም አትጨነቅ።» ስንል በእርግጥ ላክንበት።
(78) 78. ፈርዖን ከሰራዊቱ ጋር ሆኖ ተከተላቸው:: ከባህሩም የሚሸፍን ነገር ሸፈናቸው።
(79) 79.ፈርዖንም ህዝቦቹን አሳሳታቸው:: ቅኑንም መንገድ አልመራቸዉም::
(80) 80. የኢስራኢል ልጆች ሆይ! ከጠላታችሁ በእርግጥ አዳንናችሁ:: በጡር ተራራም ቀኝ ጎን ላይ ቀጠሮ አደረግንላችሁ። በእናንተም ላይ መናንና ሰልዋን (ድርጭት) አወረድንላችሁ።
(81) 81. ከሰጠናችሁ ሲሳይ ከመልካሙ ብሉ:: በእርሱም ወሰንን አትለፉ:: ቁጣዬ በእናንተ ላይ ይወርድባችኋልና:: ቁጣዬ የሚወርድበት ሁሉ በእርግጥ ይጠፋል::
(82) 82.እኔም ለተጸጸተ ላመነም መልካምንም ለሰራ ከዚያ ለተመራ ሁሉ በእርግጥ መሓሪ ነኝ::
(83) 83. «ሙሳ ሆይ! ከህዝቦችህ ምን አስቸኮለህ?» ተባለ::
(84) 84. «እነርሱ እነዚህ በዱካዬ ላይ ያሉ ናቸው:: ጌታዬ ሆይ! ትወድልኝ ዘንድ ወደ አንተ ቸኮልኩ።» አለ።
(85) 85.(አላህም) «እኛም ካንተ በኋላ ሰዎችህን በእርግጥ ፈተንን:: ሳምራዊዉም አሳሳታቸው።» አለው::
(86) 86. ሙሳም ወደ ሰዎች የተቆጣና ያዘነ ሆኖ ተመለሰ:: «ህዝቦቼ ሆይ! ጌታችሁ መልካም ተስፋን አልቀጠራችሁምን? ቀጠሮው በእናንተ ላይ ረዘመባችሁን? ወይስ በእናንተ ላይ ከጌታችሁ ቅጣት ሊወርድባችሁ ፈለጋችሁና ቃል ኪዳኔን አፈረሳችሁ?» አላቸው::
(87) 87. «ቀጠሮህን በፈቃዳችን አልጣስንም:: ግን እኛ ከህዝቦች ጌጥ ሸክሞችን ተጫን:: በእሳት ላይ ጣልናትም:: ሳምራዊዉም እንደዚሁ አብሮን ጣለ።» አሉት።
(88) 88. ለእነርሱም የመጓጎር ባህሪ ያለውን ጥጃን (መሰል) አካልን አወጣላቸው። «ተከታዮቹ ሆይ! ይህ የእናንተም ሆነ የሙሳ አምላክ ነው:: ግን ረሳው እንጂ።» አሉ።
(89) 89.ወደ እነርሱ ንግግርን የማይመልስ ለእነርሱም ጉዳትንና ጥቅምን የማይችል መሆኑን አያዩምን?
(90) 90-.ከዚያ በፊት ሀሩንም በእርግጥ አላቸው: «ህዝቦቼ ሆይ! ይህ በእርሱ የተሞከራችሁበት ብቻ ነው:: ጌታችሁም አር-ረህማን ነው:: ተከተሉኝም፤ ትእዛዜንም ስሙ።»
(91) 91. «ሙሳ ወደ እኛ እስከሚመለስ በእርሱ መገዛት ላይ ከመቆየት ፈጽሞ አንወገድም።» አሉ።
(92) 92- ሙሳም አለ፡- «ሃሩን ሆይ! ተሳስተው ባየሃቸው ጊዜ ምን ከለከለህ?
(93) 93. «እኔን ከመከተል? ትእዛዜን ጣስክን?» አለ።
(94) 94. «ሃሩን የእናቴ ልጅ ሆይ! ፂሜንም ሆነ ራሴን አትያዝ:: እኔ ‹በኢስራኢል ልጆች መካከል ለያየህ ቃሌንም አልጠበክም› ማለትህን ፈራሁና ነው።» አለው።
(95) 95. ሙሳም «ሳምራዊው ሆይ! ነገርህ ምንድን ነው?» አለ።
(96) 96. ሳምራዊውም: «እነርሱ ያላዩትን ነገር አየሁ:: ከመልዕክተኛው ፈረስ ኮቴ ዱካም ጭብጥ አፈርን ዘገንኩ:: በቅርጹ ላይ ጣልኳትም:: ልክ እንደዚሁ ነፍሴ ሸለመችልኝ።» አለ።
(97) 97. ሙሳም ለሳምራዊው አለው: «ሂድ። በህይወትህ ላየኸው ሰው ሁሉ ‹መነካካት የለም› እያልክ ኑር:: ላንተም ፈጽሞ የማትቀር ቀጠሮ አለህ:: ወደ እዚያዉም በእርሱ ላይ ተገዢው ሆነህ ወደ ቆየህበት አምላክህ ተመልከት:: በእርግጥ እናቃጥለዋለን:: ከዚያም በባህሩ ውስጥ እንበትነዋለን::»
(98) 98.(ሰዎች ሆይ!) ጌታችሁም ያ ከእርሱ በስተቀር ሌላ አምላክ የሌለ የሆነው አላህ ብቻ ነው:: እውቀቱ ሁሉን ነገር አዳረሰ::
(99) 99. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ልክ እንደዚሁ በእርግጥ ካለፉት ወሬዎች ባንተ ላይ እንተርካለን፤ ከእኛም ዘንድ ቁርኣንን በእርግጥ ሰጠንህ::
(100) 100.ከእርሱ ያፈገፈገ ሰው እርሱ በትንሳኤ ቀን ከባድን ቅጣት ይሸከማል::
(101) 101.በእርሱ ውስጥ ዘውታሪዎች ሆነው ይሸከማሉ:: በትንሳኤ ቀን ለእነርሱ እጣ ፈንታ የሆነው ሸክም ከፋ!
(102) 102. በቀንዱ በሚነፋ ቀን ሸክማቸው ከፋ:: ከሓዲያን በዚያ ቀን ዓይኖቻቸው ሰማያዊዎች ሆነው እንሰበስባቸዋለን::
(103) 103. «አስርን (ቀን) እንጂ አልቆያችሁም።» በመባባል በመካከላቸው ይንሾካሾካሉ::
(104) 104. በሃሳብ ቀጥተኛቸው «አንድን ቀን እንጂ አልቆያችሁም።» በሚል ጊዜ የሚሉትን ነገር እኛ አዋቂዎች ነን።
(105) 105. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከጋራዎች ይጠይቁሃልና (እንዲህ) በላቸው: «ጌታዬ መበተንን ይበትናቸዋል።
(106) 106. «ትክክል ሜዳም ሆና ይተዋታል።
(107) 107. «በእርሷ ዝቅታና ከፍታን ፈጽሞ አታይም።»
(108) 108. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በዚያ ቀን ለመሰብሰብ ጠሪውን ምንም እንከን የሌለውን ተጣሪ ይከተላሉ:: ድምፆችም ሁሉ ለአር-ረህማን ጸጥ ይላሉ:: ስለዚህ (የኮቴ) ሹክሹክታን እንጂ አትሰማም።
(109) 109.በዚያ ቀን ለእርሱ አር-ረህማን የፈቀደለትንና ለእርሱም ቃልን የወደደለትን ብቻ ቢሆን እንጂ ምልጃ አንድንም አትጠቅምም::
(110) 110. በስተፊታቸው ያለውንም ሆነ በስተኋላቸው ያለውን ሁሉ ያውቃል:: በእርሱ ላይ ግን ማንም በእውቀቱ አያካብብም::
(111) 111. ፊቶችም ሁሉ ህያውና የሁሉ አስተናባሪ ለሆነው አላህ ተዋረዱ:: በደልንም የተሸከመ በእርግጥ ከሰረ::
(112) 112. አማኝ ሆኖ መልካም ስራዎችን የሰራ በደልንም ሆነ መጉደልን አይፈራም::
(113) 113.ልክ እንደዚሁም ዐረብኛ ቁርኣን ሆኖ አወረድነው:: አላህን ይፈሩ ዘንድ ወይም ለእነርሱ ግሣጼን ያድስላቸው ዘንድ ከዛቻ ደጋግመን በውስጡ ገለጽን::
(114) 114. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እውነተኛው ንጉስ አላህ ከሓዲያን ከሚሉት ነገር ሁሉ ላቀ:: ወደ አንተ መወረዱም ከመፈጸሙ በፊት ቁርኣንን በማንበብ አትቸኩል:: «ጌታዬ ሆይ! ዕውቀትን ጨምርልኝ።» በልም።
(115) 115. ወደ አደምም ከዚህ በፊት ቃል ኪዳንን በእርግጥ አወረድንና ረሳ:: ለእርሱም ቆራጥነትን አላገኘንለትም::
(116) 116.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ለመላእክትም «ለአደም ስገዱ።» ባልን ጊዜ (የሆነውን አስታውስ):: እነርሱም ዲያብሎስ ብቻ ሲቀር ሰገዱ:: እሱማ እምቢ አለ::
(117) 117.ከዚያም አልን: «አደም ሆይ! ይህ ላንተም ለሚስትህም በእርግጥ ጠላት ነው:: ስለዚህ ከገነት አያውጣችሁ፤ ትለፋለህና::
(118) 118.(አደም ሆይ!) «ላንተ በእርሷ ውስጥ አለመራብና አለመታረዝ አለህ::
(119) 119. «አንተም ከእርሷ ውስጥ አትጠማም:: በጸሐይም አትተኮስም።»
(120) 120. ሰይጣን ወደ እርሱ (አደም) « አደም ሆይ! በመዘውተሪያ ዛፍ በማይጠፋ ንግስናም ላይ ላመላክትህን?» በማለት ጎተጎተ።
(121) 121.ከእርሷም በሉ:: ለእነርሱም ሀፍረተ ገላቸው ተገለጸች:: ከገነትም ቅጠል በላያቸው ላይ ይለጥፉ ጀመር:: አደምም የጌታውን ትእዛዝ ረስቶ ጣሰ:: ተሳሳተም::
(122) 122. ከዚያም ጌታው መረጠው:: ከእርሱም ጸጸቱን ተቀበለው:: መራዉም::
(123) 123.አላህም አላቸው፡- «ከፊላችሁ ለከፊሉ ጠላት ሲሆን (አደምና ሐዋ) ሁላችሁም ከእርሷ ውረዱ:: ከእኔ የሆነ መመሪያ ቢመጣላችሁ መመሪያየን የተከተለ ሁሉ አይሳሳትም:: አይቸገርምም::
(124) 124. «ከግሳጼዬ የዞረ ግን በዚህች ዓለም ጠባብ ኑሮ አለው:: በትንሳኤ ቀንም ዕውር ሆኖ እንቀሰቅሰዋለን::»
(125) 125. «ጌታዬ ሆይ! ለምን ዕውር አድርገህ አስነሳኸኝ:: በእርግጥ የማይ የነበርኩ ስሆን» አለ።
(126) 126. «ነገሩ ልክ እንደዚሁ ነው:: ተዓምራቶቻችን መጡልህና ተውካቸውም:: ልክ እንደዚሁም ዛሬ ትተዋለህ።» ይለዋል።
(127) 127.እንደዚሁም ያጋራንና በጌታው አናቅጽ ያላመነን እንቀጣዋለን:: የመጨረሻይቱ ዓለም ቅጣት በጣም ብርቱና ለሁልጊዜም ዘውታሪ ነው::
(128) 128. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ! ቁረይሾች) ከእነርሱ በፊት ከክፍለ ዘመናት ህዝቦች ብዙዎችን ያጠፋን መሆናችን በመኖሪያዎቻቸው የሚሄዱ ሆነው ሳሉ ለእነርሱ አልተገለጸላቸዉምን? በዚህ ውስጥ ለአእምሮ ባለቤቶች በእርግጥ መልዕክቶች አሉበት::
(129) 129.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከጌታህ ያለፈች ቃልና የተወሰነ ጊዜ ባልነበረ ኖሮ ቅጣቱ አሁኑኑ የሚይዛቸው ይሆን ነበር::
(130) 130. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ! ) በሚሉትም ሁሉ ላይ ታገሥ፤ ጌታህንም ጸሐይ ከመውጣቷ በፊትና ከመግባቷም በፊት የምታመሰግን ሆነህ አጥራው:: ከሌሊት ሰዓቶችም በቀን ጫፎችም አጥራው:: በሚሰጥህ ምንዳ ልትወድ ይከጀላልና::
(131) 131.ዐይኖችህን ከሰዎች የተወሰኑ ክፍሎችን ልንፈትናቸው ወደ አጣቀምንበት ወደ ቅርቢቱ ህይወት ጌጦች አትዘርጋ:: የጌታህ ሲሳይ በጣም በላጭና ዘውታሪ ነው።
(132) 132.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ቤተሰብህንም በሶላት ላይ እዘዝ:: አንተም በእርሷ ላይ ዘውትር:: ሲሳይን አንጠይቅህም:: እኛ እንሰጥሃለን:: መልካሚቱ መጨረሻ ለጥንቁቆቹ ናት::
(133) 133. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ተከራካሪዎችህ «ከጌታው በሆነ ተዓምር አይመጣምን?» አሉ:: በመጀመሪያዎቹ ጹሁፎች ውስጥ ያለችው ማስረጃ አልመጣቻቸዉምን?
(134) 134. እኛም (ከሙሐመድ መላክ) በፊት በቅጣት ባጠፋናቸው ኖሮ «ጌታችን ሆይ! ከመዋረዳችንና ከማፈራችን በፊት አናቅጽህን እንከተል ዘንድ ወደኛ መልዕክተኛን አትልክልንም ነበርን?» ባሉ ነበር::
(135) 135. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «ሁሉም ተጠባባቂ ነው:: ተጠባበቁም የቀጥታዉም መንገድ ባለቤቶች እነማን እንደ ሆኑ እነማንም እንደ ተመሩ ወደፊት ታውቃላችሁ።» በላቸው::