74 - Al-Muddaththir ()

|

(1) 1. አንተ (ልብስ) ደራቢው ሆይ!

(2) 2. ተነሳና (ህዝቦችህን) አስጠንቅቅ።

(3) 3. ጌታህንም አክብር::

(4) 4. ልብስህንም አጥራ::

(5) 5. ጣዖትንም ራቅ::

(6) 6. ማብዛትንም የምትፈልግ ሆነህ አትለግስ::

(7) 7. (ብዙ ዒባዳን ከመስራት አትድከም):: ለጌታህም (ትዕዘዛዝ) ታገስ።

(8) 8. በቀንዱም በተነፋ ጊዜ፤

(9) 9. ይህን ጊዜ ያ ቀን አስቸጋሪ ቀን ነው።

(10) 10. (በተለይ) በከሓዲያን ላይ ገር ያልሆነ ቀን ነው።

(11) 11. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በብቸኝነት ከፈጠርኩት ጋር ተወኝ።

(12) 12. ለእርሱም የተዘረጋን ገንዘብ (በዓይነቱ) አደረግኩለት።

(13) 13. በየአደባባዩ ተገኝ የሆኑ ወንዶች ልጆችንም ሰጠሁት።

(14) 14. ለእርሱም ኑሮውን መዘርጋትን ዘረጋሁለት፤

(15) 15. ከዚያ ልጨምርለት ይከጅላል::

(16) 16. ሰው ይከልከል! እርሱ ለአናቅጻችን በእርግጥ ተቃዋሚ ነበርና።

(17) 17. በእርግጥ (ገሀነም ውስጥ) ችግርን አስገድደዋለሁ።

(18) 18. እርሱ (በቁርኣን ጉዳይ) አሰበ፤ ገመተም።

(19) 19. እናም ተረገመ:: እንዴት ገመተ!

(20) 20. ከዚያ ተረገመ። እንዴትስ ገመተ!

(21) 21. ከዚያም እንደገና (በቁርኣን ጉዳይ) ተመለከተ።

(22) 22. ከዚያ ፊቱን አጨፈገገ አኮማተረም::

(23) 23. ከዚያ (በአላህ ከማመን) ዞረ:: ኮራም::

(24) 24. «ይህ ከሌላ (ሰው) የሚቀዳ ድግምት እንጂ ሌላ አይደለም።

(25) 25. «ይህ የሰው ቃል እንጂ ሌላ አይደለም» አለ::

(26) 26. ሰቀር (በተባለ የገሀነም ዋሻ ውስጥ) በእርግጥ አስገባዋለሁ::

(27) 27. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ሰቀር ምን እንደሆነ ምን አሳወቀህ?

(28) 28. (ያገኘችውን ሁሉ) አታስቀርም:: አትተዉምም::

(29) 29. የሰዎችን ቆዳ በጣም አክሳይ ናት።

(30) 30. በእርሷም ላይ አስራ ዘጠኝ (ዘበኞች) አሉባት::

(31) 31. የእሳትን ዘበኞች መላዕክት እንጂ ሌላ አላደረግንም:: ቁጥራቸውንም ለእነዚያ በአላህ ለካዱት ሰዎች መፈተኛ እንጂ ለሌላ አላደረግንም:: እነዚያ መጽሐፍን የተሰጡት ሰዎች እንዲያረጋግጡ፤ እነዚያም በትክክል ያመኑት እምነትን እንዲጨምሩ፤ እነዚያም መጽሐፍን የተሰጡትና ምዕመናኖቹ እንዳይጠራጠሩ፤ እነዚያም በልቦቻቸው ውስጥ በሽታ ያለባቸው አስመሳዮችና ከሓዲያን «አላህ በዚህ (ቁጥር) ምን ምሳሌ ሽቷል?» እንዲሉ እንጂ (አላደረግንም):: ልክ እንደዚሁ አላህ የሚፈልገውን ያጠማል:: የሚፈልገውንም ያቀናል:: (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) የጌታህንም ሰራዊት ልክ ከእርሱ በስተቀር ማንም አያውቅም:: የሰቀር እሳት ለሰዎች መገሰጫ እንጂ ሌላ አይደለም::

(32) 32. (ከክህደት) ይከልከሉ:: በጨረቃ (እምላለሁ)

(33) 33. በሌሊቱም በሄደ ጊዜ፤

(34) 34. በንጋቱም ባበራ ጊዜ እምላለሁ።

(35) 35. (ሰቀር) ከታላላቆች አደጋዎች አንዱ፤

(36) 36. ለሰዎች አስፈራሪ ናት።

(37) 37. ከናንተ መካከል ወደ በጎ ነገር መቅደምን ወይም ወደ ኋላ መቅረትን ለፈለገ (ሰው) ሁሉ፤

(38) 38. ነፍስ ሁሉ በሰራችው ስራ ተያዥ ናት::

(39) 39. እነዚያ መዝገባቸውን በቀኝ እጃቸው የሚሰጡት ብቻ ሲቀሩ::

(40) 40. (እነርሱማ) በገነቶች ውስጥ ሁነው እርስ በራሳቸው ይጠያየቃሉ::

(41) 41. ከአመጸኞች ሁኔታ (ይጠያየቃሉ)

(42) 42. (ከዚያ ለእነርሱ እንዲህ ይሏቸዋል።) «በሰቀር ውስጥ ምን አገባችሁ?»

(43) 43. «ከሰጋጆች አልነበርንም።

(44) 44. «ለድሆችም የምናበላም አልነበርንም።

(45) 45. «ከዘባራቂዎችም ጋር እንዘባርቅ ነበር።

(46) 46. «በፍርዱ ቀንም እናስተባብል ነበር፤

(47) 47. «እርግጠኛው ነገር ሞት እስከመጣብን ድረስ።» ይላሉ

(48) 48. እናም በዚያ ቀን የአማላጆች (ሁሉ) ምልጃ አትጠቅማቸዉም።

(49) 49. ከ(ቁርኣን) ከግሳጼም የሚያፈገፍጉበት ምን ምክኒያት አላቸው?

(50) 50. እነርሱ ልክ ደንባሪዎች የሜዳ አህዩች ይመስላሉ::

(51) 51. ከአንበሳ የሸሹ

(52) 52. ይልቁንም ከእነርሱ መካከል ለእያንዳንዱ ሰው የተዘረጉ ጹሑፎችን በእጁ እንዲሰጥ ይፈልጋል::

(53) 53. ከዚህ መሰል ተግባራቸው ይከልከሉ:: ይልቁንም የመጨረሻይቱን ዓለም ቅጣት አይፈሩም::

(54) 54. ይከልከሉ፤እርሱ(ቁርአን) መገሰጫ ነው።

(55) 55. ስለዚህ የፈለገ ሰው ቁርኣንን ይገሰጽበታል::

(56) 56. ሆኖም (ሰዎች) አላህ ካልፈለገ በስተቀር አይገሰጹም:: አላህ የመፈራት ባለቤት ነው:: (ለፈሩትም) የምህረት ባለቤት ነው::