(1) 1. ያሲን::
(2) 2-ጥበብ በተሞላበት ቁርኣን እምላለሁ::
(3) 3.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከመልዕክተኞቹ መካከል አንዱ ነህ።
(4) 4. አንተ በእርግጥ በቀጥታው መንገድ ላይ ነህ ::
(5) 5.ቁርኣን አሸናፊውና አዛኙ ከሆነው አምላክ ከአላህ ተወረደ::
(6) 6. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አባቶቻቸው ያልተስፈራሩትን ህዝቦች ልታስጠነቅቅበት ቁርኣን ተወረደ። እነርሱ ዘንጊዎች ናቸውና።
(7) 7. በአብዛኞቻቸቸው ላይ ቃሉ በእውነት ተረጋገጠ:: ስለዚህ እነርሱ አያምኑም::
(8) 8. እኛ በአንገቶቻቸው ላይ እንዛዝላዎችን አደረግን። (እንዛዝላይቱም) ወደ አገጮቻቸው ደራሽ ናት። እናም ከዚያም እነርሱ ራሶቻቸውን ያንጋጠጡ ናቸው።
(9) 9. ከበስተፊታቸዉም ግርዶን ከበስተኋላቸዉም ግርዶን አደረግንና ሸፈንናቸው:: ስለዚህ እነርሱ አያዩም::
(10) 10. ብታስጠነቅቃቸዉም ባታስጠነቅቃቸዉም ለእነርሱ ሁሉም እኩል ነው:: (ምንም ለውጥ አያመጣም) አያምኑምና::
(11) 11. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) የምታስጠነቅቀው ግሳጼን የተከተለንና አር-ረህማንን በሩቅ የፈራን ሰው ብቻ ነው:: እናም በምህረትና በመልካም ምንዳ አብስረው::
(12) 12. እኛ ሙታንን በእርግጥ ህያው እናደርጋለን:: ያስቀደሙትንም ስራ ፈለጎቻቸውንም እንጽፋለን:: ሁሉን ነገርም ገላጭና መሪ በሆነ መጽሐፍ ውስጥ አጠቃለልነው::
(13) 13. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ለእነርሱም የከተማይቱን (የአንጾኪያን) ሰዎች ምሳሌ መልዕክተኞች በመጧት ጊዜ የሆነውን ግለጽላቸው።
(14) 14. ወደ እነርሱ ሁለትን ሰዎች በላክንና ባስተባበሉዋቸውም ጊዜ፤ በሶስተኛም ባበረታናቸውና «እኛ ወደ እናንተ መልክተኞች ነን» ባሏቸው ጊዜ የሆነውን ምሳሌ ግለጽላቸው።
(15) 15. «እናንተ መሰላችን ሰዎች እንጂ ሌላ አይደላችሁም:: አር-ረህማንም ምንንም ነገር አላወረደም:: እናንተ የምትዋሹ እንጂ ሌላ አይደላችሁም» አሏቸው።
(16) 16. መልዕክተኞቹም አሉ: «ጌታችን ያውቃል። እኛ ወደ እናንተ በእርግጥ መልክተኞች ነን።
(17) 17. «በእኛ ላይም ግልጽ የሆነ ማድረስ እንጂ ሌላ የለብንም።» አሉ።
(18) 18. ህዝቦቹም «እኛ በእናንተ ገደ ቢሶች ሆንን። ከዚህ ጥሪያችሁ ባትከለክሉም በእርግጥ እንወግራችኋለን:: ከእኛም አሳማሚ ቅጣት በእርግጥ ያገኛችኋል» አሉ።
(19) 19. «ገደ ቢስነታችሁ ከናንተው ጋር ነው:: ብትገሰጹ (ትዝታላችሁን?) በእውነቱ እናንተ ወሰን አላፊ ህዝቦች ናችሁ» አሏቸው።
(20) 20. ከከተማይቱም ሩቅ ዳርቻ የሚሮጥ ሰው መጣና (እንዲህ) አለ: «ወገኖቼ ሆይ! መልዕክተኞቹን ተከተሉ።
(21) 21. «እነርሱም ቅኑን መንገድ የተመሩ ሲሆኑ ክፍያን የማይጠይቋችሁን ሰዎች ተከተሉ።
(22) 22. «ያንንም የፈጠረኝንና ወደ እርሱም የምትመለሱበትን ጌታ የማልገዛበት ምን ምክንያት አለኝ?
(23) 23. «ከእርሱ ሌላ አማልክትን እይዛለሁን? አልራህማን ሊጎዳኝ ቢፈልግ ምልጃቸው ከእኔ (ለመመለስ) ምንም አትጠቅመኝም አያድኑኝምም።
(24) 24. «እኔ ያን ጊዜ በግልጽ ስህተት ውስጥ ነኝ።
(25) 25. «እኔ በጌታችሁ አመንኩ። ስሙኝም።» አለ።
(26) 26. {1} «ገነትን ግባ» ተባለም። እርሱም አለ: «ወገኖቼ ቢያውቁ እመኛለሁ።
{1} ደብድበው ገደሉት ከሞተ በኋላ ጀነት ግባ ተባለ
(27) 27. «ጌታዬ ለእኔ ምህረት ያደረገልኝና ከተከበሩትም ያደረገኝ መሆኑን።» (ቢያውቁ ተመኘሁ)
(28) 28. ከእርሱም በኋላ በህዝቦቹ ላይ ልናጠፋቸው ሰራዊትን ከሰማይ አላወረድንም (በማንም) ላይ አውራጆችም አልነበርንም::
(29) 29. ቅጣታቸው አንዲት ጩኸት እንጂ ሌላ አልነበረችም:: ወዲያውኑም እነርሱ ጠፊዎች ሆኑ::
(30) 30. በባሮች ላይ ዋ ቁጭት! ከመልዕክተኛ አንድም አልመጣላቸዉም በእርሱ ያፌዙበት ቢሆን እንጂ፤
(31) 31. ከእነርሱ በፊት ከክፍለ ዘመናት ህዝቦች ብዙዎችን ማጥፋታችንንና እነርሱ የማይመለሱ መሆናቸውን አላወቁምን?
(32) 32. ሁሉም እኛ ዘንድ (የሚሰበሰቡ) የሚቀረቡ እንጂ ሌላ አይደሉም::
(33) 33. የሞተችዉም ምድር ለእነርሱ ምልክት ናት:: ህያው አደረግናት:: ከእርሷ ፍሬን አወጣን፤ ከእሱም ይበላሉ::
(34) 34. በእርሷ ውስጥ ከዘምባባዎችና ከወይኖች የሆነ አትክልቶችን አደረግን:: በእርሷም ውስጥ ምንጮችን አፈለቅን::
(35) 35. ከፍሬዉና እጆቻቸው ከሰሩትም ይበሉ ዘንድ ይህን አደረግን:: አያመሰግኑምን?
(36) 36. ያ! ምድር ከምታበቅለው፤ ወንዴንና ሴቴን ከነፍሶቻቸዉም ከማያውቁትም ነገር (ዓይነቶችን) ሁሏንም የፈጠረ (አምላክ) ጥራት ይገባው::
(37) 37. ሌሊቱም ለእነርሱ ምልክት ነው:: ከእርሱ ላይ ቀንን አንገፋለን:: ወዲያውኑም እነርሱ በጨለማ ውስጥ ይገባሉ::
(38) 38. ጸሐይም ለእርሷ ወደ ሆነው መርጊያ ትሮጣለች:: ይህ የአሸናፊውና የአዋቂው አምላክ የአላህ ውሳኔ ነው::
(39) 39. ጨረቃንም የመስፈሪያዎች ባለቤት ሲሆን እንደ አሮጌ ዘንባባ ቀንዘል እስኪሆን ድረስ መሄዱን ለካነው::
(40) 40. ጸሐይ ጨረቃን ልትደርስበት አይገባትም:: ሌሊትም ቀንን ያለ ጊዜው ቀዳሚ አይሆንም:: ሁሉም በየመዞሪያቸው (በፈለክ) ውስጥ ይዋኛሉ::
(41) 41. እኛም የቀድሞ ትውልዳቸውን (አባቶቻቸውን) በተሞላች መርከብ ውስጥ የጫን መሆናችን ለእነርሱ ምልክት ነው::
(42) 42. ከመሰሉም በእርሱ የሚሳፈሩበትን ለእነርሱ ፈጠርንላቸው::
(43) 43. ስንፈልግ እናሰምጣቸዋለን:: ለእነርሱም ነፃ የሚያደርጋቸው ረዳት የላቸዉም:: እንዲድኑ የሚደረጉም አይደሉም።
(44) 44. እኛ ግን በችሮታችንና እስከ ጊዜ ሞታቸው ለማጣቀም አዳንናቸው::
(45) 45. ለእነርሱም «በስተፊታችሁና በኋላችሁ ያለውን ነገር ተጠንቀቁ፤ ይታዘንላችኋልና» በተባለ ጊዜ ፊታቸውን ያዞራሉ።
(46) 46. ከጌታቸውም ተዓምራት አንዲትም ተዓምር አትመጣላቸዉም ከእርሷ የሚሸሹ ቢሆኑ እንጅ።
(47) 47. ለእነርሱም «አላህ ከሰጣችሁ ሲሳይ ለግሱ» በተባሉ ጊዜ እነዚያ በአላህ የካዱት ለእነዚያ በአላህ ላመኑት «አላህ ቢሻ ኖሮ የሚያበላውን እናበላለን? እናንተ በግልጽ ስህተት ውስጥ እንጂ በሌላ ላይ አይደላችሁም።» ይላሉ።
(48) 48. «እውነተኞችም እንደ ሆናችሁ ይህ ቀጠሮ መቼ ነው?» ይላሉ።
(49) 49. እነርሱ የሚከራከሩ ሲሆኑ በድንገት የምትይዛቸው የሆነችን አንዲትን ጩኸት እንጂ ሌላን አይጠባበቁም::
(50) 50. ያን ጊዜ መናዘዝን እንኳን አይችሉም:: ወደ ቤተሰቦቻቸዉም አይመለሱም::
(51) 51. በቀንዱም ይነፋል:: ወዲያውኑም እነርሱ ከየመቃብሮቻቸው ወደ ጌታቸው በፍጥነት ይገሰግሳሉ::
(52) 52. «ወይ ጥፋታችን! ከመኝታችን ማን ቀሰቀሰን? ይህ ያ አዛኙ ጌታ በእርሱ የቀጠረን መልዕክተኞቹም እውነቱን የነገሩን ነው።» ይላሉ።
(53) 53. እርሷ አንዲት ጩኸት እንጂ ሌላ አይደለችም:: ወዲያውኑም እነርሱ እኛ ዘንድ የሚሰበሰቡ የሚቀርቡ ናቸው::
(54) 54. ዛሬም ማንኛይቱም ነፍስ ምንንም አትበደልም:: ትሰሩትም የነበራችሁትን እንጂ ሌላን አትመነዱም (ይባላሉ።)
(55) 55. የገነት ሰዎች ዛሬ በእርግጥ በስራዎች ውስጥ ተደሳቾች ናቸው::
(56) 56. እነርሱም ሆኑ ሚስቶቻቸው በጥላዎች ውስጥ ናቸው:: ባለ አጎበር አልጋዎች ላይም ተደጋፊዎች ናቸው::
(57) 57. በውስጧ ለእነርሱ ፍራፍሬዎች አሏቸው:: ለእነርሱም የሚፈልጉት ሁሉ አለላቸው::
(58) 58. ለእነርሱም አዛኝ ከሆነው ጌታ በቃል ሰላምታ አለላቸው።
(59) 59. (አላህም ይላል): «እናንተ አመጸኞች ሆይ! ዛሬ ከትክክለኛ አማኞች ተለዩ።
(60) 60. «የአደም ልጆች ሆይ! ሰይጣንን አትገዙ እርሱ ለእናንተ ግልጽ ጠላት ነውና በማለት ወደ እናንተ አላዘዝኩምን?
(61) 61. «ተገዙኝም ይህ ቀጥተኛ መንገድ ነው በማለትም::
(62) 62. «ከናንተም ብዙን ፍጡር በእርግጥ አሳስቷል:: የምታውቁም አልነበራችሁምን?
(63) 63. «ይህቺ ያቺ ትቀጠሯት የነበረችው ገሀነም ናት።
(64) 64. «ትክዱ በነበራችሁት ምክንያት ዛሬዉኑ ግቧት።» (ይባላሉ።)
(65) 65. ዛሬ በአፎቻቸው ላይ እናትምና እጆቻቸው ያነጋግሩናል:: እግሮቻቸዉም ይሰሩት በነበሩት ሁሉ ይመሰክራሉ::
(66) 66. ብንፈልግ ኖሮ በዓይኖቻቸው ላይ በአበስን ነበር:: መንገድንም እንደ ልማዳቸው በተሸቀዳደሙ ነበር:: እንዴትስ ያያሉ?
(67) 67. ብንፈልግ ኖሮ በስፍራቸው ላይ እንዳሉ ወደ ሌላ ፍጥረት በለወጥናቸው ነበር:: ከዚያም መሄድንም ሆነ መመለስን ባልቻሉም ነበር::
(68) 68. እድሜውንም የምናረዝመውን በፍጥረቱ ወደ ደካማነት እንመልሰዋለን:: አያውቁምን?
(69) 69. (ሙሐመድን) ቅኔንም አላስተማርነዉም:: ለእርሱም አይገባዉም:: እርሱ (መጽሐፉ) መገሰጫና ገላጭ ቁርኣን አንጅ (ቅኔ አይደለም)::
(70) 70. ግሳጼነቱም ልቡ ህያው የሆነን ሰው ሊያስፈራራበትና ቃሉም በከሓዲያን ላይ ይፈጸም ዘንድ ነው::
(71) 71. እኛ እጆቻችን ከሰሩት ለእነርሱ እንሰሳዎችን መፍጠራችንን አያውቁምን? እነርሱም ለእርሷ ባለ መብቶች ናቸው::
(72) 72. ለእነርሱም ገራናት:: ስለዚህ ከእርሷ ውስጥ የሚጋልቡት አለ:: ከእርሷም ይመገባሉ::
(73) 73. ለእነርሱም በእርሷ ውስጥ ሌሎች ጥቅሞችና መጠጦችም አሏቸው። ታዲያ አያመሰግኑምን?
(74) 74. መረዳትንም በመከጀል ከአላህ ሌላ አመለኩ።
(75) 75. ሊረዷቸውም አይችሉም። እነርሱም ለእርሳቸው ወደ እሳት የተቀረቡ ሰራዊት ናቸው::
(76) 76. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ንግግራቸዉም አያሳዝንህ:: እኛ የሚደብቁትንም የሚገልፁትንም እናውቃለንና::
(77) 77. ሰው እኛ ከፍትወት ጠብታ የፈጠርነው መሆናችንን አላወቀምን? ወዲያዉም እርሱ ትንሳኤን በመካድ ግልጽ ተከራካሪ ይሆናልን?
(78) 78. ለእኛም ምሳሌን አደረገልን:: መፈጠሩንም ረሳ:: «አጥንቶችን እነርሱ የበሰበሱ ሲሆኑ ህያው የሚያደርጋቸው ማነው?» አለ::
(79) 79. «ያ! በመጀመሪያ ጊዜ (ከኢምንት) ያስገኛት ጌታ እንደገና ህያው ያደረጋታል:: እርሱም በፍጡሩ ሁሉ ሁኔታ አዋቂ ነው።» በለው።
(80) 80. ያ! ለእናንተ ከእርጥብ ዛፍ እሳትን የፈጠረላችሁ ነው:: ወዲያውኑም እናንተ ከእርሱ ታቀጣጥላላችሁ::
(81) 81. ያ! ሰማያትንና ምድርን የፈጠረ ብጤያቸውን በመፍጠር ላይ ቻይ አይደለምን? እንዴታ ቻይ ነው እንጂ:: እርሱም በብዙ ፈጣሪውና እጅግ አዋቂው ነው።
(82) 82. ነገሩ አንድን ነገር በሻ ጊዜ ሁን ማለት ብቻ ነው:: ከዚያ ወዲያው ይሆናልም::
(83) 83. እናም ያ የነገሩ ሁሉ ስልጣን በእጁ የሆነው ጌታ ጥራት ይገባው:: ወደ እርሱም ትመለሳላችሁ::