(1) 1. በኮከብ እምላለሁ በገባ ጊዜ፤
(2) 2. (እናንተ የመካ ሰዎች ሆይ)፤ ባልደረባችሁ ሙሐመድ ከሐቅ አልተሳሳተም። አላፈነገጠም።
(3) 3. ከልብ ወለድ ስሜቱም አይናገርም::
(4) 4. እርሱ (ንግግሩ) ከአላህ የተወረደ እንጂ ሌላ አይደለም።
(5) 5. ሀይለ ብርቱ የሆነው አስተማረው::
(6) 6. የእውቀት ባለቤት የሆነው:: ከዚያም ላይ ሆኖ ተመቻቸ።
(7) 7. በላይኛው አድማስ ላይ ሆኖ፤
(8) 8. ከዚያም (ነቢዩን) ቀረበው፤ በጣም ተጠጋውም።
(9) 9. ከዚያም የሁለት ደጋን ጫፎች ያህል ወይም ከዚያም ባነሰ ርቀት ላይ ሆነም::
(10) 10. እናም (አላህ) ለአገልጋዩ (ለሙሐመድ) ማውረድ የሻውን አወረደ::
(11) 11. ያየውን ነገር ሁሉ ልቦናው አላስተባበለዉም::
(12) 12. ታዲያ (ከሓዲያን ሆይ!) በሚያየው ጉዳይ ላይ ትከራከሩታላችሁን?
(13) 13. እርግጥ በሌላይቱም መውረድ (ነቢዩ ሙሐመድ መልዐኩ ጂብሪልን) አይቶታል::
(14) 14. ይኸዉም ሲድረቱ አል-ሙንተሃ (የመጨረሻቱ ቁርቁራ) በተባለው ዓለም ላይ ነው::
(15) 15. እርሷ ዘንድ መኖርያ የሆነችው ገነት አለች::
(16) 16. (ቁርቁራይቱን) ሸፋኝ ነገር በሸፈናት ጊዜ (አየው)።
(17) 17. አይኑ አልተዘነበለም:: ወሰንም አላለፈም።
(18) 18. ከጌታው ታላላቅ ተዐምራት በእርግጥ ተመለከተ።
(19) 19. (ቁርይሾች ሆይ!) ላትንና ዑዛን አያችሁን?
(20) 20. ስለ ሶስተኛዋ መናትም የምታውቁትን እስቲ ንገሩኝ::
(21) 21. ለእናንተ ወንድ ወንድ ለእሱ ግን ሴት ሴት ታደርጋላችሁን::
(22) 22. ይህ ተግባር አድሏዊ ክፍፍል ነው::
(23) 23. እነዚያ ጣዖታት እናንተና አባቶቻችሁ የሰየማችኋቸው ስሞች ብቻ እንጂ ሌላ አይደሉም::አላህ በእርሷ (መገዛት) ምንም ማስረጃ አላወረደም፡፡ ጣኡት አምላኪዎች ሁሉ ከጌታቸው የተላከላቸው ቅኑ መመሪያ እያለ የሚከተሉት ግን ጥርጣሬንና ስሜትን ብቻ ነው::
(24) 24. የሰው ልጅ የፈለገውን ሁሉ ያገኛልን?
(25) 25. መጪውን ዓለምም ሆነ የመጀመሪያው ዓለም የአላህ ብቻ ነው::
(26) 26. በሰማያት ውስጥ ካሉ መላዕክት አላህ የሚሻውንና የሚወደውን ለሰው ያማልዱ ዘንድ ከፈቀደላቸው በኋላ እንጂ ምልጃቸው የማይፈይድ አያሌዎች ናቸው::
(27) 27. እነዚያ በመጪው ዓለም የማያምኑት መላዕክትን በእንስት ስም ይሰይማሉ::
(28) 28. ለእነርሱም በእርሱ እውቀት የላቸውም። እነርሱ የሚከተሉት ጥርጣሬን ብቻ ነው:: ጥርጣሬ ደግሞ ሀቅን አይተካም::
(29) 29. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከቁርኣን አፈንግጦና የዚችን ዓለም ኑሮ እንጂ ሌላ ከማይመኝ ሰው እራስህን አሽሽ::
(30) 30. ይህ የእውቀታቸው ጣሪያ (መጨረሻ) ነው:: ጌታህ ግን መንገዱን የሳተውን ሁሉ አዋቂ ነው:: የተቀናውንም እንዲሁ አዋቂ ነው።
(31) 31. በሰማያትና በምድር ውስጥ ያለው ሁሉ የአላህ ነው:: እነዚያን ያጠፉትን በተግባራቸው ለመመንዳትና እነዚያን መልካም የሰሩትንም በመልካሟ (በገነት) ሊመነዳ ነው::
(32) 32. እነርሱም ከጥቃቅን ጥፋቶች በቀር ከባባድ ወንጀሎችንና አጸያፊ ተግባሮችን የራቁ ናቸው:: ጌታህ ምህረተ ሰፊ ነው:: እርሱ ከምድር በፈጠራችሁ ጊዜም ሆነ በእናቶቻችሁ ማሕጸን ውስጥ ጽንሶች በሁናችሁበት ጊዜ ያውቃችኋል:: ስለዚህ እራሳችሁን አታሞግሱ:: እርሱ በትክክል የሚፈራውን ሰው ከሁሉም ይበልጥ አዋቂ ነው::
(33) 33. ያን ከእምነት የሸሸውን አየህን (እስቲ ንገረኝ)?
(34) 34. ጥቂትን ብቻ ሰጥቶ ያቋረጠውን፤
(35) 35, ለመሆኑ የሚያውቀው የሩቅ ሚስጢር አለውና እርሱንም ያያልን?
(36) 36. ወይስ በሙሳ ፅሁፍ ያለው አልተነገረውም?
(37) 37. በኢብራሂም (ትእዛዛቱን) በፈፀመው ያለውስ አልተነገረዉምን?
(38) 38. ይኸዉም ወንጀለኛ ነፍስ የሌላውን ነፍስ ወንጀል በፍጹም አትሸከምም::
(39) 39. የሰው ልጅም የለፋበትን ብቻ እንጂ ሌላ የለዉም::
(40) 40. የሰራውም ሁሉ ወደ ፊት ይታያል::
(41) 41. ከዚያም ጌታው ሙሉ ምንዳውን ይመነዳዋል::
(42) 42. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) የሁሉም መጨረሻው ወደ ጌታህ ብቻ ነው::
(43) 43. እርሱ ያ ያሳቀና ያስለቀሰ ነው::
(44) 44. እርሱ ያ የገደለና ሕያው ያደረገም ነው::
(45) 45. እርሱ ያ ጥንድን፤ ወንድንና ሴትን የፈጠረ ነው::
(46) 46. ይኸዉም ከፍትወት ጠብታ በማሕጸን ውስጥ በምትፈሰስ ጊዜ ነው::
(47) 47. ሌላውን ማስገኘትም በእርሱ ላይ ነው::
(48) 48. እርሱ ያ ሀብትን የሰጠና ያብቃቃ ነው::
(49) 49. እርሱ የሺዕራ ጌታ ነው::
(50) 50. እርሱ የቀድሞ ሰዎችን የአድ ሕዝቦችንም አጠፋ።
(51) 51. ሰሙድንም አጠፋ:: አንድንም አላስቀረም::
(52) 52. በፊትም የኑህን ህዝቦች አጥፍቷል:: እነርሱ እጅግ በዳዮችና በጣም አመጸኞች ነበሩና ነው::
(53) 53.የተገለበጡትንም ደፋ።
(54) 54. ባሸፈናት ሸፈናት::
(55) 55. (የሰው ልጅ ሆይ)፤ ከጌታህ ጸጋዎች በየትኛው ነው የምትጠራጠረው::
(56) 56. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ይህ ከቀድሞዎቹ አስጠንቃቂዎች አንዱ ነው::
(57) 57. ቀራቢቱም ቀረበች::
(58) 58. ከአላህ በስተቀር ገላጭ የላትም::
(59) 59. በዚህ ዘገባ ትደነቃላችሁን?
(60) 60 ትስቃላችሁን? አታለቅሱምን?
(61) 61. እናንተ ዘወትር ዘንጊዎች ናችሁን?
(62) 62. ለአላህ ስገዱ በብቸኝነትም አምልኩትም::