21 - Al-Anbiyaa ()

|

(1) 1. ለሰዎች እነርሱ በዝንጋታ ውስጥ መሰናዳትን የተዉ ሆነው ሳሉ ምርመራቸው ቀረበ::

(2) 2. ከጌታቸው አዲስ የተወረደ ቁርኣን አይመጣላቸዉም:: እነርሱ የሚያላግጡበት ሆነው ፤ የሚያዳምጡት ቢሆኑ እንጂ::

(3) 3.ልቦቻቸው ዝንጉዎች ሆነው። እነዚያም የበደሉት ሰዎች መንሾካሾክን ደበቁ:: «ይህ ብጤያችሁ ሰው እንጂ ሌላ ነውን? እናንተም የምታዩ ስትሆኑ ድግምትን ለመቀበል ትመጣላችሁን?» አሉ።

(4) 4. (ሙሐመድም) «ጌታዬ ቃልን ሁሉ በሰማይና በምድር ውስጥ ያለ ሲሆን ያውቃል:: እርሱም ሰሚና አዋቂ ነው።» አለ።

(5) 5. በእውነቱ «ቁርኣኑ የሕልሞች ቅዠቶች ነው። ይልቁንም ቀጠፈው፤ እንዲያዉም እርሱ ቅኔን ገጣሚ ነው:: የቀድሞዎቹም እንደ ተላኩ ሁሉ መልዕክተኛ ከሆነ በተዓምር ይምጣብን።» አሉ።

(6) 6. ከእነርሱ በፊት ያጠፋናት ከተማ አላመነችም:: ታዲያ እነርሱ ያምናሉን?

(7) 7.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከአንተም በፊት ወደእነሱ የምናወርድላቸው የኾነን ሰዎችን እንጂ ሌላን አላክንም፡፡ የማታውቁ ከሆናችሁ የመጽሐፉን ባለቤቶች ጠይቁ::

(8) 8.ምግብን የማይበላ አካልም አላደረግናቸዉም:: ዘውታሪዎችም አልነበሩም::

(9) 9.ከዚያ ቀጠሮን ሞላንላቸውና እነርሱንና የምንሻውን ሰው አዳንናቸዉም:: ወሰን አላፊዎችንም አጠፋን::

(10) 10. (ሙስሊሞች ሆይ!) ክብራችሁ በውስጡ ያለበትን መጽሐፍ ወደእናንተ በእርግጥ አወረድን፡፡ አታውቁምን?

(11) 11. በዳይም ከነበረች ከተማ ያጠፋናትና ከኋላዋም ሌሎችን ህዝቦች ያስገኘነው ብዙ ናት::

(12) 12. ቅጣታችንም በተሰማቸው ጊዜ እነርሱ ወዲያውኑ ከርሷ ለመሸሽ ይገሰግሳሉ።

(13) 13. «አትገስግሱ፤ ትጠየቁም ይሆናልና በእርሱ ወደ ተቀማጠላችሁበት ጸጋ ወደ መኖሪያዎቻችሁም ተመለሱ።» ይባላሉ።

(14) 14. «ዋ ጥፋታችን! እኛ በእርግጥ በዳዮች ነበርን።» ይላሉ።

(15) 15.የታጨዱ ሬሳዎችም እስካደረግናቸው ድረስ ይህቺ ጥሪያቸው ከመሆን አልተወገደችም::

(16) 16. ሰማይንና ምድርን በመካከላቸው ያለውንም ሁሉ ቀላጆች ሆነን አልፈጠርንም::

(17) 17.መጫዎቻን (ሚስትንና ልጅን) ልንይዝ በሻን ኖሮ ከኛ ዘንድ በያዝነው ነበር፤ ግን ሰሪዎች አይደለንም።

(18) 18. በእርግጥ እውነትን በውሸት ላይ እንጥላለን:: አንጎሉን ያፈርሰዋልም:: ወዲያዉም እርሱ ጠፊ ነው:: ለእናንተም ከዚያ (ሚስትና ልጅ) አለው በማለት ከምትመጥኑት ነገር ብርቱ ቅጣት አላችሁ:: (ወዮላችሁ)

(19) 19. በሰማያትና በምድር ዉስጥ ያለው ሁሉም የእርሱ ብቻ ነው:: እርሱ ዘንድ ያሉትም መላእክት እርሱን ከመገዛት አይኮሩም:: አይሰለቹምም።

(20) 20. በበሌሊትና በቀንም ያጠሩታል:: አይታክቱም።

(21) 21. ይልቁንም ከምድር የሆኑን ሙታንን የሚያስነሱ አማልክትን ያዙን? የለም።

(22) 22.በሰማያትና በምድር ውስጥ ከአላህ ሌላ አማልክት በነበሩ ኖሮ ሁለቱም በተበላሹ ነበር:: የዐርሹ ጌታ አላህም ከሚሉት ሁሉ ጠራ::

(23) 23. አላህ ከሚሰራው ሁሉ አይጠየቅም:: እነርሱ (ፍጥረቶቹ) ግን ይጠየቃሉ::

(24) 24. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ይልቁንም ከርሱ ሌላ አማልክትን ያዙን? «አስረጃችሁን አምጡ:: ይህ ቁርኣን እኔ ዘንድ ያለው ህዝብ መገሰጫ፤ ከኔ በፊትም የነበሩት ህዝቦች መገሠጫ ነው።» በላቸው:: እንዲያዉም አብዛኞቻቸው እውነቱን አያውቁም:: ስለዚህ እነርሱ እንቢተኞች ናቸው::

(25) 25. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ካንተ በፊትም እነሆ ከእኔ ሌላ አምላክ የለምና ተገዙኝ በማለት ወደ እርሱ የምናወርድለት ቢሆን እንጂ ከመልዕክተኛ አንድንም አላክንም::

(26) 26. «አር-ረሕማንም ከመላእክት መካከል ልጅን ያዘ።» አሉ። ጥራት ተገባው። አይደለም መላእክት የተከበሩ ባሮች ብቻ ናቸው።

(27) 27. በንግግር አይቀድሙትም፤ ያዘዘውንም ይፈጽማሉ።

(28) 28.በፊታቸው ያለውንና በኋላቸው ያለውንም ሁሉ ያውቃል:: ለወደደውም እንጂ ለሌላው አያማልዱም:: እነርሱም እርሱን ከመፍራታቸው የተነሳ ተጨናቂዎች ናቸው::

(29) 29. ከእነርሱም «እኔ ከእርሱ ሌላ አምላክ ነኝ።» የሚል ያንን ገሀነምን እንመነዳዋለን፤ በዳዮችን እንደዚሁ እንመነዳለን።

(30) 30. እነዚያም በአላህ የካዱ ሰዎች ሰማያትና ምድር የተጣበቁ የነበሩና የለያየናቸው መሆናችንን አያውቁምን? ህያው የሆነንም ነገር ሁሉ ከውሃ ፈጠርን። አያምኑምን?

(31) 31. በምድርም ውስጥ በእነርሱ እንዳታረገርግ ጋራዎችን አደረግን። ይመሩም ዘንድ በእርሷ ውስጥ ሰፋፊ መንገዶችን አደረግን።

(32) 32. ሰማይንም ከመውደቅ የተጠበቀ ጣራ አደረግን:: እነርሱ ግን ከተዓምራቱ ዘንጊዎች ናቸው::

(33) 33.እርሱም ሌሊትንና ቀንን ጸሐይንና ጨረቃንም የፈጠረ ነው:: ሁሉም በየ ምህዋራቸው (ፈለካቸው) ውስጥ ይዋኛሉ::

(34) 34. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ካንተ በፊት ለማንም ሰው ዘለዓለም መኖርን አላደረግንም:: ታዲያ ብትሞት እነርሱ ዘውታሪዎች ናቸውን?

(35) 35.(ሰዎች ሆይ!) ነፍስ ሁሉ ሞትን ቀማሽ ናት:: ለመፈተንም በክፉም በበጎም እንሞክራችኋለን:: ወደ እኛም ትመለሳላችሁ::

(36) 36. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እነዚያም በአላህ የካዱት ሰዎች ባዩህ ጊዜ መሳለቂያ አድርገው እንጂ አይዙህም። እነርሱ በአር-ረህማን መወሳት እነርሱ ከሓዲያን ሲሆኑ: «ያ አማልክቶቻችሁን በክፉ የሚያነሳቸው ይህ ነውን?» ይላሉ።

(37) 37. ሰው ቸኳይ ሆኖ ተፈጠረ:: ታዓምራቶቼን በእርግጥ አሳያችኋለሁና አታቻኩሉኝ::

(38) 38. «እውነተኞች ከሆናቸሁ ይህ ቀጠሮም መቼ ነው?» ይላሉ።

(39) 39.እነዚያ በአላህ የካዱ ሰዎች ከፊቶቻቸውና ከጀርቦቻቸው ላይ እሳትን የማይከለክሉበትን እነርሱም የማይረዳዱበትን ጊዜ ቢያውቁ ኖሮ ይህንን አይሉም ነበር::

(40) 40. ይልቁንም ሰዓቲቱ በድንገት ትመጣቸዋለች:: ታስደነግጣቸዋለችም:: መመለሷንም አይችሉም:: እነርሱም የሚቆይላቸው አይደሉም።

(41) 41. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ካንተ በፊትም የነበሩት መልዕክተኞች በእርግጥ ተቀለደባቸው፤ በእነዚያ ከእነርሱ ይቀልዱ በነበሩት ይሳለቁበት የነበሩት ቅጣት ሰፈረባቸው።

(42) 42. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «ከአር-ረህማን ቅጣት በሌሊትና በቀን የሚጠብቃችሁ ማነው?» በላቸው:: በእውነቱ እነርሱ ከጌታቸው ግሠጼ ከቁርኣን ዘንጊዎች ናቸው::

(43) 43.ለእነርሱ ከእኛ ሌላ የምትከላከልላቸው አማልዕክት አለቻቸውን? ነፍሶቻቸውን መርዳትን አይችሉም:: እነርሱም (ከሓዲያኑ) ከእኛ አይጠብቁም።

(44) 44.በእውነትም እነዚህንና አባቶቻቸውን በእነርሱ ላይ ዕድሜ እስከ ረዘመባቸው ድረስ አጣቀምናቸው:: ተታለሉም። እኛ ምድርን ከጫፎቿ የምናጎድላት ሆነን ስንመጣባት አያዩምን? እነርሱ አሸናፊዎች ናቸውን?

(45) 45. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «የማስፈራራችሁ በተወረድልኝ ብቻ ነው። ግን ደንቆሮዎች በሚስፈራሩበት ጊዜ ጥሪን አይሰሙም።» በላቸው።

(46) 46. ከጌታህ ቅጣትም ወላፈን ብትነካቸው «ዋ ጥፋታችን! እኛ በዳዮች ነበርን።» ይላሉ።

(47) 47.በትንሳኤ ቀን ትክክለኛ ሚዛኖችን እናቆማለን:: ማንኛይቱም ነፍስ ምንንም አትበደልም:: ስራው የሰናፍጭ ቅንጣት ያክል ቢሆንም እርሷን እናመጣታለን:: ተቆጣጣሪነትም በእኛ በቃ::

(48) 48. ለሙሳና ለሃሩንም እውነትንና ውሸትን የሚለይን ብርሃንን ለጥንቁቆችም መገሰጫን በእርግጥ ሰጠናቸው::

(49) 49. ለእነዚያ ጌታቸውን በሩቅ ለሚፈሩት እነርሱም ከሰዓቲቱ ተጨናቂዎች ለሆኑት መገሰጫን ሰጠን::

(50) 50.ይህም (ቁርኣን) ያወረድነው የኾነ ብሩክ መገሰጫ ነው፡ ታዲያ እናንተ ለእርሱ ከሓዲያን ናችሁን?

(51) 51. ለኢብራሂምም ከዚያ በፊት ቅን መንገዱን በእርግጥ ሰጠነው:: እኛም በእርሱ ተገቢነት አዋቂዎች ነበርን::

(52) 52. ለአባቱና ለህዝቦቹ፡- «ይህቺ ቅርጻ ቅርጽ ያቺ እናንተ ለእርሷ ተገዢዎች የሆናችኃት ምንድን ናት?» ባለ ጊዜ መራነው።

(53) 53. «አባቶቻችንን ለእርሷ ተገዢዎች ሆነው አገኘን።» አሉት።

(54) 54. «እናንተም አባቶቻችሁም በእርግጥ በግልጽ ስህተት ውስጥ ነበራችሁ።» አላቸው።

(55) 55. «በምሩ መጣህልን? ወይንስ አንተ ከሚቀልዱት ነህ?» አሉት።

(56) 56. (እርሱም) አለ: «አይደለም። ጌታችሁ የሰማያትና የምድር ጌታ ያ የፈጠራቸው ነው:: እኔም በይሃችሁ ላይ ከመስካሪዎች ነኝ።

(57) 57. «በአላህ እምላለሁ ዟሪዎች ሆናችሁ ከሄዳችሁ በኋላ ጣዖቶቻችሁን ተንኮል እሰራባቸዋለሁ።» አለ።

(58) 58. ዘወር ሲሉም ስብርብሮች አደረጋቸው:: ለእነርሱ የሆነ አንድ ትልቅ ጣዖት ብቻ ሲቀር :: ወደ እርሱ ይመለሱ ዘንድ እርሱን ብቻ ተወው።

(59) 59. «በአማልክቶቻችን ይህንን የሰራ ማነው? እርሱ በእርግጥ ከበደለኞች ነው።» አሉ።

(60) 60. «ኢብራሂም የሚባል ጎበዝ (ወጣት) በመጥፎ ሲያነሳቸው ሰምተናል።» ተባባሉ።

(61) 61. «ይመሰክሩበት ዘንድ በሰዎች ዓይን ፊት ላይ አምጡት።» አሉ።

(62) 62. «ኢብራሂም ሆይ! በአማልክቶቻችን ይህንን የሰራህ አንተ ነህን?» አሉት።

(63) 63. «አይደለም:: ይህ ትልቃቸው ሰራው፤ ይናገሩም እንደ ሆነ ጠይቋቸው።» አለ።

(64) 64. ወደ ነፍሶቻቸዉም ተመለሱ: «እናንተ በመጠየቃችሁ በዳዮቹ እናንተው ናችሁ።» ተባባሉም።

(65) 65. ከዚያም በራሶቻቸው ላይ ተገለበጡና «እነዚህ የሚናገሩ አለመሆናቸውን በእርግጥ አውቀሃል።» አሉ።

(66) 66.ኢብራሂምም አላቸው: «ታዲያ ለእናንተ ብታመልኳቸው ምንም የማይጠቅማችሁንና ባታመልኳቸዉም በምንም ነገር የማይጎዳችሁን ጣዖታትን ከአላህ ሌላ ትገዛላችሁን?

(67) 67. «ኡፍ! ለእናንተም ሆነ ከአላህ ሌላ ለምትገዙት ጣዖታት። አታስተውሉምን?» አለ።

(68) 68. «ሰሪዎች (ተቆርቋሪዎች) እንደ ሆናችሁ ኢብራሂምን በእሳት አቃጥሉት አማልክቶቻችሁንም እርዱ።» አሉ:: (በእሳት ላይ ጣሉትም።)

(69) 69. «እሳት ሆይ! በኢብራሂም ላይ ቀዝቃዛና ሰላም ሁኚ።» አልን።

(70) 70. በእርሱም ተንኮልን አሰቡ። በጣም ከሳሪዎች አደረግናቸው።

(71) 71. እርሱንና ሉጥንም ወደዚያች በውስጡ ለዓለማት በረከትን ወደ አደረግንባት ምድር በመውሰድ አዳንናቸው::

(72) 72.ለእርሱም ኢስሐቅን ያዕቆብንም ተጨማሪ አድርገን ሰጠነው:: ሁሉንም መልካሞች አደረግን::

(73) 73. በትእዛዛችንም ወደ በጎ ስራ የሚመሩ መሪዎች አደረግናቸው:: ወደነሱም መልካም ስራዎችን መስራትን፤ ሶላትንም መስገድን ዘካንም መስጠትን አወረድን:: ለእኛም ተገዢዎች ነበሩ::

(74) 74. ሉጥንም ፍርድንና ዕውቀትን ሰጠነው:: ከዚያችም መጥፎ ስራዎችን ትሰራ ከነበረችው ከተማ አዳንነው:: እነርሱ ክፉ ሰዎች አመጸኞች ነበሩና::

(75) 75. በችሮታችንም ውስጥ አስገባነው:: እርሱ ከመልካሞች አንዱ ነውና::

(76) 76.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ኑሕንም ከዚያ በፊት ጌታውን በጠራ ጊዜ የሆነውን አስታውስ:: ለእርሱም ጥሪውን ተቀበልነው፤ እርሱንም ቤተሰቦቹንም ከከባድ ጭንቅ አዳን::

(77) 77.ከእነዚያም በታዓምራቶቻችን ከአስተባበሉት ህዝቦች ተንኮል ጠበቅነው:: እነርሱ ክፉ ህዝቦች አመጸኞች ነበሩና ሁሉንም አሰመጥናቸዉም::

(78) 78.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ ! ) ዳውድንና ሱለይማንንም በአዝመራው ነገር በሚፈርዱ ጊዜ የህዝቦቸ ፍየሎች ሌሊት በእርሱ ውስጥ በተሰማሩ ጊዜ አስታውስ:: ፍርዳቸውንም አዋቂዎች ነበርን::

(79) 79. ለሱለይማንም ትክክለኛይቱን ፍርድ አሳወቅነው:: ለሁሉም ጥበብንና እውቀትን ሰጠን:: ተራራዎችን ከዳውድ ጋር የሚያወድሱ ሲሆን ገራን፤ አእዋፍንም እንደዚሁ ገራን ሰሪዎችም ነበርን።

(80) 80.የብረት ልብስንም ስራ ለእናንተ ከጦራችሁ ትጠብቃችሁ ዘንድ አስተማርነው:: እናንተ አመስጋኞች ናችሁን?

(81) 81. ለሱለይማንም ነፋስን በኃይል የምትነፍስ በትእዛዙ ወደዚያች በእርሷ ውስጥ በረከትን ወደ አደረግንባት ምድር (ወደ ሻም) የምትነፍስ ስትሆን (ገራንለት) በነገሩ ሁሉም አዋቂዎች ነበርን::

(82) 82.ከሰይጣናትም ለእርሱ (ሉልን ለማውጣት) የሚጠልሙንና ከዚያ ሌላ ያለን ስራ የሚሰሩን ገራንለት፤ ለእነርሱም ተጠባባቂዎች ነበርን::

(83) 83. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አዩብንም ጌታውን «እኔ መከራ አገኘኝ:: አንተም ከአዛኞች ሁሉ ይበልጥ አዛኝ ነህ።» ሲል በተጣራ ጊዜ የሆነውን አስታውስ።

(84) 84. ለእርሱም ጥሪውን ተቀበልነው፤ ከጉዳትም በእርሱ ላይ የነበረውን ሁሉ አስወገድን:: ቤተሰቦቹንም ከእነርሱም ጋር መሰላቸውን ከእኛ ዘንድ ለችሮታና ለተገዢዎች ለማስገንዘብ ሰጠነው::

(85) 85. ኢስማዒልንም፤ ኢድሪስንም፤ ዙልኪፍልንም፤ አስታውስ:: ሁሉም ከታጋሾች ናቸው::

(86) 86. በችሮታችንም ውስጥ አስገባናቸው:: እነርሱ ከመልካሞቹ ናቸውና::

(87) 87. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) የዓሳውንም ባለቤት ተቆጥቶ በሄደ ጊዜ የሆነውን አስታውስ:: በእርሱም ላይ ፈጽሞ የማንፈርድበት መሆናችንን ጠረጠረ:: ዓሳም ዋጠው:: በጨለማዎችም ውስጥ ሆኖ «ካንተ በስተቀር ሌላ አምላክ የለም ጥራት ይገባህ:: እኔ በእርግጥ ከበዳዮች ነበርኩ።» በማለት ተጣራ።

(88) 88. ለእርሱም ጥሪውን ተቀበልነው:: ከጭንቅም አዳነው:: ልክ እንደዚሁም ምዕምናንን እናድናለን::

(89) 89. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ዘከሪያንም «ጌታዬ ሆይ! ብቻዬን አትተወኝ:: አንተም ከወራሾች ሁሉ በላጭ ነህ።» ሲል ጌታውን በተጣራ ጊዜ አስታውስ።

(90) 90. ለእርሱም ጥሪውን ተቀበልነው:: ለእርሱም የህያን ሰጠነው:: ለእርሱም ሚስቱን አበጀንለት:: እነርሱ በበጎ ስራዎች የሚቻኮሉ ከጃዮችና ፈሪዎች ሆነው የሚለምኑንም ነበሩ:: ለእኛ ተዋራጆችም ነበሩ::

(91) 91.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ያችንም ብልቷን (ከዝሙት) የጠበቀችውንና በእርሷም ውስጥ ከመንፈሳችን የነፋንባትን እርሷንም ሆነ ልጇን ለዓለማት ተዓምር ያደረግናትን መርየምን አስታውስ::

(92) 92. እነዚህ ህግጋት አንድ መንገድ ሲሆኑ በእርግጥ የሃይማኖታችሁ ህግጋት ናቸው:: እኔም ጌታችሁ ነኝና ተገዙኝ::

(93) 93.በሃይማኖታቸዉም ነገር በመካከላቸው ተለያዩ:: ሁሉም ወደ እኛ ተመላሾች ናቸው::

(94) 94. እርሱ ያመነ ሆኖ ከበጎ ስራዎች ማንኛውንም የሚሰራም ምንዳውን አይነፍግም፤ እኛም ለእርሱ መዝጋቢዎች ነን::

(95) 95. ባጠፋናትም ከተማ ላይ ዘበት ነው፤ (ወደ ዱኒያ) አይመለሱምና።

(96) 96.የዕጁጅና መዕጁጅም እነርሱ ከየሸንተረሩ የሚንደረደሩ ሲሆኑ ግድባቸው በተከፈተች ጊዜ ፤

(97) 97. እውነተኛዉም ቀጠሮ በቀረበ ጊዜ ያንን ጊዜ እነሆ የእነዚያ ከሀዲያን ዓይኖች ይፈጥጣሉ:: «ዋ ጥፍታችን! ከዚያ ቀን በእርግጥ በዝንጋቴ ላይ ነበርን:: በእውነትም በዳዮች ነበርን።» ይላሉ።

(98) 98. (ከሓዲያን ሆይ!) እናንተና ከአላህ ሌላ የምትገዟቸው ጣዖታት የገሀነም ማገዶዎች ናችሁ:: እናንተ ለእርሷ ወራጆች ናችሁ::

(99) 99.እነዚህ ጣዖታት አማልክት በነበሩ ኖሮ ገሀነምን አይገቧትም ነበር:: ግን ሁሉም በእርሷ ውስጥ ዘውታሪዎች ናቸው::

(100) 100.እነርሱ በእርሷ ውስጥ ይንሰቀሰቃሉ:: እነርሱም በውስጧ ምንንም አይሰሙም::

(101) 101. እነዚያ ከእኛ መልካሟ ቃል ለእነርሱ ያለፈችላቸው እነዚያ ከእርሷ የተራቁ ናቸው::

(102) 102. ድምጿንም አይሰሙም:: እነርሱም ነፍሶቻቸው በሚሹት ነገር ውስጥ ዘውታሪዎች ናቸው::

(103) 103. ታላቁ ድንጋጤ አያስተክዛቸዉም:: መላእክትም «ይህ ያ ! ትቀጠሩት የነበራችሁት ቀናችሁ ነው።» እያሉ ይቀበሏቸዋል።

(104) 104. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ለመጽሐፎች ገፆች እንደሚጠቀለሉ ሁሉ ሰማይን የምንጠቀልልበትን ቀን አስታውስ:: የመጀመሪያን ፍጥረት እንደ ጀመርን እንመልሰዋለን:: ይህን መፈጸሙ የማይቀር ቀጠሮን ቀጠርን:: እኛ የቀጠርነውን ሰሪዎች ነን::

(105) 105. ምድርንም መልካሞቹ ባሮቼ ይወርሷታል ማለትን ከመጽሐፉ (ከተጠበቀው ሰሌዳ) በኋላ በመጽሐፎች በእርግጥ ጽፈናል::

(106) 106.በዚህ ቁርኣን ውስጥ ያሉት ህግጋት ለአላህ ተገዢ ህዝቦች ሁሉ በቂ ናቸው።

(107) 107. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ለዓለማት እዝነት አድርገን እንጂ አልላክንህም::

(108) 108. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «ያ ወደ እኔ የሚወርደው መልዕክት ‹አምላካችሁ አንድ አምላክ ብቻ ነው።› የሚል ነው:: ታዲያ እናንተ ፍጹም ታዛዦች ናችሁን?» በላቸው።

(109) 109. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እምቢ ቢሉም (እንዲህ) በላቸው: «የታዘዝኩትን በእኩልነት አሳውቂያችኋለሁ:: የምትስፈራሩበትም ነገር ቅርብ ወይም ሩቅ መሆኑን አላውቅም።

(110) 110. «እርሱ ከንግግር ጩኸቱን ያውቃል:: የምትደብቁትንም ሁሉ ያውቃል::

(111) 111. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «እርሱም ቅጣትን ማቆየት ምናልባት ለእናንተ ፈተናና እስከ ጊዜው መጣቀሚያ እንደ ሆነም አላውቅም።» በላቸው::

(112) 112. «ጌታዬ ሆይ! በእውነት ፍረድ:: ጌታችንም እጅግ በጣም ሩህሩህን በምትሉት ነገር ላይ መታገዣ ነው።» አለ::