63 - Al-Munaafiqoon ()

|

(1) 1. አስመሳዮች በመጡህ (ወደ አንተ በመጡ) ጊዜ «አንተ የአላህ መልዕክተኛ መሆንህን በእርግጥ (ምለን) እንመሰክራለን» ይላሉ:: አላህም አንተ በእርግጥ መልዕክተኛው መሆንህን ያውቃል:: አላህም አስመሳዮችን ውሸታሞች መሆናቸውን ይመሰክራል::

(2) 2. መሓላዎቻቸውን ጋሻ አድርገው ያዙ:: ከአላህም መንገድ ከለከሉ:: እነርሱ ይሰሩት የነበሩት ነገር ሁሉ ከፋ::

(3) 3. ይህ እነርሱ (በምላስ) አምነው ከዚያም (በልብ) የካዱ በመሆናቸው በልቦቻቸዉም ላይ ታተመባቸው:: ስለዚህ እነርሱ አያውቁም::

(4) 4. ባየሃቸው ጊዜ አካሎቻቸው ያስደንቁሃል:: ቢናገሩም ንግግራቸውን ታዳምጣለህ:: እነርሱ ልክ ወደ ግድግዳ የተጠጉ ግንዶችን ይመስላሉ:: ጩኸትን ሁሉ በእነርሱ ላይ ነው ብለው ያስባሉ:: እነርሱ ጠላቶች ናቸውና ተጠንቀቃቸው:: አላህ ይጋደላቸው:: (ከእምነት) እንዴት ይመለሳሉ (ያፈገፍጋሉ)::

(5) 5. ለእነርሱም፡- «ኑ የአላህ መልዕክተኛ ለእናንተ ምህረትን ይለምንላችኋል» በተባሉ ጊዜ በማፌዝ ራሶቻቸውን ያዞራሉ:: እነርሱም ትዕቢተኞች ሆነው ሲሸሹ ታያቸዋለህ::

(6) 6. ምህረትን ብትለምንላቸውም ባትለምንላቸዉም በእነርሱ ላይ ሁሉም እኩል ነው:: አላህ ለእነርሱ በፍጹም አይምርም:: አላህ አመጸኛ ህዝቦችን አይመራምና::

(7) 7. እነርሱ፡- «እነዚያ ከአላህ መልዕክተኛ ዘንድ ያሉት ሰዎች እስከ ሚበታተኑ ድረስ ምጽዋት አትስጡ» የሚሉ ናቸው:: የሰማያትና የምድር ድልቦች የአላህ ብቻ ናቸው:: ግን አስመሳዮች አይገነዘቡም::

(8) 8. «ወደ መዲና ብንመለስ አሸናፊው ወራዳውን በእርግጥ ከእርሷ ያስወጣል» ይላሉ:: አሸናፊነትም ለአላህ ለመልዕክተኛው እና ለምዕምና ብቻ ነው:: ግን አስመሳዮች አያውቁም::

(9) 9. እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ገንዘቦቻችሁና ልጆቻችሁ አላህን ከማስታወስ አያታልሏችሁ (አያዘናጓችሁ):: ይህንንም የሚሰሩ ሰዎች እነዚያ እነርሱ ከሳሪዎች ናቸው::

(10) 10. አንዳችሁም ሞት ሳይመጣበትና «ጌታየ ሆይ! እንድመጸውትና ከደጋጎችም ሰዎች እንድሆን ጥቂት ጊዜ ብታቆየኝ ኖሮ እመኛለሁ» ከማለቱ በፊት ከሰጠናችሁ ሲሳይ ለግሱ።

(11) 11. ማንኛይቱም ነፍስ የሞት ጊዜዋ በመጣባት ጊዜ አላህ በፍጹም አያቆያትም:: አላህም በምትሰሩት ሁሉ ውስጠ አዋቂ ነው::