39 - Az-Zumar ()

|

(1) 1. የመጽሐፉ መወረድ አሸናፊና ጥበበኛ ከሆነው ከአላህ ነው::

(2) 2. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እኛ ወደ አንተ መጽሐፉን በእውነት የተሞላ ሲሆን አወረድነው:: አላህንም ሃይማኖትን ለእርሱ ብቻ ያጠራህ ሆነህ ተገዛው::

(3) 3. (ሙስሊሞች ሆይ!) አስተውሉ ፍጹም ጥሩ የሆነው ሃይማኖት ለአላህ ብቻ ነው:: እነዚያ ከእርሱ ሌላ ጣዖታትን ረዳቶች አድረገው የያዙት ሁሉ «ወደ አላህ ማቃረብን እንዲያቃርቡን በማሰብ እንጂ ለሌላ አንገዛቸዉም።» ይላሉ:: አላህ በዚያ እነርሱ በሚለያዩበት ነገር በመካከላቸው ይፈርዳል:: አላህም ውሸታምንና ከሓዲ የሆነን ሰው አያቀናም::

(4) 4. አላህ ልጅን መያዝ በፈለገ ኖሮ ከሚፈጥረው ውስጥ የሚሻውን ይመርጥ ነበር:: ጥራት ተገባው:: እርሱ አሸናፊውና ብቸኛው አንዱ አላህ ነው::

(5) 5. አላህ ሰማያትንና ምድርን በእውነት ፈጠረ:: ሌሊቱንም በቀን ላይ ይጠቀልላል:: ቀኑንም በሌሊት ላይ እንዲሁ ይጠቀልላል:: ጸሐይንና ጨረቃንም ገራ:: ሁሉም ለተወሰነ ጊዜ ይሮጣሉ:: (ሙስሊሞች ሆይ!) አስተውሉ! እርሱ አሸናፊዉና መሀሪው ነውና::

(6) 6. (ሰዎች ሆይ!) ከአንዲት ነፍስ ፈጠራችሁ:: ከዚያም ከእርሷ መቀናጆዋን ፈጠረ:: ለእናንተም ከግመልና ከዳልጋ ከብት፤ ከፍየልና ከበግ ስምንት አይነቶችን (ጥንዶችን) አወረደ:: በእናቶቻችሁ ሆዶች ውስጥ በሶስት ጨለማዎች ውስጥ ከመፍጠር በኋላ ሙሉ መፍጠርን ይፈጥራችኋል፤ ይህን ያደረገው ጌታችሁ አላህ ነው:: ስልጣኑም የእርሱ ብቻ ነው:: ከእርሱ ሌላ ትክክለኛ አምላክ የለም:: ታዲያ ወዴት ትዞራላችሁ::

(7) 7. በአላህ ብትክዱ አላህ ከናንተ የተብቃቃ ነው:: ለባሪያዎቹም ክህደትን አይወድም፤ ብታመሰግኑም እርሱን ይወድላችኋል:: ማንኛይቱም ኃጢአትን ተሸካሚ ነፍስ የሌላይቱን ኃጢአት አትሸከምም:: ከዚያም የሁላችሁም መመለሻችሁ ወደ ጌታችሁ ብቻ ነው:: ትሰሩት የነበራችሁትንም ሁሉ ይነግራችኋል:: እርሱ በልቦች ውስጥ ያሉትን ሁሉ አዋቂ ነውና::

(8) 8. የሰውን ልጅ ጉዳት ባገኘው ጊዜ ወደ እርሱ ተመላሽ ሆኖ ጌታወን ይጠራል:: ከዚያም ከእርሱ ዘንድ ጸጋን በሰጠው ጊዜ ያንን ከዚያ በፊት ወደ እርሱ ይጸልይበት የነበረውን መከራ ይረሳል:: ከመንገዱ ለማሳሳትም ለአላህ ባላንጣዎችን ያደርጋል:: ለእንዲህ አይነቱ ሰው «በክህደት ጥቂትን ተጣቀም፤ አንተ በእርግጥ ከእሳት ጓዶች ነህ።» በለው።

(9) 9. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ያ የመጨረሻይቱን ዓለም ቅጣት የሚፈራ የጌታውንም ችሮታ የሚከጅል ሲሆን በሌሊት ሰዓቶችም ሰጋጅና ቋሚ ሆኖ ለጌታው የሚገዛ ሰው (እንደ ተስፋ ቢሱ ከሓዲ ነውን? በለው።) «እነዚያ የሚያውቁና እነዚያ የማያውቁ ይስተካከላሉን?» በላቸው:: የሚገሰፁት ባለ አእምሮዎች ብቻ ናቸው።

(10) 10. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) (ጌታችሁ) «እናንተ ያመናችሁ ባሮቼ ሆይ! ጌታችሁን ፍሩ፡፡ ለነዚያ በዚህች በቅርቢቱ ዓለም መልካም ለሠሩት መልካም ምንዳ አላቸው፡፡ የአላህ ምድርም ሰፊ ናት፤ (ብትቸገሩ ተሰደዱ)፡፡ ታጋሾቹ ምንዳቸውን የሚሰጡት ያለግምት ነው» (ይላል) በላቸው፡፡

(11) 11. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ! እንዲህ) በል: «እኔ አላህን ሃይማኖትን ለእርሱ ያጠራሁ ሆኜ እንድገዛው ታዘዝኩ።

(12) 12. «የሙስሊሞች መጀመሪያ እንድሆን ታዘዝኩ» በል።

(13) 13. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «እኔ ከጌታዬ ባምጽ የታላቁን ቀን ቅጣት እፈራለሁ» በል::

(14) 14. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) (እንዲህ) በል: «አላህን ሃይማኖቴን ለእርሱ ያጠራሁ ሆኜ እገዛዋለሁ።

(15) 15. «ከእርሱ ሌላ የሻችሁትን ተገዙ:: ከሳሪዎች ማለት እነዚያ በትንሳኤ ቀን ነፍሶቻቸውንና ቤተሰቦቻቸውን ያከሰሩ ናቸው። ሰዎች ሆይ! አስተዉሉ:: ግልጽ ከሳራ ማለት ይህ ነው።» በላቸው።

(16) 16. ለእነርሱ ከበላያቸው ከእሳት የሆኑ ድርብርብ ጥላዎች አሏቸው:: ከስራቸዉም እንዲሁ:: ይህ አላህ ባሮቹን እንዲጠነቀቁ በእርሱ ያስፈራራበታል:: ባሮቼ ሆይ! ስለዚህ ፍሩኝ::

(17) 17. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እነዚያም ጣዖታትን ከመገዛት የራቁ እና ወደ አላህ የዞሩ ሁሉ ለእነርሱ ታላቅ ብስራት አላቸው። ስለዚህ ባሮቼን አብስር፡፡

(18) 18. እነዚያን ንግግርን የሚያዳምጡትንና መልካምን የሚከተሉትን (ባሮቼን አብስር)፤ እነዚያ አላህ ወደ ቀናው መንገድ የመራቸው ናቸው። እነዚያም እነርሱ ባለ አእምሮዎቹ ናቸው።

(19) 19. በእርሱ ላይ የቅጣት ቃል የተረጋገጠችበትን (ትመራዋለህን?) አንተ በእሳት ውስጥ ያለን ታድናለህን?

(20) 20. ግን እነዚያ ጌታቸውን የፈሩ፤ ለእነርሱም ከበላያቸው የታነጹ ሰገነቶች ያሏቸው ሰገነቶች ከስሮቻቸውም ወንዞች የሚፈሱባቸው የሆኑ አሏቸው:: (ይህንን) አላህ ቃል ገባላቸው፤ አላህም ቃሉን አያፈርስም::

(21) 21. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አላህ ከሰማይ ውሃን እንዳወረደና በምድር ውስጥ ምንጮች አድርጎ እንዳስገባው አላየህምን? ከዚያም በእርሱ ብዙ አይነቶች የሆኑ የተለያዩ አዝመራዎችን ያወጣበታል:: ከዚያም ይደርቃል:: ገርጥቶም ታየዋለህ:: ከዚያ ስብርብር ያደርገዋል፤ በዚህ ውስጥ ለባለ አእምሮዎች ግሳፄ አለበት::

(22) 22. አላህ ደረቱን ለእስልምና ያሰፋለትና እርሱም ከጌታው ዘንድ በብርሃን ላይ የሆነ ሰው (ልቡ እንደ ደረቀ ሰው ነውን?) ልቦቻቸዉም ከአላህ መወሳት ለደረቁ ሰዎች ወየውላቸው፤ እነዚያ በግልጽ መሳሳት ውስጥ ናቸው::

(23) 23. አላህ ከዜና ሁሉ መልካምን ተመሳሳይ ተደጋጋሚ የሆነን መጽሐፍ (ቁርኣንን) አወረደ:: ከእርሱ ግሳፄ የእነዚያ ጌታቸውን የሚፈሩት ሰዎች ቆዳዎች ይኮማተራሉ:: ከዚያም ቆዳዎቻቸውና ልቦቻቸው ወደ አላህ ተስፋ ማስታወስ ይለዝባሉ:: ይህ የአላህ መምሪያ ነው፤ በእርሱ የሚሻዉን ሰው ይመራበታል። አላህም የሚያጠመውን ሰው ለእርሱ ምንም አቅኝ የለዉም::

(24) 24. በትንሳኤ ቀን ክፉን ቅጣት በፊቱ የሚመክት ሰው (ከቅጣቱ እንደዳነው ነውን?) ለበዳዮችም «ትሰሩት የነበራችሁን ቅጣትን ቅመሱ» ይባላሉ።

(25) 25. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከእነርሱ በፊት የነበሩት አስተባበሉ:: ቅጣቱም ከማያውቁት በኩል መጣባቸው::

(26) 26. አላህም በቅርቢቱ ሕይወት ውርደትን አቀመሳቸው:: የመጨረሻይቱም ዓለም ቅጣት በጣም ትልቅ ነው:: የሚያውቁ ቢሆኑ ኖሮ አያስተባብሉም ነበር::

(27) 27. በዚህም ቁርኣን ውስጥ ለሰዎች ይገሰጹ ዘንድ ከየምሳሌው ሁሉ በእርግጥ አብራራን::

(28) 28. መዛባት የሌለበት ዐረብኛ ቁርኣን ሲሆን (አብራራነው):: ሊጠነቀቁ ይከጀላልና::

(29) 29. አላህ በእርሱ ተጨቃጫቂዎች የሆኑ ተጋሪዎች ያሉትን ባሪያና ለአንድ ሰው ብቻ ንጹህ የሆነን ባሪያ ለሚያጋራና በአንድነት ለሚያምን ሰው ምሳሌ አደረገ። በምሳሌ ይስተካካላሉን? ምስጋና ሁሉ ለአላህ ይገባው:: በእውነቱ አብዛኞቻቸው አያውቁም::

(30) 30. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አንተም ሟች ነህ፤ እነርሱም ሟቾች ናቸው::

(31) 31 ከዚያም እናንተ በትንሳኤ ቀን እጌታችሁ ዘንድ ትከራከራላችሁ::

(32) 32. በአላህ ላይም ከዋሸ እውነቱንም በመጣለት ጊዜ ካስተባበለ ሰው ይበልጥ በዳይ ማን ነው? በገሀነም ውስጥ ለከሓዲያን መኖሪያ የለምን? (አለ እንጂ)::

(33) 33. ያም በእውነት የመጣውና በእርሱ ያመነዉም እነዚያ እነርሱ አላህን ፈሪዎቹ ናቸው::

(34) 34. ለእነርሱም በጌታቸው ዘንድ የሚሹት (የሚፈልጉት) ሁሉ አላቸው:: ይህ የበጎ አድራጊዎች ምንዳ ነው::

(35) 35. አላህ ያንን በስህተት የሰሩትን መጥፎ ስራ ከእነርሱ ሊሰርዝላቸውና በዚያም ይሰሩት በነበሩት መልካም ስራ ምንዳቸውን ሊመነዳቸው ይህንን አደረገ::

(36) 36. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በእነዚያ ከእርሱ ሌላ በሆኑትም ጣኦታት ያስፈራሩሀል፤ አላህ ለባሪያው በቂ አይደለምን? አላህ የሚያጠመውን ለእርሱ ምንም አቅኝ የለዉም::

(37) 37. አላህ የሚያቀናውንም ለእርሱ ምንም አጥማሚ የለዉም:: አላህ አሸናፊውና የመበቀል ባለቤት አይደለምን?

(38) 38. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ሰማያትንና ምድርን የፈጠረ ማን እንደሆነ ብትጠይቃቸው «አላህ ነው» ይሉሃል:: «ከአላህ ሌላ የምትገዟቸውን ጣዖታት አያችሁን? እስቲ ንገሩኝ:: አላህ በጉዳት ቢፈልገኝ እነርሱ ጉዳቱን ገላጮች ናቸውን? ወይስ በችሮታው ቢፈልገኝ እነርሱም ችሮታውን አጋጆች ናቸውን?» በላቸው:: «አላህ በቂዬ ነው:: በእርሱ ላይ ተመኪዎች ይመካሉ» በል::

(39) 39. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በላቸውም: «ህዝቦቼ ሆይ! ባላችሁበት ሁኔታ ላይ ሁናችሁ ስሩ:: እኔም ባለሁበት ሁኔታ ላይ ሁኜ ሰሪ ነኝና:: ወደ ፊትም ትክክለኛው የቱ እንደነበር ታውቃላችሁ።

(40) 40. «ያንን የሚያሳፍረው ቅጣት የሚመጣበትንና በእርሱ ላይ ዘውታሪ ቅጣት የሚሰፍርበትን ማንነት ታውቃላቸሁ።»

(41) 41. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እኛ መጽሐፉን ባንተ ላይ ለሰዎች ጥቅም በእውነት አወረድነው:: እናም በሱ የተመራ ሰው ሁሉ ፋይዳው ለነፍሱ ነው:: የጠመመም ሰው ጉዳቱ ለራሱ ነው የሚጠመው:: አንተም ታስገድዳቸው ዘንድ በእነርሱ ላይ ጠባቂ አይደለህም::

(42) 42. አላህ ነፍሶችን በሞታቸው ጊዜ ይወስዳል:: ያችንም ያልሞተችውን ነፍስ በእንቅልፈ ጊዜ ይወስዳታል:: ከዚያም ያችን ሞትን የፈረደባትን ነፍስ ይይዛታል:: ሌላይቱን ደግሞ እስከተወሰነ ጊዜ ድረስ ይለቃታል:: በዚህ ውስጥ ለሚያስተነትኑ ህዝቦች ሁሉ አያሌ ተአምራት አሉበት::

(43) 43. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ይልቁንም ቁረይሾች ከአላህ ሌላ አማላጆችን ያዙ። «እነርሱ ምንም የማይችሉና ምንም የማያውቁ ቢሆኑም ታመልኳቸዋላችሁን?» በላቸው።

(44) 44. «ምልጃ ሁሉም የአላህ ብቻ ነው:: የሰማያትና የምድር ስልጣንም የእርሱ ብቻ ነው:: ከዚያም ወደ እርሱ ትመለሳላችሁ» በላቸው::

(45) 45. አላህ ብቻዉን በተወሳ ጊዜ የእነዚያ በመጨረሻይቱ ዓለም የማያምኑት ሰዎች ልቦች ይሸማቀቃሉ (ይደነብራሉ) እነዚያ ከእርሱ ሌላ የሆኑት ጣዖታት በተወሱ ጊዜ ደግሞ እነርሱ ወዲያውኑ ይደሰታሉ።

(46) 46. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «ሰማያትንና ምድርን የፈጠርክ ሩቁንም ቅርቡንም አዋቂ የሆንከው አላህ ሆይ! አንተ በባሮችህ መካከል በዚያም ይለያዩበት በነበሩት ነገር ትፈርዳለህ» በል::

(47) 47. ለነዚያም ለበደሉት በምድር ያለው ሁሉ መላዉም ከእርሱ ጋር መሰሉም ቢኖራቸው ኖሮ በትንሳኤ ቀን ከቅጣቱ ክፋት የተነሳ በእርሱ ነፍሶቻቸውን በተበዡበት ነበር:: ለእነርሱም ከአላህ ዘንድ ያስቡት ያልነበሩት ሁሉ ይገለጽላቸዋል::

(48) 48. ለእነርሱም የሰሯቸው መጥፎዎቹ ይገልጹላቸዋል:: በእነርሱም ላይ በእርሱ ያላግጡበት የነበሩት ቅጣት ይሰፍርባቸዋል::

(49) 49. ሰውም ጉዳት ባገኘው ጊዜ ይጠራናል:: ከዚያም ከእኛ የሆነውን ጸጋ በሰጠነው ጊዜ «እርሱን የተሰጠሁት በእውቀቴ ብቻ ነው።» ይላል:: ይልቁንም እርሷ (ጸጋይቱ) መፈተኛ ናት:: ግን አብዛሀኞቻቸው አያውቁም::

(50) 50. እነዚያ ከእነርሱ በፊት የነበሩት ህዝቦች ይችኑ ቃል በእርግጥ ብለዋታል:: ይሰሩት የነበሩትም ነገር ከእነርሱ አልጠቀማቸዉም::

(51) 51. የሰሯቸዉም መጥፎዎች ቅጣት አገኛቸው:: ከእነዚህም እነዚያ የበደሉት የሰሯቸውን መጥፎዎች ፍዳ በእርግጥ ይነካቸዋል:: እነርሱም አምላጮች አይደሉም::

(52) 52. አላህ ሲሳዩን ለሚሻው ሰው የሚያሰፋ፤ ለሚሻው ሰው የሚያጠብም መሆኑን አያውቁምን? በዚህ ውስጥ ለሚያምኑት ህዝቦች ሁሉ አያሌ ግሳጼዎች አሉበት::

(53) 53. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በላቸው «እናንተ በነፍሶቻችሁ ላይ ድንበር ያለፋችሁ ባሮቼ ሆይ! ከአላህ እዝነት ተስፋ አትቁረጡ:: አላህ ኃጢአቶችን ሁሉ ይምራልና:: እነሆ እርሱ መሀሪዉና አዛኙ ነውና።»

(54) 54. (ሰዎች ሆይ!) ቅጣቱ ወደ እናንተ ከመምጣቱና ከዚያም የማትረዱ ከመሆናችሁ በፊት ወደ ጌታችሁ (በመጸጸት) ተመለሱ:: ለእርሱም ታዘዙ::

(55) 55. እናንተ የማታውቁ ስትሆኑ ቅጣቱ በድንገት ሳይመጣባችሁ በፊት ከጌታችሁ ወደ እናንተ የተወረደውን መልካሙን መጽሐፍ ተከተሉ::

(56) 56. የካደች ነፍስ ሁሉ «እኔ ከሚሳለቁት የነበርኩ ስሆን በአላህ በኩል ባጓደልኩት ዋ! ጸጸቴ!» የምትል እንዳትሆን

(57) 57. ወይም «አላህ በመራኝ ኖሮ ከሚጠነቀቁት ሰዎች እሆን ነበር።» የምትል እንዳትሆን

(58) 58. ወይም ቅጣቱን በምታይ ጊዜ «ለእኔ ወደ ምድረ አለም አንድ ጊዜ የመመለስ ዕድል በኖረኝና ከበጎ አድራጊዎች በሆንኩ።» የምትል ከመሆኗ በፊት መልካሙን ተከተሉ::

(59) 59. የለም ተመርተሃል:: አንቀፆቼ በእርግጥ መጥተውሃል:: በእነርሱም አስተባብለሃል፤ ኮርተሃልም:: ከከሓዲያንም ሆነሃል (ይባላል)::

(60) 60. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በትንሳኤ ቀንም እነዚያን በአላህ ላይ የዋሹትን ፊቶቻቸው የጠቆሩ ሆነው ታያቸዋለህ:: በገሀነም ውስጥ ለትዕቢተኞች መኖሪያ የለምን?

(61) 61. እነዚያም የተጠነቀቁትን በማግኛቸው ስፍራ ሆነው አላህ ያድናቸዋል፤ ክፉ ነገር አይነካቸዉም:: እነርሱም አያዝኑም::

(62) 62. አላህ የነገሩ ሁሉ ፈጣሪ ነው:: እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ አስተናባሪ ነው::

(63) 63. የሰማያትና የምድር (ድልብ) መከፈቻዎች የእርሱ ብቻ ናቸው:: እነዚያም በአላህ አናቅጽ የካዱት እነዚያ እነርሱ ከሳሪዎቹ ናቸው::

(64) 64. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «እናንተ መሃይማን ሆይ! ከአላህ ሌላን እንድንገዛ ታዙኛላቸሁን?» በላቸው::

(65) 65. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ብታጋራ ስራህ በእርግጥ ይታበሳል:: በእርግጥም ከከሓዲያን ትሆናለህ በማለት ወደ አንተና እነዚያ ካንተ በፊት ወደ ነበሩት ሰዎች በእርግጥ ተወርዷል::

(66) 66. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ይልቅ አላህን ብቻ ተገዛም:: ከአመስጋኞችም ሁን::

(67) 67. አላህንም በትንሳኤው ቀን ምድርን በመላ ጭብጡ ስትሆንና ሰማያትም በቀኝ እጁ የሚጠቀለሉ ሲሆኑ ከእርሱ ጋር ሌላን በማጋራታቸው ተገቢ ክብሩን አላከበሩትም:: ከሚያጋሩት ሁሉ ጠራ። ላቀም::

(68) 68. በቀንዱም ይነፋል:: በሰማያት ውስጥ ያለው ፍጡርና በምድርም ውስጥ ያለው ፍጡር ሁሉ አላህ የሻው ሲቀር በድንጋጤ ይሞታል:: ከዚያም በእርሱ ሌላ መነፋት ይነፋል:: ወዲያውኑም እነርሱ የሚሰራባቸውን የሚጠባበቁ ሆነው ቋሚዎች ይሆናሉ::

(69) 69. ምድርም በጌታዋ ብርሃን ታበራለች፤ መጽሐፉም ይቀርባል:: ነብያትና ምስክሮችም ይመጣሉ:: በመካከላቸዉም በእውነት ይፈረዳል:: እነርሱም አይበደሉም::

(70) 70. ነፍስም ሁሉ የሰራቸውን ስራ ትሞላለች (ትሰፍራለች):: እርሱም የሚሰሩትን ሁሉ አዋቂ ነው::

(71) 71. እነዚያ በአላህ የካዱትም የተከፋፈሉ ቡድኖች ሆነው ወደ ገሀነም ይነዳሉ፤ በመጧትም ጊዜ በሮቿ ይከፈታሉ:: ወደሷ በመጡም ጊዜ ዘበኞቿ «ከእናንተ የሆኑ የጌታችሁን አናቅጽ በእናንተ ላይ የሚያነቡላችሁ የዚህንም ቀን መገናኘት የሚያስጠነቅቋችሁ መልዕክተኞች አልመጧችሁምን ነበርን?» ይሏቸዋል፤ «የለም መጥተውልናል። ግን የቅጣቲቱ ቃል በከሓዲያን ላይ ተረጋገጠች።» (ይላሉ።)

(72) 72. «የገሀነምን በሮች በውስጧ ዘወታሪዎች ስትሆኑ ግቡ የትዕቢተኞችም መኖሪያ ምን ትከፋ!» ይባላል።

(73) 73. እነዚያም ጌታቸውን የፈሩት የተከፋፈሉ ቡድኖች ሆነው ወደ ገነት ይነዳሉ:: በመጧትም ጊዜ ደጃፎቿ የተከፈቱ ሲሆኑ ዘበኞቿም ለእነርሱ «ሰላም በእናንተ ላይ ይሁን ተዋባችሁ፤ ዘወታሪዎች ሆናችሁ ግቧት።» ይሏቸዋል።

(74) 74. «ምስጋና ሁሉ ለአላህ ለዚያ የተስፋ ቃሉን ለሞላልን፤ የገነትንም ምድር በምንሻው ስፍራ የምንሰፍር ስንሆን ላወረሰን ይገባው።» ይላሉ። የሰሪዎችም ምንዳ ምን ያምር!

(75) 75. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) መላዕክትንም በጌታቸው ምስጋና ቀላቅለው የሚያጠሩ ሲሆኑ በአርሹ ዙሪያ ከባቢዎች ሆነው ታያለህ፡፡ በመካከላቸውም እውነት ይፈረዳል። ይባላልም፤ «ምስጋና ሁሉ ለዓለማት ጌታ ለሆነው ለአላህ ብቻ ይገባው።»