(1) 1. አሊፍ፤ ላም፤ ራ፤ እነዚህ አናቅጽ ከመጽሐፍ አናቅጽና ገላጭ ከሆነው ቁርኣን ናቸው።
(2) 2.እነዚያ በአላህ የካዱት ሰዎች በትንሳኤ ቀን ሙስሊሞች በሆኑ ኖሮ ብለው በብዛት ይመኛሉ::
(3) 3. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እነርሱን ተዋቸው:: ይብሉ ይጠቀሙም:: ተስፋም ያዘናጋቸው:: በእርግጥም መጥፎ ፍጻሜያቸውን ያውቃሉ::
(4) 4. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ማንኛይቱንም ከተማ ለእርሷ የተወሰነ መጽሐፍ ጊዜያት ያላት ሆና እንጂ አላጠፋንም::
(5) 5. ማንኛይቱም ሕዝብ የመጥፊያ ጊዜዋን በምንም ዘዴ አትቀድምም:: ከእርሱም በማንም ሀይል አትዘገይምም::
(6) 6. እነዚያ የመካ ከሓዲያን አሉ: «አንተ ያ በእርሱ ላይ ቁርኣን የተወረደለት ሆይ! አንተ በእርግጥ እብድ ነህ።
(7) 7. «ከእውነተኞቹ እንደ ሆንክ መስካሪ መላዕክት ለምን አታመጣልንም?» አሉ።
(8) 8. መላእክትን ደግሞ በእውነት በቅጣት እንጂ አናወርድም:: ያን ጊዜም የሚቆዩ ጊዜ የሚሰጣቸው አይደሉም::
(9) 9. እኛ ቁርኣንን እኛው አወረድነው:: እኛም ጠባቂዎቹ ነን::
(10) 10. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ካንተም በፊት በነበሩት በመጀመሪያዎቹ ሕዝቦች ውስጥ መልክተኞችን በእርግጥ ልከናል:
(11) 11. ማንኛዉም መልዕክተኛ በእርሱ የሚያላግጡበት ሆነው እንጂ አይመጣላቸዉም ነበር::
(12) 12. ልክ እንደዚሁ ማስተባበልን በአመጸኞች ልቦች ውስጥ እናስገባዋለን::
(13) 13. በእርሱ አያምኑበትም፤ የቀድሞዎቹም ድርጊት በእርግጥ አልፋለች (እንደጠፉ ይጠፋሉ)::
(14) 14. በእነርሱም ላይ ከሰማይ ደጃፍን በከፈትንላቸውና በእርሱ ሲወጡ ቢውሉም
(15) 15. «የተዘጉ ዓይኖቻችን ተጭበርብረው ነው:: እንዲያዉም እኛ የተደገመብን ሰዎች ነን።» ባሉ ነበር።
(16) 16. በሰማይም ላይ ከዋክብቶችን በእርግጥ አድርገናል (ፈጥረናል):: ለተመልካቾችም በከዋክብት አጊጠናታል::
(17) 17. ከተባረረ ሰይጣንም ሁሉ ጠብቀናታል::
(18) 18. ግን ወሬ መስማትን የሚሰርቅ ወዲያውኑ አብሪ ችቦ ይከተለዋል:: (ያቃጥለዋል)::
(19) 19. ምድርንም ዘረጋናት:: በውስጧም ኮረብታዎችን ጣልንባት:: በውስጧም የተለካን በቃይ ሁሉ አበቀልንባት::
(20) 20.(ሰዎች ሆይ!) በእርሷ ውስጥ ለእናንተ ልዩ ልዩ መኖሪያዎችንና ለእርሱ መጋቢዎቹ ያልሆናችሁትንም እንስሳትን አደረግንላችሁ::
(21) 21. መጋዘኖቹም መክፈቻቸው እኛው ዘንድ ያልሆነ ምንም ነገር የለም:: በተወሰነም ልክ እንጂ አናወርደዉም::
(22) 22. ንፋስን ደመናን ተሸካሚዎች አድርገን ላክን:: ከሰማይም ከደመና ዝናብን አወረድን:: እርሱንም አጠጣናችሁ:: እናንተ ለእርሱ አድላቢዎች (አከማቾች) አይደላችሁም::
(23) 23. እኛ ሕያው የምናደርግና የምንገድል እኛው ብቻ ነን:: እኛው ፍጡርን ሁሉ የምንወርስ ቀሪ ነን::
(24) 24. ከናንተም ተቀዳሚዎቹን በእርግጥ አውቀናል:: ወደ ኋላ ቀሪዎቹንም በእርግጥ አውቀናል::
(25) 25. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!)ጌታህ ይሰበስባቸዋል:: እርሱ ጥበበኛና ሁሉን አዋቂ ነውና::
(26) 26. ሰውንም ከሚቅጨለጨል ሸክላ ከሚገማ ጥቁር ጭቃ በእርግጥ ፈጠርነው::
(27) 27. ጃንን ከሰው በፊት ከእሳት ነበልባል ፈጠርነው::
(28) 28. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህም ለመላዕክት ባለ ጊዜ (የሆነውን አስታውስ): «እኔ ሰውን ከሚቅጨለጨል ሸክላ ከሚገማ ጭቃ እፈጥራለሁ።
(29) 29. «ፍጥረቱን ባስተካከልኩትና በውስጡ ከመንፈሴ በነፋሁበትም ጊዜ ለእርሱ ሰጋጆች ሆናችሁ ውደቁ።»
(30) 30. መላዓክትም ሁሉም ተሰብስበው ሰገዱ::
(31) 31. ዲያብሎስ ብቻ ሲቀር:: እርሱማ ከሰጋጆቹ ጋር ከመሆን እንቢ አለ።
(32) 32. አላህም፡ «ዲያብሎስ ሆይ! ከሰጋጆቹ ጋር የማትሆን ላንተ ምን ምክንያት አለህ?» አለው።
(33) 33. «ከሚቅጨለጨል ሸክላ ከግም ጭቃ ለፈጠርከው ሰው ልሰግድ አይገባኝም።» አለ።
(34) 34. አላህም አለው: «ከእርሷም ውጣ አንተ የተባረርክ እርጉም ነህና።
(35) 35. «ባንተ ላይም እስከ ፍርዱ ቀን ድረስ እርግማን አለብህ።» አለው።
(36) 36. «ጌታዬ ሆይ! እንግዲያውስ እስከሚቀሰቀሱበት ቀን ድረስ አቆየኝ።» አለ።
(37) 37. አላህም አለ፡- «አንተ ከሚቆዩት ነህ።
(38) 38. «እስከታወቀው ቀን ድረስ።»
(39) 39. ዲያብሎስም አለ፡- «ጌታዬ ሆይ! እኔን በማጥመምህ ይሁንብኝ ለእነርሱ በምድር ላይ ኃጢአትን እሸልምላቸዋለሁ። ሁላቸውንም አጠማቸዋለሁ።
(40) 40. «ከእነርሱ ፍጹሞቹ ባሮችህ ብቻ ሲቀሩ።»
(41) 41. አላህም አለ፡- «ይህ በእኔ ላይ መጠበቁ የተገባ ቀጥተኛ መንገድ ነው።
(42) 42. «እነሆ ባሮቼ! በእነርሱ ላይ አንተ ስልጣን የለህም። ከጠማሞች የተከተለህ ሰው ብቻ ሲቀር።
(43) 43. «ገሀነምም ለእርሱና ለተከተሉት ለሁሉም በእርግጥ ቀጠሯቸው ናት።
(44) 44. «ለእርሷ ሰባት በሮች (ደጃፎች ) አሏት። ለየበሮቹም ሁሉ ከሰይጣናት ቡድኖች የተከፋፈለ ድርሻ አለ።»
(45) 45. እነዚያ ከኃጢአት የተጠነቀቁት በአትክልቶችና በምንጮች ውስጥ ናቸው::
(46) 46. «ጸጥተኞች ሆናችሁ በሰላም ግቧት።» ይባላሉ።
(47) 47. በአልጋዎችም ላይ ፊት ለፊት የሚተያዩ ወንድማማቾች ሆነው በልቦቻቸው ውስጥ ያለውን ቂም ሁሉ እናስወግዳለን::
(48) 48. በእርሷም ውስጥ ምንም ድካም አይነካቸዉም፤ እነርሱም ከእርሷ ለምንጊዜም የሚወጡ አይደሉም::
(49) 49. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) መሃሪና አዛኝ እኔው ብቻ መሆኔን ለባሮቼ ንገር::
(50) 50. ቅጣቴም እርሱ አሳማሚ ቅጣት መሆኑንም ንገራቸው።
(51) 51. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከኢብራሂም እንግዶችም ወሬ ንገራቸው::
(52) 52. በእርሱ ላይ በገቡና ሰላም ባሉት ጊዜ (የሆነውን አስታውስ):: እርሱም፡- «እኛ ከናንተ ፈሪዎች ነን።» አላቸው።
(53) 53. «አትፍራ እኛ አዋቂ በሆነ ወንድ ልጅ እናበስርሃለን።» አሉት።
(54) 54. «እርጅና የደረሰብኝ ከመሆኔ ጋር አበሰራችሁኝን? በምን ታበስሩኛላችሁ?» አለ።
(55) 55. «በእውነት አበሰርንህ ከተስፋ ቆራጮችም አትሁን።» አሉ።
(56) 56. «ከጠማማዎችም በስተቀር ከጌታው እዝነት ተስፋን የሚቆርጥ ማነው?» አለ።
(57) 57. «እናንተ መልዕክተኞች ሆይ! ኧረ ለመሆኑ ነገራችሁ ምንድን ነው?» አለ።
(58) 58. አሉም: «እኛ አመፀኞች ወደ ሆኑ ሕዝቦች ተልከናል።
(59) 59. «የሉጥ ቤተሰቦች ብቻ ሲቀሩ እነርሱን እኛ ሁላቸውንም በእርግጥ የምናድናቸው ነን።
(60) 60. «ሚስቱ ብቻ ስትቀር።» (አሉ) እርሷንማ በቅጣቱ ውስጥ ከሚቀሩት ሰዎች መሆኗን ወስነናል።
(61) 61. መልዕክተኞቹም የሉጥን ቤተሰቦች በመጡባቸው ጊዜ።
(62) 62. ሉጥ «እናንተ የተሳሳታችሁ ሕዝቦች ናችሁ።» አላቸው።
(63) 63. አሉም: «አይደለም:: እኛ ህዝቦችህ በእሱ ይጠራጠሩበት በነበሩት ቅጣት መጣንልህ።
(64) 64. «እውነትንም ይዘን መጣንልህ:: እኛም በእርግጥ እውነተኞች ነን።
(65) 65. «ከቤተሰብህ ጋር በሌሊቱ ከፊል (አጋማሽ) ላይ ሂድ:: በኋላቸዉም ተከተል:: ከናንተም አንድም ሰው ወደ ኋላው አይገላመጥ:: ወደ ታዘዛችሁበትም ስፍራ እለፉ።» አሉት::
(66) 66. ወደ እርሱም ያንን ትዕዛዝ አወረድን :: እርሱም የእነዚህ ሕዝቦች መጨረሻ ያነጉ ሲሆኑ ስራቸው መቆረጥ ነው::
(67) 67. የከተማይቱም ሰዎች የሚበሳሰሩ ሆነው መጡ::
(68) 68. ሉጥም አለ፡- «እነዚህ እንግዶቼ ናቸውና አታጋልጡኝ።
(69) 69. «አላህንም ፍሩ አታሳፍሩኝም።»
(70) 70. «ከዓለማት ማንንም እንዳታስተናግድ አልከለከልንህምን?» አሉት።
(71) 71. ሉጥም፡- «እነዚህ ሴቶች ልጆቼ ናቸው። የምትፈጽሙ ከሆናችሁ አግቧቸው።» አለ።
(72) 72. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በዕድሜህ እንምላለን እነርሱ በእርግጥ በስካራቸው ውስጥ ይዋልላሉ::
(73) 73. ጩኸቲቱም ጸሐይ የወጣችባቸው ሲሆኑ ያዘቻቸው::
(74) 74. ላይዋንም ከታችዋ አደረግን:: በእነርሱም ላይ የሸክላ ድንጋዮችን አዘነብንባቸው::
(75) 75. በዚህ ውስጥ ለተመልካቾች በእርግጥ ብዙ መገሰጫዎች አሉበት::
(76) 76. እርሷም ከተማይቱ በቀጥታ መንገድ ላይ ናት::
(77) 77. በዚህ ውስጥ በእርግጥ ለአማኞች መገሰጫ አለ::
(78) 78. እነሆ የአይካ ሰዎችም በእርግጥ በዳዮች ነበሩ::
(79) 79. ከእነርሱም ተበቀልን ሁለቱም የሉጥና የአይከት ሕዝቦች ከተሞች በእርግጥ በግልጽ መንገድ ላይ ናቸው::
(80) 80. የሒጅር ሰዎች መልዕክተኞቹን በእርግጥ አስተባበሉ::
(81) 81. ተዓምራታችንን ሰጠናቸው ከርሷም ዘንጊዎች ነበሩ::
(82) 82. ከኮረብታዎችም ቤቶችን ጸጥተኞች ሆነው ይጠርቡ ነበር::
(83) 83. ያነጉ ሲሆኑ ጩኸት ያዘቻቸው (ወደሙ)።
(84) 84. ይሠሩት የነበሩትም ምንም አልጠቀማቸዉም::
(85) 85. ሰማያትንና ምድርን በመካከላቸው ያለውንም ሁሉ በእውነት እንጂ በላግጣ አልፈጠርንም:: ሰዓቲቱም በእርግጥ መጪ ናት:: መልካምን ይቅርታ አድርግላቸው::
(86) 86. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህ እርሱ ያልነበረን ነገር ሁሉ ፈጣሪው፤ አዋቂው ነው።
(87) 87. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ከሚደጋገሙ የሆኑን ባለ ሰባት አንቀጽንና ታላቁንም ቁርኣን በሙሉ በእርግጥ ሰጠንህ::
(88) 88. ከእነርሱ ከከሓዲያን ብዙዎችን ወገኖች በእርሱ ወደ አጣቀምንበት ጸጋ ዓይኖችህን አትዘርጋ፤ በእነርሱም ላይ ባያምኑ አትዘን፤ ክንፍህንም ለአማኞች አለዝብ።
(89) 89. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «ግልጽ አስፈራሪ እኔ ነኝ።» በል።
(90) 90. (ሰዎችን ለማገድ የመካን በሮች) በተከፋፈሉት ላይ እንደ አወረድነው (ቅጣት አስፈራሪያችሁ ነኝ በል)::
(91) 91. እነርሱም እነዚያ ቁርኣንን ክፍልፍሎች ያደረጉ ናቸው::
(92) 92. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) በጌታህ እንምላለን ሁላቸውንም እንጠይቃቸዋለን::
(93) 93. ይሠሩት ከነበሩት ነገር ሁሉ
(94) 94. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) የታዘዝክበትንም ነገር በይፋ ግለጽ:: አጋሪዎችንም ተዋቸው::
(95) 95. ተሳላቂዎችንም ሁሉ እኛ በቅተንሃል::
(96) 96. እነርሱም እነዚያ ከአላህ ጋር ሌላ አምላክን ያደረጉ ናቸው:: በእርግጥም ፍጻሜያቸውን ወደፊት ያውቃሉ::
(97) 97. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) አንተም በሚሉት ነገር ልብህ የሚጠብ መሆኑን እናውቃለን::
(98) 98. ጌታህን ከማመስገን ጋር አጥራው:: ከሰጋጆቹም ሁን::
(99) 99. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እውነቱም ነገር (ሞት) እስኪመጣልህ ድረስ ጌታህን ተገዛ::