28 - Al-Qasas ()

|

(1) 1.ጧ፤ ሲን፤ ሚም፤

(2) 2. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) እነዚህ አናቅጽ ገላጭ ከሆነው መጽሐፍ አናቅጽ ናቸው::

(3) 3. ከሙሳና ከፈርዖን ዜና ለሚያምኑ ህዝቦች ሁሉ ባንተ ላይ እናነባለን::

(4) 4. ፈርዖን በምድር ላይ ተንበጣረረ:: ነዋሪዎቿንም የተከፋፈሉ ጓዶች አደረጋቸው:: ከእነርሱም ቡድኖችን ያዳክማል:: ወንዶች ልጆቻቸውን በብዛት ያርዳል:: ሴቶቻቸውንም ይተዋል፤ እርሱ ከሚያበላሹት ሰዎች ነበርና::

(5) 5. በእነዚያ በምድር ውስጥ በተጨቆኑት ህዝቦች ላይ ልንለግስና መሪዎችም ልናደርጋቸው ወራሾችም ልናደርጋቸው እንሻለን::

(6) 6. ለእነርሱም በምድር ላይ ልናስመች ፈርዖንን፤ ሃማንንና ሰራዊቶቻቸውንም ከእነርሱ ይፈሩት የነበሩትን ነገር ልናሳያቸው እንሻለን::

(7) 7. ወደ ሙሳም እናት “አጥቢው፤ በእርሱም ላይ በፈራሽ ጊዜ በባህሩ ውስጥ ጣይው፤ አትፍሪም:: አትዘኝም:: እኛ ወዳንቺ መላሾቹና ከመልእክተኞቹም አድራጊዎቹ ነንና” ማለትን አመለከትን (አወረድን)::

(8) 8. የፈርዖን ቤተሰቦችም መጨረሻው ለእነርሱ ጠላት ሐዘንም ይሆን ዘንድ አነሱት:: ፈርዖንና ሃማንም ሰራዊቶቻቸዉም ኃጢአተኞች ነበሩ::

(9) 9. የፈርዖንም ሚስት “ለእኔም ሆነ ላንተ የዓይናችን መርጊያ ነው:: አትግደሉት:: ሊጠቅመን ወይም ልጅ ልናደርገው ይከጀላልና” አለች:: እነርሱም ፍጻሜውን የማያውቁ ሆነው (አነሱት)::

(10) 10. የሙሳም እናት ልብ ባዶ ሆነ:: ከምእምናን ትሆን ዘንድ በልቧ ላይ ባላጠነከርን ኖሮ ልትገልጸው ቀርባ ነበር::

(11) 11. ለእህቱም “ተከታተይው” አለቻት:: (እርሱንም) እነርሱ የማያውቁ ሲሆኑ በሩቅ ሆና አየችው፤

(12) 12. ወደ እናቱ ከመመለሱ በፊትም አጥቢዎችን መጥባትን በእርሱ ላይ እርም አደረግን:: እህቱም “ለእናንተ የሚያሳድግላችሁን እነርሱም ለእርሱ ቅን አገልጋዮች የሆኑን ቤተሰቦች ላመልክታችሁን?” አለችም።

(13) 13. ወደ እናቱም ዓይኗ እንድትረጋ እንዳታዝንም የአላህም የተስፋ ቃል እርግጥ መሆኑን እንድታውቅ መለስነው:: ግን አብዛኞቻቸው አያውቁም::

(14) 14. ብርታቱንም በደረሰና በተስተካከለ ጊዜ ጥበብንና እውቀትን ሰጠነው፤ ልክ እንደዚሁም መልካም ሰሪዎችን እንመነዳለን::

(15) 15. ሙሳ ከተማይቱንም ሰዎቿ በዝንጋቴ ላይ ሆነው ሳሉ ገባ:: በእርሷም ውስጥ የሚጋደሉን ሁለት ሰዎች አገኘ:: ይህ (አንዱ) ከወገኑ ነው፤ ይህ (ሌላው) ደግሞ ከጠላቱ ነው፤ ያ ከወገኑ የሆነው ሰው በዚያ ከጣላት በሆነው ሰው ላይ እርዳታን ጠየቀው:: ሙሳም በጡጫ መታው:: ገደለዉም:: “ይህ ከሰይጣን ስራ ነው:: እርሱ ግልጽ አሣሣች ጠላት ነውና” አለ::

(16) 16. “ጌታዬ ሆይ! እኔ ነፍሴን በደልኩ ለኔም ማር” አለ ለርሱም ምህረት አደረገለት:: እርሱ መሓሪና አዛኝ ነውና::

(17) 17. “ጌታዬ ሆይ! በእኔ ላይ በመለገስህ ይሁንብኝ (ከስህተቴ እጸጸታለሁ):: ለአመጸኞችም ፈጽሞ ረዳት አልሆንም” አለ::

(18) 18. በከተማይቱም ውስጥ ፈሪና የሚጠባበቅ ሆኖ አደረ:: በንጋቱም ያ ትላንት እርዳታን የጠየቀው ሰው በጩኸት እርዳታን ይጠይቀዋል:: ሙሳም ለእርሱ፡- “አንተ በእርግጥ ግልጽ ጠማማ ነህ” አለው::

(19) 19. ሙሳ ያንን እርሱ ለሁለቱም ጠላት የሆነው ሰው በኃይል ሊይዘው በፈለገም ጊዜ “ሙሳ ሆይ በትላንትናው ቀን ነፍስን እንደ ገደልክ ልትገድለኝ ትፈልጋለህን? በምድር ላይ ጨካኝ መሆንን እንጂ ሌላ አትፈልግም ከመልካም ሰሪዎች መሆንን አትፈልግም” አለው።

(20) 20. ከከተማይቱም ዳርቻ አንድ ሰው እየሮጠ መጣ “ሙሳ ሆይ! ሹማምንቶቹ ሊገድሉህ ባንተ ይመካከራሉና ውጣ እኔ ላንተ ከመካሪዎች ነኝና” አለው::

(21) 21. የፈራና የሚጠባበቅ ሆኖም ከእርሷ ወጣ:: “ጌታዬ ሆይ! ከበደለኞች ህዝቦች አድነኝ” አለ::

(22) 22. ወደ መድየን አቅጣጫ ፊቱን ባዞረ ጊዜም “ጌታዬ ቀጥተኛውን መንገድ ሊመራኝ እከጅላለሁ” አለ::

(23) 23. ወደ መድየንም ውሃ በመጣ ጊዜ እርሱ ላይ ከሰዎች ቡድኖችን መንጋዎቻቸውን የሚያጠጡ ሆነው አገኘ:: ከእነርሱ በታችም ከውሃው መንጎቻቸውን የሚከለክሉ ሁለት ሴቶች ልጆችን አገኘ። “ነገራችሁ ምንድን ነው?” አላቸው። “እረኞች ሁሉ መንጋዎቻቸውን እስከሚመልሱ አናጠጣም። አባታችንም ትልቅ ሽማግሌ ነው።” አሉት::

(24) 24. ለሁለቱም አጠጣላቸው ከዚያ ወደ ጥላው ዘወር አለና “ጌታዬ ሆይ! እኔ ከመልካም ነገር ወደ እኔ ለምታወርደው ፈላጊ ነኝ” አለ::

(25) 25. ከሁለቱ አንደኛይቱም ከሀፍረት ጋር የምትሄድ ሆና ወደ እርሱ መጣች፤ “አባቴ ለእኛ ያጠጣህልንን ዋጋ ሊሰጥህ ይጠራሃል” አለችው፤ ወደ እርሱ በመጣና ወሬውን በእርሱ ላይ በተረከለትም ጊዜ “አትፍራ:: ከበደለኞች ህዝቦች ድነሃል” አለው::

(26) 26. ከሁለቱ አንደኛይቱም “አባቴ ሆይ ቅጠረው ከቀጠርከው ሰው ሁሉ በላጩ፤ ብርቱው፤ ታማኙ ነውና” አለችው።

(27) 27. “ስምንትን ዓመታት ልታገለግለኝ እኔ ከእነዚህ ሁለት ሴቶች ልጆቼ አንዲቷን ላጋባህ እሻለሁ፤ ዐስርን ብትሞላም ካንተ ነው:: ባንተ ላይ ማስቸገርንም አልሻም:: አላህ የሻ እንደሆነ ከመልካም ሰዎች ሆኜ ታገኘኛለህ” አለው::

(28) 28. ሙሳም "ይህ ውለታ በእኔና ባንተ መካከል ረጊ ነው:: ከሁለት ጊዜያቶች ማንኛውንም ብፈጽም በእኔ ላይ ወሰን ማለፍ የለም:: አላህ በምንለው ላይ ሁሉ ምስክር ነው" አለ።

(29) 29. ሙሳም ጊዜውን በጨረሰና ከቤተሰቦቹ ጋር በሄደ ጊዜ ከጡር ተራራ ጎን እሳትን አየ:: ለቤተሰቡም “እዚህ ቆዩ:: እኔ እሳትን አየሁ:: ከእርሷ አጠገብ ወሬ ወይም ትሞቁ ዘንድ ከእሳት ትንታግን (ችቦን) አመጣላችኋለሁ” አለ::

(30) 30. ወደ እርሷ በመጣም ጊዜ ከሸለቆው ቀኝ ዳርቻ ከዛፊቱ በኩል በተባረከችው ስፍራ ውስጥ “ሙሳ ሆይ! እኔ የዓለማት ጌታ አላህ ነኝ” በማለት ተጠራ።

(31) 31. “ብትርህንም ጣል” ተባለ:: እንደ ትንሽ እባብ ስትስለከለክ ባያትም ጊዜ ወደ ኋላ ዞሮ ሸሸ:: አልተመለሰምም፤ ተባለም: “ሙሳ ሆይ! ተመለስ አትፍራም፤ አንተ ከጥብቆቹ ነህና

(32) 32. "እጅህን በአንገትጌህ ውስጥ አስግባ:: ያለ ነውር ነጭ ሆና ትወጣለችና፤ ክንፍህንም ከፍርሃት ለመዳን ወደ አንተ አጣብቅ:: እነዚህም ከጌታህ የሆኑ ወደ ፈርዖንና ወደ መኳንቶች የሚደርሱ ሁለት አስረጅዎች ናቸው:: እነርሱ አመጠኞች ህዝቦች ነበሩና።“

(33) 33. ሙሳ አለ: "ጌታዬ ሆይ! እኔ ከእነርሱ ነፍስን ገድያለሁ ስለዚህ እንዳይገሉኝ እፈራለሁ::

(34) 34. "ወንድሜንም ሃሩን እርሱ ምላሱ ከእኔ የተባ (የተሻለ) ነው:: እውነተኛነቴንም የሚያረጋግጥልኝ ረዳት ሆኖ ከእኔ ጋር ላከው እኔ ሊያስተባብሉኝ እፈራለሁና።”

(35) 35. (አላህም)፡- “ጡንቻህን በወንድምህ በእርግጥ እናበረታለን:: ለሁለታችሁም ስልጣንን እናደርጋለን:: ወደ እናንተም በመጥፎ አይደርሱም:: በታዓምራታችን ሂዱ:: እናንተና የተከተላችሁ ሁሉ አሸናፊዎች ናችሁ” አላቸው።

(36) 36. ሙሳም ተዓምራቶቻችንም ግልጽ ሆነው በመጣባቸው ጊዜ “ይህ የተቀጠፈ ድግምት እንጅ ሌላ አይደለም:: ይህንንም በመጀመሪያዎች አባቶቻችን ውስጥ አልሰማንም” አሉ::

(37) 37. ሙሳም “ጌታዬ ከእርሱ ዘንድ በቀጥታው መንገድ የመጣውን ምስጉኒትም አገር ለእርሱ የምትሆንለትን ሰው አዋቂ ነው:: እነሆ በደለኞች አይድኑም” አለ።

(38) 38. ፈርዖንም “እናንተ ቡድኖች ሆይ! ከእኔ ሌላ ለእናንተ አምላክን ምንም አላውቅም:: ሃማን ሆይ! ጭቃ ለእኔ አቃጥልልኝ:: ጡብ ስራልኝ:: ለእኔም ከፍተኛ ህንጻን ስራልኝ:: ወደ ሙሳ አምላክ ልወጣ እከጅላለሁና:: እኔም ከውሸታሞች መሆኑን እጠረጥረዋለሁ” አለ።

(39) 39. እርሱም ሰራዊቶቹም በምድር ላይ ያለ አግባብ ኮሩ:: እነርሱም ወደእኛ የማይመለሱ መሆናቸውን ጠረጠሩ::

(40) 40. እርሱንም ሰራዊቱንም በጥብቅ ያዝናቸው:: በባህርም ውስጥ ጣልናቸው:: (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) የበደለኞች መጨረሻም እንዴት እንደነበረ ተመልከት::

(41) 41. ወደ እሳት የሚጠሩ መሪዎችም አደረግናቸው:: በትንሳኤም ቀን አይረዱም::

(42) 42. በዚችም በቅርቢቱ ዓለም ውስጥ እርግማንን አስከተልናቸው:: በትንሳኤም ቀን እነርሱ ከሚባረሩት ናቸው::

(43) 43. የፊተኞቹን የክፍለ ዘመናት ህዝቦችንም ከአጠፋን በኋላ ለሰዎች የልብ ብርሃን መሪም እዝነትም ሲሆን ይገሠጹ ዘንድ ለሙሳ መጽሐፉን በእርግጥ ሰጠነው::

(44) 44. ወደ ሙሳም ትዕዛዝን ባወረድንለት ጊዜ ከተራራው በምዕራባዊው ጎን አልነበርክም:: ከተጣዱትም አልነበርክም::

(45) 45. እኛ ግን ከእርሱ ኋላ አያሌ የክፍለ ዘመናትን ሰዎች አስገኘን:: በእነርሱም ላይ ዕድሜዎች ተራዘሙ:: በመድየንም ሰዎች ውስጥ ተቀማጭና በእነርሱ ላይ አናቅጻችንን የምታነብ አልነበርክም:: እኛ ግን ላኪዎችህ ሆንን::

(46) 46. በጠራነዉም ጊዜ በጡሩ (ጋራ) ጎን አልነበርክም፤ ግን ካንተ በፊት ምንም አስፈራሪ ያልመጣባቸውን ህዝቦች ታስፈራራ ዘንድ ከጌታህ በሆነ ችሮታ ላክንህ ሊገሠጹ ይከጅላልና።

(47) 47. እጆቻቸዉም ባሳለፉት ምክንያት መከራ የምትነካቸውና “ጌታችን ሆይ! አናቅጽህን እንድንከተል ከትክክለኛ አማኞችም እንድንሆን ወደ እኛ መልዕክተኛን አትልክም ኖሯልን? ይህ ሁሉ የሚሉ ባልሆኑ ኖሮ” አንልክም ነበር።

(48) 48. እውነቱም ከኛ ዘንድ በመጣላቸው ጊዜ “ለሙሳ የተሰጠው ብጤ አይሰጠዉም ኖሯልን?” አሉ፤ ከዚህ በፊት ሙሳ በተሰጠው አልካዱምን? “ሁለት የተረዳዱ ድግምቶች ናቸው። እኛ በሁሉም ከሓዲያን ነን” አሉ።

(49) 49. “ከአላህ ዘንድ የሆነን መጽሐፍ እርሱ ከሁለቱም ይበልጥ ቅን የሆነን አምጡ፤ እውነተኞች እንደ ሆናችሁ ብታመጡት እከተለዋለሁ” በላቸው።

(50) 50. እሺ ባይሉህም የሚከተሉት ዝንባሌዎቻቸውን ብቻ መሆኑን ዕወቅ፤ ከአላህም የሆነ መምሪያ ሳይኖረው ዝንባሌውን ብቻ ከተከተለ ይበልጥ የጠመመ አንድም የለም፤ አላህ በደለኞች ህዝቦችን አይመራምና::

(51) 51. ይገሠጹም ዘንድ ቃልን (ቁርኣንን በያይነቱ) ለእነርሱ በእርግጥ አስከታተልን::

(52) 52. እነዚያም ከእርሱ በፊት መጽሐፍን የሰጠናቸው እነርሱ በእርሱ ያምናሉ::

(53) 53. በእነርሱ ላይ በሚነበብላቸዉም ጊዜ «በእርሱ አምነናል:: እርሱ ከጌታችን የሆነ እውነት ነው እኛ ከእርሱ በፊት ሙስሊሞች ነበርን።» ይላሉ።

(54) 54. እነዚያ በመታገሳቸው ምክኒያት ዋጋቸውን ሁለት ጊዜ ይሰጣሉ:: ክፉውንም ነገር በበጎ ምግባር ይገፈትራሉ፤ ከሰጠናቸዉም ሲሳይ ይለግሳሉ::

(55) 55. ውድቅንም ቃል በሰሙ ጊዜ ከእርሱ ይርቃሉ። «ለእኛ ስራዎቻችን አሉን:: ለእናንተም ስራዎቻችሁ አሉላችሁ:: ሰላም በእናንተ ላይ ይሁን ባለጌዎችን አንፈልግም።» ይላሉ።

(56) 56. አንተ የወደድከውን ሰው ፈጽሞ አታቀናም:: ግን አላህ የሚሻውን ሰው ያቀናል:: እርሱም ቅኖቹን አዋቂ ነው።

(57) 57. «ካንተ ጋር ቅንን መንገድ ብንከተል ከምድራችን እንባረራለን።» አሉም:: ከእኛ ዘንድ የተሰጠ ሲሳይ ሲሆን የነገሩ ሁሉ ፍሬዎች ወደ እርሱ የሚሄዱበትን ጸጥተኛ ክልል (መካን) እነርሱ አላስመቸናቸዉምን? ግን አብዛኞቻቸው አያውቁም::

(58) 58. ከከተማም ኑሮዋን ምቾትዋን የካደችን ከተማ ያጠፋናት ብዙ ናት፤ እነዚህም ከእነርሱ በኋላ ጥቂት ጊዜ እንጂ ያልተኖረባቸው ሲሆኑ መኖሪያዎቻቸው ናቸው:: እኛም ከእነርሱ ወራሾች ነበርን።

(59) 59. ጌታህም ከተሞችን በዋናዋ ከተማ ውስጥ አናቅጻችንን በእነርሱ ላይ የሚያነብ መልዕክተኛን እስከሚልክ ድረስ አጥፊ አልነበረም:: ከተሞችንም ባለቤቶችዋ በዳዮች ሆነው እንጂ አጥፊዎች አልነበርንም::

(60) 60. ሰዎች ሆይ! በማንኛዉም ነገር የተሰጣችሁት የቅርቢቱ ሂይወት ጥቅምና ጌጣ ጌጥ ነው:: አላህ ዘንድ ያለዉም ምንዳ በጣም በላጭና ዘውታሪ ነው:: አታውቁምን?

(61) 61. መልካምን ተስፋ ቃል የገባንለትና እርሱም አግኚው የሆነ ሰው የቅርቢቱን ህይወት ጥቅም እንዳስመቸነውና ከዚያ እርሱ በትንሳኤ ቀን ለእሳት ከሚቀረቡት እንደ ሆነው ሰው ነውን?

(62) 62. (አላህ) የሚጠራባቸውንና «እነዚያ ተጋሪዎቼ ትሏቸው የነበራችሁት የት ናቸው?» የሚልበትን ቀን (አስታውስ)::

(63) 63. እነዚያ በእነርሱ ላይ ቅጣቱ የተረጋገጠባቸው ይላሉ «ጌታችን ሆይ እነዚህ እነዚያ ያጠመምናቸው ናቸው፤ እንደጠመምን አጠመምናቸው (ከእነርሱ) ወደ አንተ ተጥራራን:: እኛን ይገዙ አልነበሩም።»

(64) 64. «ለአላህ የምታጋሯቸውንም ጥሩ» ይባላሉ:: ይጠሩዋቸዋልም ግን ለእነርሱ አይመልሱላቸዉም:: ቅጣትንም ያያሉ፤ እነርሱ ይመሩ በነበሩ ኖሮ (አያዩትም ነበር)::

(65) 65. የሚጠራባቸውንና «ለመልዕክተኞች ምንን መለሳችሁ?» የሚልበትን ቀን አስታውስ።

(66) 66. በዚያም ቀን ወሬዎች ሁሉ በእነርሱ ላይ ይሰወሩባቸዋል፤ እነርሱም አይጠያየቁም::

(67) 67. የተጸጸተና ያመነማ መልካምንም የሰራ ከሚድኑት ሊሆን ይከጀላል::

(68) 68. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ጌታህም የሚፈልገውን ይፈጥራል:: ይመርጣልም:: ለእነርሱ ምርጫ የላቸዉም:: አላህ ከማይገባው ሁሉ ጠራ ከሚያጋሯቸዉም ላቀ::

(69) 69. ጌታህም ልቦቻቸው የሚደብቁትንና የሚገልጹትን ሁሉ ያውቃል።

(70) 70. እርሱም አላህ ነው። ከእርሱ ሌላ አምላክ የለም:: ምስጋና ሁሉ በመጀመሪያም በመጨረሻይቱም ዓለም ለእርሱ ብቻ ነው:: ፍርዱም የእርሱ ብቻ ነው፤ ወደ እርሱም ትመለሳላችሁ::

(71) 71. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «አያችሁን? (እስቲ ንገሩኝ) አላህ በእናንተ ላይ ሌሊትን እስከ ትንሳኤ ቀን ድረስ ዘውታሪ ቢያደርገው ከአላህ ሌላ ብርሃንን የሚያመጣላችሁ አምላክ ማነው? አትሰሙምን?» በላቸው።

(72) 72. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) «አያችሁን? አላህ በእናንተ ላይ ቀንን እስከ ትንሳኤ ቀን ድረስ ዘውታሪ ቢያደርገው ከአላህ ሌላ በውስጡ የምታርፉበትን ሌሊት የሚያመጣላችሁ አምላክ ማን ነው? አታስተውሉምን?» በላቸው።

(73) 73. ከችሮታዉም ለእናንተ ሌሊትንና ቀንን በውስጡ ልታርፉበት ከትሩፋቱም ልትፈልጉበት አመስጋኞችም ልትሆኑ አደረገላችሁ::

(74) 74. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) የሚጠራባቸውንም ቀንና «እነዚያ ተጋሪዎቼ ትሉዋቸው የነበራችሁት የት ናቸው?» የሚልበትን ቀን አስታውስ::

(75) 75. ከህዝቦችም ሁሉ መስካሪን እናወጣና «ማስረጃችሁን አምጡ» እንላለን። ያን ጊዜ እውነተኛዉም አምላክነት ለአላህ ብቻ መሆኑን ያውቃሉ:: ይቀጣጥፉት የነበሩትም ከእነርሱ ይጠፋባቸዋል::

(76) 76. ቃሩን ከሙሳ ነገዶች አንዱ ነበር:: በእነርሱም ላይ አመጸ:: ከድልቦችም ያንን መክፈቻዎቹ ብቻ የኃይል ባለቤቶች የሆኑ ቡድኖችን ሸክሙ የሚከብድን ሰጠነው:: ወገኖቹ ለእርሱ ባሉትም ጊዜ አስታውስ: «አትኩራ አላህ ኩራተኞችን አይወድምና።

(77) 77. «አላህም በሰጠህ ሀብት የመጨረሻይቱን አገር ፈልግ:: ሆኖም ከቅርቢቱ አለምም ፈንታህን አትርሳ:: አላህ ወደ አንተ መልካምን እንዳደረገልህ መልካምን አድርግ:: በምድርም ውስጥ ማጥፋትን አትፈልግ:: አላህ አጥፊዎችን አይወድምና።» አሉት።

(78) 78. «(ሀብትን) የተሰጠሁት እኔ ዘንድ ባለው እውቀት ነው።» አለ። አላህ ከእርሱ በፊት ከክፍለ ዘመናት ሰዎች በኃይል ከእርሱ ይበልጥ የበረቱትን ሀብትን በመሰብሰብም ይበልጥ የበዙትን በእርግጥ ያጠፋ መሆኑን አያውቅምን? አመጸኞችም ከኃጢአቶቻቸው ጥያቄ አይጠየቁም።

(79) 79. በህዝቦቹም ላይ በጌጡ ውስጥ ሆኖ ወጣ:: እነዚያ ቅርቢቱን ህይወት የሚፈልጉት «ወይ ምኞታችን! ቃሩን የተሰጠው ቢጤ ምነው ለእኛ በኖረን፤ እርሱ የታላቅ ዕድል ባለቤት ነውና።» አሉ።

(80) 80. እነዚያም ዕውቀትን የተሰጡት «ወዮላችሁ! የአላህ ምንዳ ላመነ ሰው መልካምንም ለሰራ በላጭ ነው:: ታጋሾችም እንጂ ሌላው አያገኛትም።» አሉ።

(81) 81. በእርሱም በቤትም ምድርን ደረባን (አሰጠምን):: ለእርሱም ከአላህ ሌላ የሚረዱት ቡድኖች ምንም አልነበሩትም:: ከሚረዱትም አልነበረም::

(82) 82. እነዚያም በትላንትናው ቀን ስፍራውን ይመኙ የነበሩት «ወይ ጉድ! ለካ አላህ ከባሮቹ ለሚሻው ሰው ሲሳይን ያሰፋል:: ያጠባልም:: አላህ በእኛ ላይ በእምነት ባልለገሰልን ኖሮ ምድርን በእኛ ላይ በገለበጠብን ነበር:: ወይ ጉድ! ከሓዲያን አይድኑም።» የሚሉ ሆነው አነጉ።

(83) 83. ይህች የመጨረሻይቱ አገር ናት:: ለእነዚያ በምድር ውስጥ ኩራትንና ማመጽን ለማይፈልጉት ሁሉ እናደርጋታለን:: ምስጉኒቱም መጨረሻ ለጥንቁቆቹ ብቻ ናት::

(84) 84. በደግ ስራ የመጣ ለእርሱ ከእርሷ በላጭ ምንዳ አለው:: በክፉም ስራ የመጡ እነዚህ መጥፎዎችን የሰሩ ይሰሩት የነበሩትን እንጂ አይመነዱም::

(85) 85. (መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) ያ ቁርኣንን የተከፋፈለ ሆኖ ባንተ ላይ ያወረደውና ህግጋቱን እንድትትገበር ግድ ያደረግብህ አምላክ ወደ መመለሻ (ወደ መካ) በእርግጥ መላሽህ ነው። «ጌታዬ በቅን መንገድ የመጣውንና እርሱም በግልጽ ስህተት ውስጥ የሆነውን አዋቂ ነው» በላቸው።

(86) 86.(መልዕክተኛችን ሙሐመድ ሆይ!) መጽሐፉ ወደ አንተ መወረዱን ተስፋ የምታደርግ አልነበርክም :: ግን ከጌታህ ችሮታ ተወረደልህ:: ለከሓዲያን በፍጹም ረዳት አትሁን::

(87) 87.(መልዕክተኛችንሙሐመድ ሆይ!) ከአላህም አናቅጽ ወደ አንተ ከተወረዱ በኋላ አያግዱህ:: ወደ ጌታህም ሰዎችን ጥራ:: ከአጋሪዎችም አትሁን::

(88) 88. ከአላህም ጋር ሌላን አምላክ አትገዛ:: ከእርሱም በቀር አምላክ የለም። ከእርሱ በስተቀር ሁሉም ጠፊ ነው:: ፍርዱ የእርሱ ብቻ ነው:: ሁላችሁም ወደ እርሱ ትመለሳላችሁ::